ሞዛምቢክ ከሞባይል ስልክ ላይ መረጃ የሚወስዱ ሰዎችን በእስር ልትቀጣ ነው

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የሞዛምቢክ የህዝብ እንደራሴዎች በዘመናዊ የመረጃ መለዋወጫ ዘዴዎች አማካይነት መረጃን የሚመዘብሩ ወንጀለኞችን በተመለከተ የሃገሪቱን የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ማሻሻላቸው ተገለጸ።
በተሻሻለው ሕግ መሰረት ማንኛውም ሰው ከባለቤቶቹ ፈቃድ ውጪ ሞባይል ስልኮችን ጨምሮ ኮምፒውተሮች ወይም ሌሎች መሳሪያዎችን በመጠቀም መረጃ የወሰደ እንደሆነ እስከ ሁለት ዓመት የሚደርስ የእስር ቅጣት ይጣልበታል።
በተጨማሪም ፈቃድ ሳያገኙ የወሰዱትን ለሕዝብ ይፋ የማይደረጉ መረጃዎችን በሕገ ወጥ መንገድ ያዘጋጁ፣ የሸጡ ወይም ያሰራጩ ሰዎች እስከ አምስት ዓመት በሚደርስ እስር እንዲቀጡ ሕጉ ይደነግጋል።
መሻሻል የተደረገበት የሞዛምቢክ የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ በድርጊቱ ላይ የሚገኙ ሰዎች ከሚጣልባቸው የእስር ቅጣት በተጨማሪ ሊያገኙ ይችላሉ ተብሎ የሚታሰበውን ዝቅተኛ የአንድ ዓመት ገቢያቸውን ያህል የሚሆን የገንዘብ ቅጣትም ይጣልባቸዋል።
ሃገሪቱ በነበራት የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ላይ ክለሳ ማድረግ ያስፈልገው እየጨመረ ካለው የዘመናዊ የመረጃ ቴክኖሎጂ ተጠቃሚነት አንጻር ለግለሰቦችና ለተቋማት ተገቢውን ጥበቃ ለመስጠት ሲባል እንደሆነ ተገልጿል።
ሞዛምቢክ ውስጥ ካለው 31 ሚሊዮን የሚደርስ ሕዝብ ውስጥ የሞባይል ስልክ ተጠቃሚ የሆነው ከግማሽ ያነሰው ብቻ ነው።















