የጀርመን ቡንደስሊጋ ቡድኖች ለ'ብላክ ላይቭስ ማተር' ያላቸውን ድጋፍ አሳዩ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የጀርመን ቡንደስሊጋ የእግር ኳስ ቡድኖች ለ'ብላክ ላይቭስ ማተር' እንቅስቃሴ ያላቸውን ድጋፍ በትናንትናው ዕለት በተለያዩ ተቃውሞዎች አሳይተዋል።
የብሮሲያ ዶርትሙንድና ሄርታ በርሊን ተጫዋቾች በሲግናል ኢዱና ፓርክ በመገኘት ሜዳውን በመክበብም በጉልበታቸው ተንበርክከው ነበር።
የዶርትሙንድ ተጫዋቾች ከውድድሩ በፊት ሲያሟሙቁ "ፍትህ ከሌለ ሰላም የለም" እንዲሁም "ተባብረን እንቁም" የሚሉ መልእክቶች በተፃፈባቸው ማሊያዎች (ካናቴራዎች) ነው።
የባየር ሙኒክ ተወዳዳሪዎች "ለዘረኝነት ቀይ ካርድ" የሚል ማሊያ (ካናቴራ) ለብሰው የነበረ ሲሆን፤ በዛኑ ዕለት ባየር ሌቨርኩሰንን 4 ለ2 በሆነ ውጤት ረትተዋል።
የቡንደስሊጋ ቡድኑ አመራሮችም እንዲሁም የቡድኑ አባላት በጨዋታዎች ላይ 'ብላክ ላይቭስ ማተር' የሚል ፅሁፍ ያለበት እጃቸው ላይ አጥልቀው ነበር ተብሏል።
የሜይንዝ ቡድን አጥቂ ካሜሮናዊው ፒየር ኩንዴ ከኤይንትራችት ፍራንክፈርት ጋር ባደረጉት ጨዋታም ላይ ጎል ካስቆጠረ በኋላ በጉልበቱ ተንበርክኳል። በግጥሚያው ቡድኑ 2 ለ0 ረትቷል።
በዚህ ሳምንትም ታዋቂዎቹ የስፖርት ሰዎች ሴረና ዊልያምስ፣ ፓውል ፖግባና ሊውስ ሃሚልተን በአሜሪካ በጥቁሮች ላይ የሚፈፀመውን የፖሊስ ጭካኔ አስመልክቶ ድምፃቸውን አሰምተዋል።
ባለፈው ሳምንት በሚኒያፖሊስ ጥቁር አሜሪካዊው ጆርጅ ፍሎይድ እጁ ከኋላ እንደተጠፈረ ከመሬት ላይ ተጣብቆ ነጭ ፖሊስ አንገቱን በጉልበቱ ለዘጠኝ ደቂቃ ተጭኖት ህይወቱ ማለፉን ተከትሎ በበርካታ ግዛቶች ተቃውሞች ተቀጣጥለዋል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የፎቶው ባለመብት, Twitter

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የፎቶው ባለመብት, Getty Images












