አብዲ ሞሃመድ ኡመር በቁጥጥር ስር ዋሉ

የፎቶው ባለመብት, BBC Somali
የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ፕሬዚዳንት የነበሩት አብዲ ሞሃመድ ኡመር በቁጥጥር ስር መዋላቸው ተገለጸ።
አብዲ ሞሃመድ ኡመር ትናንት ከክልሉ ፕሬዚዳንትነታቸው መነሳታቸው ቢገለጽም የኢትዮጵያ ሶማሌ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢሶዴፓ) መሪ ሆነው ይቀጥላሉ ተብሎ ነበር።
የቀድሞው የክልሉ ፕሬዝዳንት በመከላከያ ሠራዊት አባላት በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ ከተደረጉ በኋላ ጅግጅጋ ከሚገኘው ቤተ-መንግሥት እንደተወሰዱ ምንጮች ለቢቢሲ ሶማልኛ ገልጸዋል።
ከቅዳሜ አንስቶ በጂግጂጋ እና በሌሎች የክልሉ ከተሞች የተከሰተውን ሁከት ተከትሎ የሃገር መከላከያ ሠራዊት እና የፌደራል ፖሊስ ወደ ክልሉ ገብቶ ሰላም እንዲያስከብር መታዘዙ የታወሳል።
አህመድ አብዲ ሞሃመድ የቀድሞውን ፕሬዝዳንት በመተካት መሾማቸውም ይታወሳል።
አዲሱ የክልሉ ፕሬዚዳንት አህመድ አብዲ ሞሃመድ የሶማሌ ክልል ፋይናንስ እና ኢኮኖሚ ልማት ቢሮ ሃላፊ በመሆን አገልግለዋል።
አህመድ አብዲ ሞሃመድ ከቢቢሲ ሶማልኛ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የቀድሞው ፕሬዚዳንት ስልጣናቸውን አስረክበው በሰላም የስልጣን ሽግግር መካሄዱን ተናግረው ነበር።
አህመድ አብዲ ሞሃመድ ''አብዲ ሞሃመድ ሥልጣን መልቀቃቸውን ተከትሎ የክልሉ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አዲስ መሪ መርጧል። የቀድሞው ፕሬዚዳንት ሰላማዊ በሆነ ሁኔታ ጂግጂጋ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው ውስጥ እየኖሩ ይገኛሉ'' ሲሉም ትናንት ተናግረው ነበር።















