ናይጄሪያዊው የባህል ሃኪም የተማመነበት ጥይት ማርከሻ ባለመስራቱ ሞተ

A man holds an AK-47 rifle (file image)

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የምስሉ መግለጫ, ጥይት ያከሽፋሉ የሚባሉ ባህላዊ መድሃኒቶችን መሸጥም ሆነ መጠቀም ናይጄሪያ ውስጥ የተለመደ ነው

አንድ ናይጄሪያዊ የባህል ህኪምና አዋቂ የተማመነበት የጥይት ማርከሻ ባለመስራቱ ለሞት ተዳረገ።

የ26 ዓመቱ ቺናካ አድዙዌ ጥይት ያከሽፋል ብሎ ያመነበትን መድሃኒት በአንገቱ ካጠለቀ በኋላ አንድ ደንበኛው ለሙከራ ጥይት በእሱ አቅጣጫ እንዲተኩስ ማዘዙን ተከትሎ ነው ህይወቱ ያለፈው።

የአገሪቱ ደቡብ ምሥራቅ ክፍል ፖሊስ ደንበኛውን በግድያ በቁጥጥር ስር አውሎታል።

የባህል ህክምናና ባህላዊ እምነት በናይጄሪያ የተለመደ ነገር በመሆኑ የብዙዎች ለተለያዩ ህመሞች የባህል ሃኪሞችን ማማከርም በተመሳሳይ የተለመደ ነው።

ሪፖርቶች እንደሚያሳዩት ጥይት ያከሽፋል በሚል ከባህላዊ አምልኮ ጋር በተያያዘ ብዙዎች ህይወታቸውን አጥተዋል።

በተያዘው የአውሮፓውያን ዓመት መጀመሪያ ላይ ባህላዊ መድሃኒት አዋቂ ጥይት ያከሽፋል ያለውን መድሃኒት ጠጥቶ የመድሃኒቱን መስራት ለማረጋገጥ ሲል ባደረገው ሙከራ አንድ ግለሰብ ህይወቱን ማጣቱን ተከትሎ መድሃኒት ሸጩ በቁጥጥር ስር ውሏል።