በዋሽንግተን ዲሲ ለጠ/ሚ አብይ የድጋፍ ሰልፍ ተደረገ

የፎቶው ባለመብት, Ethiotube/ Yesuf Ibrahim
ነዋሪነታቸውን በአሜሪካን ሀገር ያደረጉ በርካታ ኢትዮጵያዊያን ትናንት ሰኔ 20/2010 ዓ.ም በዋሽንግተን ዲሲ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድን ለመደገፍ ያለመ ሰላማዊ ሰልፍ አከናውነዋል፡፡
ከአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ፊት ለፊት በተደረገው ሰልፍ ላይ፣ የአዲሱን ጠቅላይ ሚኒስትር ርምጃዎች የሚደግፉ እና ስለ ኢትዮጵያ አንድነት የሚሰብኩ መፈክሮች ተሰምተዋል፡፡
ለዓመታት የኢትዮጵያን መንግሥት በሚቃወሙ መድረኮች እና ሰልፎች ላይ በመገኘት ንግግሮችን በማድረግ የሚታወቀው አርቲስት ታማኝ በየነ ጨምሮ ታዋቂ የፖለቲካ እና የኪነጥበብ ሰዎች በሰልፉ ላይ መገኘታቸውም ታውቋል፡፡
በሰልፉ ላይ ቅዳሜ ሰኔ 16 በአዲስ አበባ በነበረው የድጋፍ ሰልፍ ላይ በደረሰው የቦንብ ፍንዳታ ለሞቱ እንዲሁም በዓመታት ውስጥ ‹ለፍትህ እና እኩልነት ሲታገሉ› ሕይወታቸውን ላጡ ወገኖች የህሊና ጸሎት ተደርጓል፡፡
ሽመልስ ወልደ ገብረ-ሰንበት የተባሉ የሰልፉ ተሳታፊ ‹‹ሰልፉከዓመታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ኢትዮጵያዊያን ከተቃውሞ ወጥተው ለምስጋና እና ደስታ የተሰባሰቡበት ነበር ›› በማለት ለቢቢሲ ተናግረዋል፡








