ቀጥታ, ፊፋ ለዓለም ዋንጫ አሸናፊዎች ቀለበት ሊሸልም ነው፤ ትራምፕ የፍጻሜውን ውድድር ይታደማሉ

ፊፋ እሁድ ዕለት በአርጀንቲና እና በስፔን መካከል በሚካሄደው የፍፃሜ ጨዋታ አሸናፊ ለሚሆነው ቡድን የዓለም ዋንጫ ቀለበቶችን እንደሚሸልም ሲገለጽ፣ ዶናልድ ትራምፕም ግጥሚያውን ይታደማሉ ተባለ። ለአሸናፊ ተጋጣሚዎች ቀለበቶችን መሸለም በአሜሪካ ስፖርት ውስጥ የተለመደ ባህል ነው።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ቴህራን፣ አሜሪካ የሰላማዊ ዜጎች መጠቀሚያ የሆኑ መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት አድርሳለች ስትል ከሰሰች

    ቢቢሲ ቬሪፋይ በሆርሞዝጋን ግዛት በሚገኝ ድልድይ ላይ ጥቃት መፈጸሙን አረጋግጧል

    የፎቶው ባለመብት, SocialMedia

    የምስሉ መግለጫ, ቢቢሲ ቬሪፋይ በሆርሞዝጋን ግዛት በሚገኝ ድልድይ ላይ ጥቃት መፈጸሙን አረጋግጧል

    በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የሚካሄደው የሰላም ድርድሩ ከተቋረጠ ወዲህ የአሜሪካ ጦር በቅርቡ በፈፀመው የአየር ጥቃት የሲቪል መሠረተ ልማቶችን እየደበደበ ነው ስትል ቴህራን ከሰሰች።

    የመንግሥት ሚዲያዎች እና የአካባቢ ባለሥልጣናት ድልድዮች፣ የባቡር ጣቢያ እና የአየር ማረፊያ መመታታቸውን ተናግረዋል። ቢቢሲ ቬሪፋይ በሆርሞዝጋን ግዛት በሚገኝ ድልድይ ላይ ጥቃት መፈጸሙን አረጋግጧል።

    የአሜሪካማዕከላዊ ዕዝ (ሴንቲኮም) የዒላማዎቹንዝርዝር ባይገልጽም፣ ጥቃቶቹ "የኢራንን ወታደራዊ አቅም የበለጠ ለማዳከም" የታለሙ ናቸውብሏል።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ቴህራን የካቲት 21 2018 ዓ.ም. በአሜሪካ እና በእስራኤል ጥቃቶች የተጀመረውን ጦርነት ለማስቆም ኢራን ወደ ድርድር እንድትመለስ ለማስገደድ ድልድዮችን እና የኃይል ማመንጫ ጣቢያዎችን እንደሚመቱ ዝተው ነበር።

    ኢራን የአሜሪካ ጦር ጥቃትን ተከትሎ በባህረ ሰላጤው ውስጥ በሚገኙ የዩኤስኤ ጦር ሰፈሮች እና አጋሮች ላይ የበቀል እርምጃ እንድትወስድ አድርጓታል።

    አሜሪካ ለስድስት ተከታታይ ምሽቶች በኢራን ዒላማዎች ላይ የአየር ድብደባ ስትፈጽም ቆይታለች።

    የኢራን የመንግሥት ሚዲያዎች እና የአካባቢው ባለሥልጣናት ሐሙስ ምሽት ላይ በደቡብ ምሥራቅ ኢራን የሚገኘው የኢራንሻህር አውሮፕላን ማረፊያ፣ የባቡር ጣቢያ እና በሆርሞዝጋን ግዛት የሚገኙ ስድስት ድልድዮች ጥቃት እንደ ደረሰባቸው ዘግበዋል።

    በሆርሞዝጋን የሚገኙ የክልል ባለሥልጣናት ደግሞ ሰባትሰዎች መገደላቸውን ይፋ አድርገዋል።

    ቢቢሲ ቬሪፋይ እና ቢቢሲ ፐርሺያ በጋሪቭህ ድልድይ ላይ የደረሰውን ጉዳት የሚያሳይ ቪዲዮን ትክክለኛለነት አረጋግጠዋል፤ በሌሊት የተቀረጹት ቪዲዮዎች በድልድዩ ላይ የእሳት ነበልባል ሲንቀለቀል አሳይተዋል።

    በቀን የተቀረጹ ምስሎች በተሰበረው ድልድይ ዙሪያ የመንገድ ፍርስራሽ ያሳያል።

    ሴንትኮም በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ ቢጠየቅም ቀደም ሲል ባወጣው መግለጫ ላይ የሚያክለው ምንም ነገር እንደሌለ ተናግሯል።

    ትራምፕ በሚያዝያ ወር አሜሪካ በኢራን ድልድዮችንና የኃይል ማመንጫዎችን ጨምሮ የሲቪል መሠረተ ልማቶችን እንደምትደበድብ ከተናገሩ በኋላ፣ የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብቶች ኃላፊ ቮልከር ቱርክ "ሆን ብሎ ሲቪሎችንና የሲቪል መሠረተ ልማቶችን ማጥቃት የጦር ወንጀል ነው" ብለዋል።

  2. ፊፋ ለዓለም ዋንጫ አሸናፊዎች ቀለበት ሊሸልም ነው፤ ትራምፕ የፍጻሜውን ውድድር ይታደማሉ

    ፊፋ የሚሸልመውን ቀለበት በድረ ገጹ ላይ ይፋ አድርጓል

    የፎቶው ባለመብት, Fifa.com

    የምስሉ መግለጫ, ፊፋ የሚሸልመውን ቀለበት በድረ ገጹ ላይ ይፋ አድርጓል

    ፊፋ እሁድ ዕለትበአርጀንቲና እና በስፔን መካከል በሚካሄደው የፍፃሜ ጨዋታ አሸናፊ ለሚሆነው ቡድን የዓለም ዋንጫ ቀለበቶችን እንደሚሸልም ሲገለጽ፣ ዶናልድ ትራምፕም ግጥሚያውን ይታደማሉ ተባለ።

    ለአሸናፊ ተጋጣሚዎች ቀለበቶችን መሸለም በአሜሪካ ስፖርት ውስጥ የተለመደ ባህል ነው።

    የዓለም ዋንጫ አሸናፊ ለሚሆነው ቡድን 30 ቀለበቶች የሚቀርቡ ሲሆን፣ በተጨማሪ 1,996 ቀለበቶች ለደጋፊዎች ይሸጣሉ። በእያንዳንዱ ቀለበት ላይ አነስተኛ የዓለም ዋንጫ እና ጽሑፍ ተቀርጾበታል።

    ዋንጫውን ለአሸናፊው ቡድን የሚያበረክቱት ፕሬዝዳንት ትራምፕ እስካሁን ድረስ ከ102ቱ የዓለም ዋንጫ ጨዋታዎች መካከል በአንዱም ላይ አልተገኙም።

    አሜሪካ በቤልጂየም ተረትታ ከመሰናበቷ በፊት ያደረገቻቸውን ጨዋታዎችንም ቢሆን አልተከታተሉም።

    በካናዳ የተከሰተውን ሰደድ እሳት ተከትሎ በኒው ዮርክ የሚኖረው አየር ሊበከል እንደሚችል ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷል።

    ነገር ግን በሜትላይፍ ስታዲየም የሚካሄደው የፍፃሜ ውድድር ላይ ተጽዕኖ እንደሚያሳድር የሚጠቁም ምንም ነገርየለም።

    የፊፋ ፕሬዝዳንት ጂያኒ ኢንፋንቲኖ ትራምፕ በፍፃሜው ጨዋታ ላይ እንደሚገኙ አስቀድመው ተናግረው ነበር፤ የዋይት ሐውስ የፕሬስ ሴክሬታሪ ካሮሊን ሌቪት ይህንኑ አረጋግጠዋል።

    አሜሪካ ከቦሲኒያ ሄርዜጎቪኒያ ጋር ባደረገችው የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ላይ በተቃራኒው ቡድን ላይ በሠራው ጥፋት ለአሜሪካው አጥቂ ፎላሪን ባልገን የተሰጠው ቀይ ካርድ እንዲታገድ መደረጉን ተከትሎ በፊፋ ፕሬዚዳንት ላይ ከፍተኛ ትችት ቀርቧል።

    የዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማኅበር (ፊፋ) አጥቂው በቀጣዩ የአገሪቱ ብሔራዊ ቡድን ጨዋታ እንዳይሳተፍ የሚያግደው ውሳኔን የሻረው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በጉዳዩ ላይ ጣልቃ ከገቡ በኋላ ነው።

    በዓለም ዋንጫ ታሪክ 189 ጊዜ ቀይ ካርድ የተሰጠ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ ቀጣዩን ጨዋታ ያለመሳተፍ ዕገዳ ተፈጻሚ ያልሆነው የአሁኑን ጨምሮ በሁለት ተጫዋቾች ላይ ብቻ ነው።

    የዘንድሮው ዓለም ዋንጫ በአሜሪካ፣ በሜክሲኮ እና በካናዳ አስተናጋጅነት የተካሄደ ነው።

    ቅዳሜ ዕለት እንግሊዝ ከፈረንሳይ ለሦስተኝ ደረጃ የምትጫወት ሲሆን አርጀንቲና እና ስፔን ደግሞ እሁድ ዕለት ይጋጠማሉ።

  3. የዩኬ ፖሊስ ለኢራን ደኅንነት መሥሪያ ቤት ድጋፍ አድርጓል ያለውን ግለሰብ ከሰሰ

    የብሪታኒያ ፖሊስ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የብሪታኒያ ፖሊስ አርብ ዕለት የኢራን የደኅንነት መሥሪያ ቤትን አግዟል ባለው የ39 ዓመት ግለሰብ ላይ ክስ መመሥረቱን አስታወቀ።

    ፖሊስ ቫሂድ አበሪ የተባለው የሊቨርፑል ነዋሪ በቁጥጥር ውሎ ማዕከላዊ እንግሊዝ ወደ ሚገኝ ፖሊስ ጣቢያ መወሰዱን እና በርሚንግሃም እና ሊቨርፑል የሚገኙ መኖሪያ ቤቶች ላይ ፍተሻ ማካሄዱን አስታውቋል።

    የዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) የደኅንነት ባለሥልጣናት በተደጋጋሚ ኢራን በአገሪቱ ውስጥ አለመረጋጋት ለመፍጠር ወንጀለኛ ቡድኖችን ልትጠቀም ትችላለች በማለት ሲያስጠነቅቁ ነበር።

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጦርነት ከከፈቱ ጊዜ ጀምሮ በብሪታኒያ በርካታ ፀረ ሴማዊ ጥቃቶች ተፈጽመዋል።

    በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ብሪታኒያ በኢራን መንግሥት የሚደገፉ አለመረጋጋቶችን ለማስቀረት በሚል ለኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የሚደረግ ድጋፍን አግዳለች።

    አበሪ እስካሁን ድረስ ለየትኛውም ማኅበረሰብ ወይንም ግለሰብ ስጋት መሆኑ አልተለየም ተብሏል።

    ነገር ግን በውጭ የደኅንነት ተቋማት የሚደረጉ ጣልቃ ገብነቶችን ለመከላከል በፍጥነት መንቀሳቀስ እንዳለባቸው ተናግረዋል።

    ባለፈው ሳምንት ብሪታኒያ የኢራን ከፍተኛ ዲፕሎማትን ጠርታ ሁለት ሮማኒያውያን ስለተከሰሱበት በለንደን ስለተፈጸመ የስለት ጥቃት አነጋግራቸዋልች።

    በለንደን የሚገኘው የኢራን ኤምባሲ ከዚህ ቀደም እንዲህ ዓይነቱን ክስ “መሠረት የሌለው፣ ፖለቲካዊ እና ጠብ አጫሪ ውንጀላ ነው” ሲል ውድቅ አድርጎት ነበር።

    በቁጥጥር ስር የዋለው ግለሰብ አርብ ከሰዓት በለንደን በሚገኝ ፍርድ ቤት ይቀርባል ተብሎ ይጠበቃል።

  4. በጋና ፕሬዝዳንት ላይ ሐሰተኛ ዜና ያሠራጨችው ቲክቶከር ተፈረደባት

    ጋናዊቷ ቲክቶከር ካሚላ አልሃሳን

    የፎቶው ባለመብት, Camilla Alhassan/TikTok

    የምስሉ መግለጫ, ጋናዊቷ ቲክቶከር ካሚላ አልሃሳን

    ጋናዊቷ ቲክቶከር ስለ አገሪቱ ፕሬዝዳንት ጆን ማሃማ ባጋራቻቸው ሐሰተኛ ዜናዎች የተነሳ ጥፋተኛ መሆኗ በመረጋገጡ የአንድ ዓመት እስር ተፈረደባት።

    በግንቦት እና ሰኔ ወር መጀመሪያ ላይ ቲክቶከሯ ካሚላ አልሃሳን ፕሬዝዳንቱ የአውሮፓውያኑ 2024ቱን አጠቃላይ ምርጫ እንዲያሸንፉ ለአምልኮ ሥርዓት ማስፈጸሚያ 32 ላሞችን መስዋዕት እንዳደረጉ የሚገልጹ ተከታታይ ቪዲዮዎችን አጋርታለች።

    የ43 ዓመቷ ቲክቶከር በተጨማሪም መንግሥት በቅርቡ በጎርፍ ለተጎዱ ሰዎች የንፅህና መጠበቂያዎችን ለማከፋፈል የወሰደው እርምጃ ፈጽመውታል ያለችውን አምልኮ ሥርዓት ለመደበቅ የተደረገ ሙከራ ነው ስትል ተናግራለች።

    ጉዳዩን የተመለከቱት ዳኛ ቀላል ቅጣት እንዲጣል የቀረበውን ይግባኝ ውድቅ በማድረግ ተመሳሳይ ድርጊትን ያስቀራል ያሉትን የእስር ቅጣት ወስነዋል።

    ዐቃቤ ሕግ በቲክቶክ ላይ ከ70 ሺህ በላይ ተከታዮች ያሏት አልሃሳን በፕሬዝዳንቱ ላይ ተከታታይ የሐሰት እና የስም ማጥፋት ውንጀላዎችን አቅርባለች ሲል ተከራክሯል።

    በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ አልሃሳን እንድትታሰር ምክንያት የሆኑት በስፋት የተጋሩት ቪዲዮዎቿ በጋና በማኅበራዊ ሚዲያ ስለሚሠራጩ ሐሰተኛ መረጃዎች የተነሳ በወንጀል እና ሀሳብን በነፃነት የመግለጽ ነፃነት መካከል ያለውን ሚዛን እንዴት መጠበቅ እንደሚቻል ክርክር አስነስተዋል።

    ዳኛው ፍርዱ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ እየተስፋፋ የመጣውን የሐሰተኛ መረጃ ሥርጭት ለመግታት አስፈላጊ ነበር ብለዋል።

    በጋና ተፅዕኖ ፈጣሪ ሲታሰር ይህ የመጀመሪያው አይደለም።

    በመስከረም ወር፣ ክዋሜ ንክሩማህ II በመባል የሚታወቀው ታዋቂው ቲክቶከር ዴቪድ ክዎድዎ ፕራህ አፍፉል የግድያ ዛቻ በመፈጸም እና ሰላምን የሚያደፈርስ አጸያፊ ተግባር በመፈጸም ጥፋተኛ ሆኖ ከተገኘ በኋላ የሰባት ወራት እስራት ተፈርዶበታል።

    ቲክቶከሩ በስፋት በተጋራው ቪዲዮው ላይ ፕሬዝዳንት ማሃማን እና የፓርላማ አባላትን እንደሚገድል አስፈራርቶ ነበር።

    ባለፈው ዓመት ፕሬዝዳንቱ መንግሥታቸው የማኅበራዊ ሚዲያዎችን "ለማጽዳት" መንገዶችን እያሰበ መሆኑን ተናግረዋል። የአገሪቱ ባለሥልጣናትም የተሳሳተ እና የተዛባ መረጃ የሚያሠራጩትን ተከታትለው እንዲያስሩ መመሪያ ሰጥተዋል።

    “ለጋናውያን ሐሰተኛ ወሬዎችን፣ የጥላቻ ንግግሮችን የምታሠራጩ እና ፍርሃትና ድንጋጤ የሚፈጥሩ ድርጊቶችን የምትፈጽሙ ከሆነ እናገኛችኋለን’ የሚል ምልክት እያስተላለፍኩ ነው” ሲሉ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ተናግረዋል።

  5. ኩዌት በኢራን ጥቃት የውሃ ማጣሪያ እና የኃይል ማመንጫ እንደተመታባት ገለጸች

    የኢራን ሚሳዔል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኩዌት፤ የኢራን ጦር በፈጸማቸው ጥቃቶች የጨው ውሃ ማጣሪያ እና የኃይል ማመንጫ ጣቢያ ላይ ጉዳት መድረሱን አስታወቀች።

    ካለፈው ሳምንት አንስቶ ያገረሸው የአሜሪካ እና ኢራን ግጭት፤ ትናንት ምሽትም ቀጥሎ ታይቷል። አሜሪካ በኢራን የተለያዩ ሥፍራዎች ካደረሰችው ጥቃት በኋላ ቴህራን በምላሹ ጎረቤቶቿ የሆኑ የቀጣናው አገራትን ዒላማ አድርጋለች።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጥቃት ከሰነዘረባቸው አገራት አንዷ ኩዌት እንደሆነች ገልጾ ነበር። የኩዌት የኤሌክትሪክ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ የኢራን ጥቃት በኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ እና የጨው ውሃ ማጣሪያ ላይ ጉዳት ማድረሱን አስታውቋል።

    ጥቃቱ በሥፍራዎቹ “ቃጠሎ እንዲነሳ፣ ጉዳት እንዲሰርስ እና በርካታ የማምረቻ ክፍሎች ከአገልግሎት ውጪ እንዲሆኑ አድርጓል” ብሏል።

    በተቋማቱ ላይ ስለደረሰው ጉዳት ተጨማሪ መረጃ አልተገለጸም።

    ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ዜጎች “በዚህ የተለየ ወቅት የኤሌክትሪክ ፍጆታቸውን እንዲያስተካክሉ እና ኤሌክትሪክ እንዲቆጥቡ” ጠይቋል።

  6. የዋይት ሀውስ የጽሑፍ ማንበቢያ ማሽን ተቆጣጣሪ የትራምፕ ንግግር ላይ ተወራርዶ 100 ሺህ ዶላር በማግኘት ተከሰሰ

    የዋይት ሀውስ የንግግር ጽሑፍ ማንበቢያ ማሽን (ቴሌፕሮምፕተር) ኦፕሬተር

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የዋይት ሀውስ የንግግር ጽሑፍ ማንበቢያ ማሽን (ቴሌፕሮምፕተር) ኦፕሬተር፤ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ንግግሮች ላይ ውርርድ በማድረግ 100,000 ዶላር ገደማ አግኝቷል በሚል ምርመራ ተከፈተበት።

    ቴሌፕሮምፕተር በጽሑፍ የተዘጋጀ ንግግርን በስክሪን ላይ የሚያሳይ ማሽን ነው። እንደ ፕሬዝዳንቶች ያሉ ባለሥልጣናት ወረቀት ሳይዙ ስክሪኑን በመመልከት ንግግራቸውን ለታዳሚዎች እንዲያቀርቡ ያስችላል።

    ከአውሮፓውያኑ 2016 አንስቶ የዋይት ሀውስ ሠራተኛ የሆነው ገብርኤል ፔሬዝ፣ በአሜሪካው ቤተ መንግሥት የሚገኘው እና ፕሬዝዳንቱን ጨምሮ የተለያዩ ባለሥልጣናት ለንግግራቸው የሚጠቀሙበት ቴሌፕሮምፕተር ተቆጣጣሪ ነው።

    ፔሬዝ፣ ፕሬዝዳንቱ በሚያደርጓቸው ዋና ዋና ሕዝባዊ ንግግሮች የሚጠቀሟቸው ቃላት ላይ ሲወራረድ ነበር የሚል ክስ ቀርቦበታል።

    ውርርዱን ሲያካሂድ የነበረው ‘ካልሺ’ በተባለው እና ሰዎች በዓለም የሚከናወኑ ኹነቶችን በተመለከተ በመገመት መወራረድ በሚያስችለው ድረ ገጽ ላይ ነው። ኩባንያው ይህንን ድርጊት በተመለከተ ለተቆጣጣሪው መሥሪያ ቤት ማሳወቁን አረጋግጧል።

    ካልሺ የዋይት ሀውሱ ሠራተኛ ያገኘውን ትርፍ ከማውጣቱ በፊት መወራረጃ አካውንቱ እንዲታገድ ማድረጉን በሪፖርቱ ገልጿል።

    ኩባንያው የሠራተኛውን እንቅስቃሴ መከታተል የጀመረው ባለፈው መጋቢት ላይ ያልተለመደ ዓይነት ውርርድ ከተመለከተ በኋላ መሆኑን ለቢቢሲ ገልጿል።

    ይህ ዓይነት እንቅስቃሴ የተስተዋለው የተለያዩ አካላት በሚያደርጓቸው ንግግሮች የሚጠቀሟቸውን ቃላት በመገመት እንዲወራረዱ በሚያስችለው የግብይት ዓይነት ላይ ነው።

    በዚህ መልኩ ውርርድ የሚያደርጉ ተጫዋቾች፤ በንግግሮች ውስጥ የሆነ አገር፣ ኢኮኖሚያዊ ቃል ወይም የቅስቀሳ መፈክር ይጠቀስ እንደሆነ በመገመት ገንዘብ ያስይዛሉ።

    ካልሺ “እንደ ፕሬዝዳንቶች እና የብሔራዊ ባንክ ገዢዎች ያሉ የፖለቲካ መሪዎች ቃላት በፎሬክስ፣ የነዳጅ ኦፕሽን እና የአክስዮን ገበያ ላይ በቢሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር እንዲንቀሳቀሱ ያደርጋሉ” በማለት አስረድቷል።

    ካልሺ ተወራራጁ በዋይት ሀውስ ውስጥ በጽሑፍ የተዘጋጁ ንግግሮች ወደ ማንበቢያው ማሽን (ቴሌፕሮፕተር) የሚያስገባ የፌደራል ሠራተኛ መሆኑን የደረሰበት የአካውንቱን መረጃ በመጠቀም ነው።

    የዋይት ሀውስ ሠራተኛው ያገኘውን 90 ሺህ ዶላር ከማውጣቱ በፊት ታግዶበታል።

    የዋይት ሀውስ ፕሬስ ሴክሬታሪያት ካሮሊን ሌቪት፣ ፕሬዚዳንት ትራምፕ ስለ ቴሌፕሮምፕተር ኦፕሬተሩ ጉዳይ እንደሚያውቁ ተናግረዋል። በአሁኑ ሰዓት ሠራተኛው ያለ ክፍያ እረፍት እንዲወጣ መደረጉን የገለጹት ቃል አቀባይዋ፤ ከአሁን በኋላም በዋይት ሀውስ መሥራት እንደማይቀጥል አስታውቀዋል።

  7. በኡጋንዳ የተማሪዎች አውቶብስ ተገልብጦ ቢያንስ 20 ልጆች ሞቱ

    በትምህርታዊ ጉዞ ላይ የነበሩ ተማሪዎችን ጭኖ ሲጓዝ የነበረ አውቶብስ በምሥራቃዊ የአገሪቱ ክፍል ተገልብጧል

    የፎቶው ባለመብት, Uganda Police Force/X

    በኡጋንዳ በደረሰ የትራፊክ አደጋ ቢያንስ 20 ልጆች እና አንድ አዋቂ ሰው መሞታቸው ተገለጸ።

    በትምህርታዊ ጉዞ ላይ የነበሩ ተማሪዎችን ጭኖ የተጓዘው አውቶብስ በምሥራቃዊ የአገሪቱ ክፍል የተገለበጠ ሲሆን፤ በቅርብ ጊዜ ውስጥ ልጆች ላይ ከደረሱ የተሽከርካሪ አደጋዎች የከፋው ነው ተብሏል።

    የትምህርት ቤት ሠራተኞችን ጨምሮ ሌሎች በርካታ ሰዎችም በአደጋው ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    አደጋው የተከሰተው ትናንት ሐሙስ ማታ ካምቾርዋ በተባለ አካባቢ ነው።

    የመጀመሪያ ደረጃ የምርመራ ውጤት እንደሚያሳየው ለአደጋው መንስዔ አውቶብሱ የገጠመው የቴክኒክ ብልሽት ሲሆን፤ መኪናው ከአሽከርካሪው ቁጥጥር ውጭ ሆኗል።

    አደጋው የደረሰበት አካባቢ ከዚህ ቀደምም የትራፊክ አደጋዎች የተከሰቱበት እንደሆነ ተገልጿል።

    ፖሊስ ባወጣው መግለጫ “አሽከርካሪው መኪናውን መቆጣጠር እንዳልቻለ ሪፖርት ተደርጓል። መኪናው መንገድ ስቶ ከግዙፍ ድንጋይ ጋር ተጋጭቶም ተገልብጧል” ብሏል።

    የአካባቢው የመንግሥት ባለሥልጣን “በሚያሳዝን ሁኔታ 20 ልጆች እና አንድ አዋቂ ወደ ፈጣሪ ሄደዋል” በማለት በኤክስ ገጻቸው ሐዘናቸውን ገልጸዋል።

  8. ኢራን በኦማን፣ ኩዌት፣ ባሕሬን እና ሶሪያ ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን መምቷን አስታወቀች

    የኢራን ባንዲራን የያዙ ሰልፈኞች የቀድሞ ጠቅላይ መሪ አሊ ኻሜኒ ምስል ከሚታይበት ትልቅ ቢልቦርድ ስር ቆመው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ኦማን ውስጥ የሚገኝ የአሜሪካ የባሕር ኃይል መከታተያ ራዳር ሥፍራዎችን እንዲሁም ኩዌት እና ባሕሬን ውስጥ የሚገኙ ዒላማዎችን መምታቱን አስታወቀ። ሶርያ ውስጥ የሚገኝ የአሜሪካ የልዩ ዘመቻ ዕዝ ማዕከል ላይም ጥቃት መፈጸሙን ገልጿል።

    ኦማን ውስጥ በተፈጸመው ጥቃት “የባሕር ኃይል የቁጥጥር ራዳር እና የአሜሪካ አየር መቆጣጠሪያ ራዳር” መመታታቸውን ዘቡ ባወጣው መግለጫ ጠቅሷል።

    “በኃይል የሚፈጸሙ የአጸፋ ዘመቻዎች ይቀጥላሉ። የሆርሙዝ ወሽመጥም በአብዮታዊ ዘቡ ባሕር ኃይል ቁጥጥር ሥር እንደሆነ ቀጥሏል” ብሏል።

    የአሜሪካ የልዩ ዘመቻ ዕዝ ማዕከል ላይ ተፈጽሟል በተባለው የሶርያው ጥቃት፤ “የራዳር ሥርዓት፣ በርካታ የልዩ ሄሊኮፕተሮች እና በርከት ያሉ አሜሪካውያን ኃይሎች” ዒላማ መደረጋቸውን ጠቅሷል።

    እንደ አብዮታዊ ዘቡ ገለጻ፤ በዮርዳኖስ ድንበር አቅራቢያ በሚገኘው አል ታንፍ የተፈጸመው ድንገተኛ ጥቃት፤ ከሁለት ቀናት በፊት በኢራናውያን ወታደሮች ላይ ለተፈጸመው ግድያ የአጸፋ እርምጃ ነው።

    ሶርያም ሆኑ አሜሪካ እስካሁን ተፈጸመ ስለተባለው ጥቃት አስተያየት አልሰጡም።

    የዮርዳኖስ ጦር ግን ወደ አገሪቱ የተወነጨፉ ሦስት የኢራን ሚሳዔሎችን ጉዳት ወይም ውድመት ሳይደርስ መትቶ መጣሉን አስታውቋል።

    ኢራን አብዮታዊ ዘብ አዲሱን ጥቃት ከመፈጸሙ አስቀድሞ አሜሪካ “በርካታ የኢራን ጦር ዒላማዎችን” መምታቷን ገልጻለች።

    ኢራን በበኩሏ ድልድዮች፣ ባቡር ጣቢያ እና የአየር ማረፊያን ጨምሮ በተለያዩ የሲቪል መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት እንደተፈጸመባት አስታውቃለች።

    ሁለቱም አገራት የሚፈጽሟቸው ጥቃቶች እየተባባሱ ባሉበት በዚህ ወቅት፤ ወሳኙ የባሕር መተላለፊያ ሆርሙዝ ወሽመጥ በኢራን እንደተዘጋ ነው።

  9. አሜሪካ ለስድስተኛ ተከታታይ ምሽት በከፈተችው ጥቃት የኢራን የሲቪል መሠረተ ልማቶች መደብደባቸው ተገለጸ

    ጥቃት ደረሰበት ኢራን ድልድይ

    የፎቶው ባለመብት, irib

    የምስሉ መግለጫ, ቢቢሲ በሆርሞዝጋን ግዛት ድልድይ መመታቱን አረጋግጧል

    አሜሪካ እና ኢራን ሆርሙዝ ወሽመጥን ለመቆጣጠር የሚደርጉት ውጊያ ቀጥሎ፤ የዋሽንተግን ጦር ለስድስተኛ ተከታታይ ምሽት በኢራን አዲስ ዙር ጥቃት ፈጸመ።

    ሐሙስ ሌሊት የደረሱት ጥቃቶች በድጋሚ ያገረሸው የሁለቱ አገራት ግጭት እየተባባሰ መሆኑን የሚያመለክቱ ናቸው።

    አሜሪካ የኢራን ድልድዮች፣ ባቡር ጣቢያ እና የአየር ማረፊያን ጨምሮ በተለያዩ የሲቪል መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት መፈጸሟን የቴህራን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል። በሆርሞዝጋን ግዛት ከባንደር አባስ በምዕራብ አቅጣጫ የሚገኝ አንድ ድልድይ መመታቱን ቢቢሲ አረጋግጧል።

    ቢቢሲ ስለ ጥቃቱ ለዋይት ሀውስ እና ለአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) ጥያቄ አቅርቧል።

    በተጨማሪም የአሜሪካ ሚሳዔሎች በሆርሙዝ አቅራቢያ የሚገኘውን ቃሽም ደሴት እንዲሁም የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ጣቢያ መገኛ የሆነው ቡሼህርን መትተዋል። የወደብ ከተማው ባንዳር አባስም የሚሳዔል ዒላማ ሆኗል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ የተፈጸሙት ጥቃቶች "የኢራንን ወታደራዊ አቅም ይበልጥ ለማዳከም" ያለሙ እንደሆኑ ገልጿል። በተጨማሪም አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የጣለችውን እገዳ ሊጥስ የነበረ አንድ መርከብን መቆጣጠሩን አስታውቋል።

    ሴንትኮም በዚህ ዙር ጥቃት የተደበደቡ በሚል በዘረዘራቸው “በርካታ የኢራን ጦር ዒላማዎች” ውስጥ ድልድዮችን አልጠቀሰም።

    በዚህ ጥቃት የተሳተፉት የአሜሪካ የጦር አውሮፕላኖች፣ ድሮኖች እና የጦር መርከቦች የኢራንን "የባሕር ዳርቻ መከታተያ እና የአየር መከላከያ ጣቢያዎችን፣ ወታደራዊ የሎጂስቲክስ መሠረተ ልማት እና የባሕር ኃይል አቅሞችን" መምታታቸውን ገልጿል።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ ቴህራን ወደ ድርድር የማትመለስ ከሆነ በአገሪቱ ውስጥ የሚገኙ ድልድዮች እና የኃይል ማመንጫዎችን እንደሚመቱ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ዝተው ነበር።

    ፕሬዝዳንቱ ባለፈው ሚያዝያ ላይም ድልድዮች እና የኃይል ማመንጫዎችን ጨምሮ የኢራን የሲቪል መሠረተ ልማቶች እንደሚደበድቡ መናገራቸው ይታወሳል።

    በወቅቱም የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር ቮልከር ቱርክ፤ "ሆነ ብሎ ሲቪሎች እና የሲቪል መሠረተ ልማቶችን ማጥቃት የጦር ወንጀል" እንደሆነ መገናራቸው ይታወሳል።

    በ1949 የወጣው እና በጦርነት ወቅት የሚከበሩ ሰብአዊ ሥነ ምግባሮችን የሚዘረዝረው የጄኔቫ ስምምነት፤ ለሲቪሎች አስፈላጊ እንደሆኑ በሚታሰቡ ሥፍራዎች ላይ ጥቃት መፈጸምን ይከለክላል።

  10. የየመን ሁቲዎች የሳዑዲ አረቢያን የነዳጅ ማምረቻ ተቋማት እንደሚያጠቁ አስጠነቀቁ

    በሰነዓ አውሮፕላን ማረፊያ ላይ ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ የታየ ጭስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በሰነዓ አውሮፕላን ማረፊያ ላይ ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ የታየ ጭስ

    ሁቲዎች ከሳዑዲ አረቢያ ጋር የሚያካሂዱት ግጭት የሚባባስ ከሆነ የሳዑዲን የነዳጅ ተቋማት እና ሌሎች ወሳኝ ተቋማት ዒላማ እንደሚያደርጉ አስጠነቀቁ።

    የሁቲ ታጣቂ ቡድን መሪ የሆነው አብዱል-ማሊክ ሁቲ እንደተናገረው "ሳዑዲ አረቢያ በአገራችን ላይ መጠነ ሰፊ ጥቃት በመክፈት ግጭቱን የምታባብስ ከሆነ፣ ሁሉም የነዳጅ ማምረቻ ተቋማቷ እና ወሳኝ ማዕከላቷ የሚሳዔሎቻችን እና የድሮኖቻችን ዒላማ ይሆናሉ” በማለት አስጠንቅቋል።

    ሰኞ ዕለት ሳዑዲ በሰነዓ አውሮፕላን ማረፊያ ላይ ጥቃት ፈጽማለች በማለት ሁቲዎች የከሰሱ ሲሆን በምላሹም በሳዑዲ ውስጥ የሚገኝን ዒላማ ማድረጋቸውን አሳውቀዋል። በሁለቱ ወገኖች መካከል አሁን እየተካሄደ ያለው የተኩስ ልውውጥ በአውሮፓውያኑ 2022 ከተደረሰው ተኩስ አቁም ወዲህ በመካከላቸው ያለው ውጥረት መባባሱን ያሳያል።

    ሳዑዲ ተጨማሪ ጥቃት በሰነዓ ላይ የምትፈጽም ከሆነ ሪያድ የሚገኘው አውሮፕላን ማረፊያዋ ዒላማ እንደሚሆን የሁቲ ታጣቂ ቡድን መሪ ማስጠንቀቁን ኤኤፍፒ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    በሳዑዲ የሚደገፈው እና ኤደን ከተማ ውስጥ መቀመጫውን ያደረገው የየመን መንግሥት በሰነዓ ላይ የተፈጸመው ጥቃት የሁቲዎች አጋር የሆነችው የኢራን አውሮፕላን እንዳያርፍ ለማድረግ ነው ብሏል።

    ወደ የመን የአየር ክልል የሚገቡ አውሮፕላኖች የቅድሚያ ፈቃድ በሳዑዲ ከሚመራው የአካባቢው አገራት ጥምረት ማግኘት እንዳለበት የሚያስገድደው አሠራር ከአስር ዓመታት በላይ በሥራ ላይ ቆይቷል።

    የየመን መንግሥት እና ደጋፊዎቹ እንደሚሉት ይህንን የበረራ ፍቃድ ሁቲዎች እና ኢራን ከግዛቷ ቀጥታ በረራ በማድረግ ጥሰት እየፈጸሙ ናቸው ሲሉ ይከስሳሉ።

    ማክሰኞ ዕለት ሁቲዎች በሳዑዲ የሚመራው ጥምረት ያሰማራው የቅኝት ድሮንን መትተው መታላቸውን አሳውቀዋል።

  11. አሜሪካ የኃይል ተቋማቷን ካጠቃች ሁቲዎች የቀይ ባሕር የነዳጅ መተላለፊያን ለመዝጋት እንዲዘጋጁ ኢራን ማሳሰቧ ተዘገበ

    የሁቲ አማጺያን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ የኢራን የኃይል ማመንጫ መሠረተ ልማቶች ላይ ጥቃት የምትሰነዝር ከሆነ፤ የየመን ሁቲ አማጺያን በቀይ ባሕር የሚገኙ የነዳጅ መተላለፊያን ለመዝጋት እንዲዘጋጁ ቴህራን ማሳሰቧን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘገበ።

    የኢራን አመራሮች በጉዳዩ ላይ እንደተወያዩ እና በየመን አጋሮቻቸው ለሆኑት ሁቲዎች መልዕክቱ እንደተላለፈ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ሁለት ከፍተኛ የቴህራን ባለሥልጣናት ተናግረዋል።

    የሮይተርስ ዘገባ እንደሚጠቁመው ጉዳዩ ስሱ ከመሆኑ የተነሳ ባለሥልጣናቱ ማንነታቸው እንዲገለጽ አልፈቀዱም።

    ከዚህ ቀደም ስለ ጉዳዩ ምንም ያልተሰማ ሲሆን የሁቲ አማጺያንም በቅርቡ መልዕክቱ እንደደረሳቸው ተጠቁሟል።

    መልዕክቱ በምን መንገድ እንደተላለፈ እንዲሁም መልዕክቱ የተላለፈው ማክሰኞ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራንን የኃይል አቅርቦች መሠረተ ልማቶች ለመምታት ከዛቱ በኋላ ስለመሆኑ የሮይተርስ ምንጮች ማብራሪያ አልሰጡም።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እና የሁቲ ቃል አቀባይ በጉዳዩ ላይ ከሮይተርስ አስተያየት እንዲሰጡ ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ አልሰጡም።

  12. በአልጄሪያ በሕጻናት ማሳደጊያ ላይ በተነሳ እሳት ቢያንስ 11 ሰዎች ሞቱ

    የእሳት አደጋ ሠራተኞች ቃጠሎውን ለማጥፋት ጥረት ሲያደርጉ

    የፎቶው ባለመብት, Algeria's General Directorate for Civil Protection

    የምስሉ መግለጫ, የእሳት አደጋ ሠራተኞች ቃጠሎውን ለማጥፋት ጥረት ሲያደርጉ

    በሰሜን አፍሪካዊቷ አገር አልጄሪያ ውስጥ በሚገኝ ወላጆቻቸውን ያጡ ማሳደጊያ ላይ በተከሰተ የእሳት አደጋ ቢያንስ 11 ሰዎች ሕይወታቸው ሲያልፍ ሌሎች 19 ደግሞ ጉዳት ደረሰባቸው።

    በዋና ከተማዋ አልጀርስ ዳርቻ ላይ በምትገኘው ሚሐመድያ ተብላ በምትጠራ አካባቢ ባለው የእጓለሙታን ማዕከል ውስጥ የተነሳውን እሳት ለመቆጣጠር የእሳት አደጋ እና የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ጥረት እያደረጉ መሆናቸው ተዘግቧል።

    ባለ ሁለት ፎቅ በሆነው ሕንጻ ላይ ረቡዕ ሌሊት በተከሰተው የእሳት ቃጠሎ ጉዳት የደረሰባቸው ሕጻናት ማንነት እና ዕድሜ ይፋ አልተደረገም።

    በማሳደጊያው ውስጥ የነበሩ የአካል ጉዳት የነበረባቸው አምስት ሕጻናትን ማትረፍ መቻሉን የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች የገለጹ ሲሆን፣ የእሳቱ ምክንያት ምን እንደሆነ አልታወቀም።

    አደጋውን ተከትሎ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሲፊ ጋሪብ ጉዳት የደረሰባቸውን ሆስፒታል ተገኝተው ጎብኝተዋል።

    በአልጄሪያ በአሁኑ ጊዜ ከፍተኛ ሙቀት የተከሰተ ሲሆን በአገሪቱ ሰሜናዊ ክፍል ውስጥ በርካታ ሰደድ እሳቶች እንዲከሰቱ ምክንያት ሆኗል።

  13. የአርጀንቲናውያን የዓለም ዋንጫ ፖለቲካዊ መልዕክት እና የሚጠበቀው የፊፋ ቅጣት

    የአርጀንቲና ተጫዋቾች ያሳዩት ምልዕክት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አርጀንቲና ተጫዋቾቿ የእንግሊዝን ብሔራዊ ቡድንን በዓለም ዋንጫ የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታ ካሸነፉ በኋላ፤ አገራቸው በፎክላንድ ደሴቶች ላይ ያላትን የይገባኛል ጥያቄ የሚደግፍ ጽሁፍ አሳይተዋል። ይህ ድርጊታቸው ከፊፋ የሥነ ምግባር ጥሰት ቅጣት እንደሚያስወስድ እየተጠበቀ ነው።

    የአርጀንቲና ቡድን አትላንታ ውስጥ በተካሄደው ጨዋታ እንግሊዝን 2 ለ 1 በሆነ ውጤት ያሸነፈ ሲሆን እሁድ በሚደረገው የፍፃሜ ጨዋታ ከስፔን ጋር ይገጥማል።

    የጨዋታው የመጨረሻ ፊሽካ ከተሰማ በኋላ የአርጀንቲና ተጫዋቾች 'ላስ ማልቪናስ' በሚል በማለት የሚጠሯቸው ደሴቶች የአገራቸው ግዛት መሆናቸውን የሚገልጽ ባነር ይዘው ታይተዋል።

    ደስታቸውን ሲገልጹ የያዙት ባነር "ፎልክላንድ ደሴቶች የአርጀንቲና ናቸው" የሚል ነው።

    የፎልክላንድ ደሴቶች፣ በደቡብ ምዕራብ አትላንቲክ ውቅያኖስ ላይ የሚገኙ የእንግሊዝ የባሕር ማዶ ግዛት አካል ሲሆኑ፣ በብሪታንያ እና በአርጀንቲና መካከል የሉዓላዊነት ይገባኛል ውዝግብ ርዕሰ ጉዳይ ሆነው ቀጥለዋል።

    ሁለቱ አገራት ከአውሮፓውያኑ ሚያዝያ እስከ ሰኔ 1982 ድረስ በአርጀንቲና ምሥራቃዊ የባሕር ዳርቻ 300 ማይል ርቀት በሚገኙት ደሴቶች ላይ ጦርነት አካሂደው ነበር።

    ለ74 ቀናት በዘለቀው ጦርነት 655 የአርጀንቲና ወታደሮች እና 255 የእንግሊዝ ወታደሮችን ሲሞቱ ከደሴቶቹ የመጡ ሦስት ሰዎችም በጦርነቱ ተገድለዋል።

    በአውሮፓውያኑ 2014 የአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን ከስሎቬንያ ጋር ባደረገው የወዳጅነት ጨዋታ ተጫዋቾቹ ተመሳሳይ መልዕክት የያዘ ባነር በማሳየታቸው ፊፋ በአገሪቱ እግር ኳስ ማኅበር ላይ የ20 ሺህ ፓውንድ ቅጣት ጥሎበት ነበር።

    የዓለም እግር ኳስ የበላይ አስተዳዳሪ አካል የሆነው ፊፋ ይህ የአርጀንቲና ቡድን ድርጊት የተቋሙን የሚጥስ ነው ስላለ፤ ክስተቱን መርምሮ ቅጣት እንደሚያስተላለፍ እየተጠበቀ ነው።

  14. ኢራን በባሕረ ሰላጤው የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን አጠቃች

    የኢራን ጦር

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ኢራን በከፈተችው አዲስ ዙር ጥቃት በጎረቤቶቿ የባሕረ ሰላጤው አገራት ውስጥ የሚገኙ አሜሪካ የጦር ሠፈሮችን መታች።

    ዮርዳኖስ፣ ኩዌት እና ባሕሬንን ጨምሮ በቀጣናው የሚገኙ ዒላማዎች ጥቃት እንደተፈጸመቸባው ኢራን ገልጻለች። የኢራን ጦር ሌሊት ላይ በፈጸመው ጥቃት ዮርዳኖስ ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ሠራዊት “የግንኙነት ሥርዓቶች እና የነዳጅ ማጠራቀሚያዎችን” መምታቱን እንዳስታወቀ ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ዮርዳኖስ ውስጥ ዒላማ ከተደረጉት ስፍራዎች አንዱ ‘አል አዝራቅ’ ጦር ሠፈር እንደሆነ የገለጸው ጦሩ፤ ቦታው “ፀረ ሚሳዔል መከላከያ ሥርዓት የሚገኝበት” እንደሆነ ጠቅሷል።

    ኩዌት ውስጥ በሚገኘው አሊ ሳሌም የጦር ሠፈር ደግሞ “የቅድመ ማስጠንቂያ ራዳር ሥርዓት” ዒላማ መደረጉን የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ገልጿል።

    አብዮታዊ ዘቡ እንደሚናገረው “የአሜሪካ ወታደሮች ኩዌት ውስጥ የሚሰበሰቡበት” ስፍራ ላይም ጥቃት ደርሷል። ጥቃቱ የተፈጸመው “ሚሳዔል እና ድሮን” በመጠቀም እንደሆነ አስታውቋል።

    በተመሳሳይ አሜሪካ ረቡዕ ሌሊት በመላው ኢራን በርካታ ስፍራዎች ላይ ጥቃት ፈጽማለች። ለስድስት ሰዓታት ቆየው ጥቃት ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ “ንጹኃን ባሕርተኞችን ስጋት ላይ ለመጣል ያላትን አቅም ያዳከመ” እንደሆነ የአሜሪካ ጦር ገልጿል።

  15. አሜሪካ ለሳዑዲ አረቢያ እና ለኩዌት መሣሪያ እንዲሸጥ ፈቀደች

    የጦር አውሮፕላን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የጦር አውሮፕላን ምሥል ( ከክምችት)

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የሳዑዲ አረቢያን የአየር መከላከያ ሥርዓት ለማጠናከር የ1.96 ቢሊዮን ዶላር የጦር መሣሪያዎች ሽያጭ መፍቀዱን ገለጸ።

    ውሳኔው የተላለፈው በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው ግጭት ተባብሶ በቀጠለበት ወቅት ነው።

    ሚኒስቴሩ ባወጣው መግለጫው የጦር መሣሪያ ሽያጩ፣ “የኔቶ አባል ያልሆነችውን ቁልፍ አጋር ፀጥታ በማጠናከር የአሜሪካን የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ እና ብሔራዊ የደኅንነት ዓላማዎችን ይደግፋል" ብሏል።

    ሳዑዲ አረቢያ በፋርስ ባሕረ ሰላጤ ቀጣና ላለው ፖለቲካዊ እና ኢኮኖሚያዊ መረጋጋት ወሳኝ ሚና እንደምትጫወትም መግለጫው ጠቅሷል።

    መግለጫው ጨምሮም ለሳዑዲ አረቢያ የቀረበው ስምምነት፣ ለአየር በአየር እና ከአየር ወደ ምድር ለሚደረጉ ዘመቻዎች የሚውሉ ዘመናዊ የጦር መሣሪያ ሥርዓትን ጨምሮ ተኳሽ፣ ተተኳሽ እና ሌሎች መለዋወጫዎች ፣ ሥልጠና እና የሎጂስቲክ ድጋፍን ያካትታል።

    የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤቱ ለኩዌት ለጦር አውሮፕላኖች ቴክኒካዊ ድጋፍ የሚውል የ484 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍም አፅድቋል።

    ከኩዌት ጋር የተደረሰው የመሣሪያ ሽያጭ ስምምነት ቴክኒካዊ ድጋፍ እና ለሲ- 17 አውሮፕላን የሚውሉ መለዋወጫዎችን፣ የጥገና አገልግሎት፣ ሶፍትዌር፣ ሥልጠና እና ሎጂስቲክስ አገልግሎቶችን ያካትታል።

    የመሣሪያ ሽያጩ ምክር ቤቱ ከገመገመው በኋላ ተግባራዊ እንደሚሆንም መስሪያ ቤቱ ገልጿል።

  16. በናይጄሪያ ፕሬዚደንት ቢሮ ውስጥ የተከፈተው "ሐሰተኛ ተቋም" ኃላፊ በቁጥጥር ሥር ዋለ

    አዴኒይ አዴየሚ ማቲው

    የፎቶው ባለመብት, @princeadeyemi_adeniyi/instagram

    የምስሉ መግለጫ, አዴኒይ አዴየሚ ማቲው ከመያዙ በፊት ለሳምንታት ተሰውሮ ቆይቷል

    በናይጄሪያው ፕሬዚደንት ቢሮ ውስጥ እንደተቋቋመ የተገለፀው ሐሰተኛ ተቋም ኃላፊ ለሳምንታት ሲፈለግ ከቆየ በኋላ በቁጥጥር ሥር ዋለ።

    አዴኒይ አዴይሚ ማቲው የተባለው ግለሰብ 'ፕሬዚደንሻል ፌሪን ኢንቨስትመንት ፕሮሞሽን' በሚል ለመሰረተው ተቋም ዋና ዳይሬክተር እንደሆነ ይገልጻል።

    ፕሬዚደንቱ እና ቢሯቸው ግን ስለተቋሙም ሆነ ስለዳይሬክተሩ ሹመት የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ተናግረዋል።

    ይህንንም ተከትሎ በ950 ሺህ ዶላር በተመሰረተው ሐሰተኛ ተቋም ላይ የሙስና ምርመራ እንዲደረግ አዝዘዋል።

    ግለሰቡ መጀመሪያ ላይ ጥፋተኛ አለመሆኑን ለአገሪቷ መገናኛ ብዙኃን የተናገረ ሲሆን የቀረበበትን ሐሰተኛ እና የማስመሰል ክሶች ቀርቦ በመከላከል ስሙን እንደሚያድስ ገልጾ ነበር።

    ሆኖም ይህንን ማድረግ ባለመቻሉ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የእስር ማዘዣ አውጥቶበታል።

    ማቲው ለሳምንታት ተሰውሮ ከቆየ በኋላ በደቡብ ምዕራቧ ኦሱን ግዛት በቁጥጥር ሥር ውሏል።

    ጉዳዩ ፕሬዚደን ቦላ ቲኑቡ ባለፈው ሳምንት በማያውቁት ተቋም ላይ የሙስና ምርመራ እንዲደረግ ካዘዙ በኋላ በናይጄሪያ መነጋገሪያ ሆኗል።

    የፕሬዚደንቱ ቢሮ፣ የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ ፊርማ ያለበት እና ግለሰቡ ራሱን የሾመበት ደብዳቤ ሐሰተኛ መሆኑን አረጋግጧል።

    የፍርድ ቤቱ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳውም አደይሚ እና ሌሎች ሁለት ግለሰቦች ምክር ቤቱን ለማቋቋም ሐሰተኛ ሰነድ በማዘጋጀት፣ በርካታ የባንክ አካውንቶችን በተቋሙ ስም በመክፈት እና መሬት ላይ ለሌለ ተቋም ሕጋዊ እውቅና በመፈለግ ተከስሰዋል።

  17. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኢራን “ባህሪዋን እንድታስተካክል” ካስጠነቀቁ በኋላ የአሜሪካ ጦር አዲስ ጥቃት ከፈተ

    የኢራን ባንዲራን የያዘች ታዳጊ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ረቡዕ ዕለት ኢራን “ባህሪዋን እንድታስተካክል” ካስጠነቀቁ በኋላ፤ የአሜሪካ ጦር በአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች አዲስ ጥቃት ከፈተ።

    የአሜሪካ ጦር ባወጣው መግለጫ፤ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያልፉ መርከቦች ጉዞን አደጋ ላይ ለመጣል ጥቅም ላይ የዋሉ "የኢራን ወታደራዊ አቅሞች" ዒላማ መደረጋቸውን አስታውቋል።

    ለ90 ደቂቃ በቆየው አዲስ ዙር ጥቃት በታላቁ ቱንብ ደሴት የሚገኙ የኢራን የባሕር ዳርቻ መከላከያዎች እንዲሁም የክሩዝ ሚሳዔል ማከማቻ እና ማስወንጨፊያ ጣቢያዎች መመታታቸውን ገልጿል።

    የአራን “የዕዝ ማዕከላት፣ የፀረ-አውሮፕላን መከላከያ ሥርዓቶች፣ የሚሳኤልና የድሮን አቅሞች እንዲሁም የባሕር ዳርቻ መከታተያ ተቋማት" ጥቃት ከደረሰባቸው የመከላከያ አቅም መካከል ተጠቅሰዋል። በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የምትገኘው የባንደር አባስ ከተማም ዒላማ እንደሆነች ተነግሯል።

    እነደ ጦሩ ገለጻ፤ አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረግ ጉዞ ላይ የጣለችውን እግድ በመጣስ ለማለፍ የሞከረ አንድ መርከብ ላይ ተተኩሷል።

    ዋሽንግተን ይህንን ጥቃት ያደረሰችው ኢራን ባሕሬን እና ኩዌት ውስጥ ያሉትን ጨምሮ በቀጣናው የሚገኙ የአሜሪካ ወታደራዊ ዒላማዎችን መምታቷን ከገለፀች በኋላ ነው።

    ለአምስተኛ ቀን የቀጠለው አዲስ ዙር የጥቃት ምልልስ አገራቱ ጦርነቱን ለመቋጨት ገብተውት የነበረውን የመጀመሪያ ደረጃ ስምምነት አደጋ ላይ ጥሎታል።

    የኢራን ዋና ተደራዳሪ እና የፓርላማ አፈ ጉባኤ መሀማድ ባገር ጋሊባፍ አገራቸው ከስምምነቱ የማትጠቀም ከሆነ ለውሉ የምትገዛበት “ምንም ምክንያት” እንደሌላት ለመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኢራን እስከሚቀጥለው ሳምንት ድረስ ወደ ንግግር የማትመለስ ከሆነ ድልድዮችን እና የኃይል ማመንጫዎችን እንደሚመቱ ማክሰኞ ዕለት ዝተው ነበር።

    ረቡዕ ዕለት ከጋዜጠኞች ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ ይህንን ከማድረጋቸው በፊት ቀነ ገደብ ይሰጡ እንደሆነ ተጠይቀዋል። “ቀነ ገደብ ማስቀመጥ አልወድም፤ ነገር ግን እነሱ በደንብ ያውቃሉ፣ ታሪኩን ያውቁታል . . . ባህሪያቸውን ቢያስተካክሉ ይሻላቸዋል" ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

    በኋላ ላይ ደግሞ አሁን ኢራን "ደስተኛ አይደለችም" ሲሉ በመከላከያ ጉባኤ ላይ ለተገኙት ልዑካን ተናግረዋል።

    “ለመስማማት እጅጉን ይፈልጋሉ። እያደረግን ያለነውን ነገር አልወደዱትም” ብለዋል። “የምንፈልገው ከእነርሱ ጋር መስማማት ነው ወይስ የጀመርነውን እናጠናቅቅ የሚለውን እንመለከታለን” ሲሉም ተደምጠዋል።

    የኢራኑ ዋና ተደራዳሪ ጋሊባፍ በበኩላቸው፤ የአገራቸው ብሔራዊ ደኅንነት የተመሠረተው በሆርሙዝ ወሽመጥ ያለውን “የኢራን አሰራር” በማስቀጠል ላይ እንደሆነ ገልጸዋል።

    ከአሜሪካ ጋር “የኅልውና” ግጭት ውስጥ ያለችው ኢራን ድርድርን የምትመለከተው ከጦርነት ጎን ለጎን እንዳለ የትግል ስትራቴጂ እንደሆነም አክለዋል።

  18. አሜሪካ አዳዲስ ጥቃቶችን ስትፈጽም ኢራን በበኩሏ ተጨማሪ የንግድ መስመሮችን እንደምትዘጋ አስጠነቀቀች

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን የአገሪቱ ጦር በአሜሪካ የጦር ሠፈሮች ላይ ጥቃት መፈጸሙን ዘግበዋል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን መገናኛ ብዙኃን የአገሪቱ ጦር በአሜሪካ የጦር ሠፈሮች ላይ ጥቃት መፈጸሙን ዘግበዋል

    አሜሪካ በወታደራዊ ዒላማዎች ላይ ተጨማሪ ድብደባዎችን ስትፈጽም ኢራን በቀጣናው የሚገኙ ተጨማሪ የንግድ መስመሮችን እንደምትዘጋ አስጠነቀቀች።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ አሜሪካ “ጠብ አጫሪነቷን” እስክታቆም ድረስ የሆርሙዝ ወሽመጥ ዝግ ሆኖ እንደሚቆይ ተናግሯል።

    አክሎም በቀጣናው የሚገኙ ተጨማሪ የነዳጅ እና ጋዝ መላኪያ መስመሮችን እንደሚዘጋ አስጠንቅቋል።

    ማስጠንቀቂያው የተሰማው የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንቲኮም) ሌሊቱን ካካሄደው የሰባት ሰዓት ድብደባ ተከትሎ የድሮን፣ የአየር እና የባሕር ጥቃቶችን መፈጸሙ ካስታወቀ በኋላ ነው።

    ከቅርብ ቀናት ወዲህ በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተቀሰቀሰው አዲስ ጦርነት ለዓለም ምጣኔ ሃብት ወሳኝ የሆነውን የባህር ወሽመጥ እንቅስቃሴ አልባ አድርጎታል።

    ይህ ጥቃት ወሳኝ የነዳጅ መተላላፊያ በሆነው የሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ መርከቦች መንቀሳቀስ ባለመቻላቸው የነዳጅ ዋጋ ዳግም እንዲጨምር አድርጓል።

    የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ ረቡዕ ማለዳ የተፈጸሙ ጥቃቶች “የኢራን ጦር በንግድ መርከቦች ላይ ተጨማሪ ጥቃት መፈጸም እንዳይችል በማድረግ አቅሙን ያዳከሙ ናቸው” ሲል አስታውቋል።

    የሴንቲኮም ባለሥልጣናት አክለውም ለ90 ደቂቃ ያህል የኢራን የባሕር ዳርቻ መከላከያዎች እና ክሩዝ ሚሳዔል ማከማቻ ላይ ድብደባ ተፈጽሟል ብለዋል።

    ማክሰኞ ዕለት የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ወደ ድርድር የማትመለስ ከሆነ በሚቀጥለው ሳምንት ድልድዮቿን እና የኃይል ማመንጫዎቿን እንደሚደበድቡ ዝተው ነበር።

  19. ከ300 በላይ ናይጄሪያውያን ከደቡብ አፍሪካ ወደ አገራቸው ተመለሱ

    ናይጄሪያ በቅርብ ወራት በተደረጉ ተቃውሞች ምክንያት ደቡብ አፍሪካን ለቅቀው ለተመለሱ ዜጎቿ ካሳ ልትጠይቅ መሆኑን አስታውቃለች።

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ናይጄሪያ በቅርብ ወራት በተደረጉ ተቃውሞች ምክንያት ደቡብ አፍሪካን ለቅቀው ለተመለሱ ዜጎቿ ካሳ ልትጠይቅ መሆኑን አስታውቃለች

    ናይጄሪያ ስድስተኛው እና የመጨረሻ ነው ባለችው ጉዞ ወደ አገራቸው ለመመለስ ፈቃደኛ የሆኑ 306 ሰዎችን ወደ አገራቸው መመለሷን አስታወቀች።

    ተመላሾቹ ዛሬ ረፋድ ላይ በሌጎስ በሚገኘው ሙርታላ ሙሐመድ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ደርሰዋል።

    በደቡብ አፍሪካ መጤ ጠል ዘመቻ ዳግም ካገረሸ በኋላ ወደ አገራቸው በፈቃደኝነት የተመለሱት ናይጄሪያውያን ቁጥር ከ1200 በላይ መሆኑ ተገልጿል።

    በደቡብ አፍሪካ በዚህ ዓመት አጋማሽ ላይ የተጀመረው መጤ ጠል እንቅስቃሴ በብዛት ሰላማዊ የነበረ ቢሆንም፤ ነገር ግን በአንዳንድ አካባቢዎች ብጥብጥ፣ ማስፈራራት እና የሕይወት መጥፋት ተከስቷል።

    የደቡብ አፍሪካ ፖሊስ በተፈጠሩ ክስተቶች ዙሪያ ምርመራ እያደረገ መሆኑን አስታውቋል።

    የናይጄሪያ መንግሥት ንግዳቸውን፣ ቤታቸውን እና ያላቸውን ንብረት ትተው ከደቡብ አፍሪካ እንዲወጡ ለተደረጉ ዜጎቹ ካሳ እንደሚጠይቅ አስታውቋል።

    የደቡብ አፍሪካ ባለሥልጣናት በበኩላቸው ምንም ዓይነት ካሳ እንደማይከፍሉ ተናግረዋል።

    በናይጄሪያ ምክር ቤት የዲያስፖራ ጉዳዮች ኮሚቴ በደቡብ አፍሪካ በሚገኙ ስደተኛ ዜጎቹ ላይ የደረሰውን እና ከአገር መውጣታቸውን ተከትሎ የሁለቱ አገራት ግንኙነትን እያጤነው መሆኑን አስታውቋል።

    የደቡብ አፍሪካ መንግሥት ከአምስት ሳምንታት በፊት "የስደተኞች አስተዳደር" ላይ ዘመቻ ከከፈተ በኋላ ከ53,000 በላይ የውጭ ዜጎች ከአገር መባረራቸውን ወይንም እንዲወጡ መደረጋቸውን አስታወቀ።

    እነዚህ ስደተኞች ከማላዊ፣ ከዚምባብዌ እና ከሞዛምቢክ የመጡ መሆናቸውን የገለጹት ባለሥልጣናቱ፤ ቁጥሩ ከዚህም በላይ ሊጨምር ይችላል ብለዋል።

    በደቡብ አፍሪካ ለተከታታይ ሳምንታት ፀረ ስደተኛ ሰልፎች ከተካሄዱ እንዲሁም አለመረጋጋት፣ ማስፈራራት እና ዘረፋ ከተፈጸመ በኋላ በአገሪቱ ያለ ሕጋዊ የመኖሪያ እና የሥራ ፈቃድ የሚገኙ ስደተኞች ላይ ሰፊ የተባለ ዘመቻ እያካሄደች ትገኛለች።

  20. አሜሪካ በኢራን ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት ስታስፋፋ፣ ኢራን ምላሿ የበለጠ የከፋ እንደሚሆን አስታወቀች

    የአሜሪካ የጦር መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአሜሪካ ጦር ሠራዊት ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) ዛሬ ረቡዕ ከሰዓት በኋላ በኢራን ላይ ከፍተኛ ተከታታይ ጥቃት መፈጸሙን ሲያስታውቅ፣ ኢራን የአጸፋ ምላሿ ዒላማ የሚሆኑ ተቋማትን መጠን እንደምትጨምር ገለጸች።

    በአገሪቱ የሰዓት አቆጣጠር ሰባት ሰዓት ተኩል ላይ አሜሪካ የፈጸመችው ጥቃት ኢራን በሆርሙዝ ወሽወመጥ በኩል በሚያልፉ መርከቦች ላይ ጥቃት እንዳትፈጽም ለማድረግ ያለመ መሆኑን ተገልጿል።

    ማዕከላዊ ዕዙ በኤክስ ገጹ ላይ ባሠራጨው መረጃ "እነዚህ ጥቃቶች የኢራን ኃይሎች በሆርሙዝ ወሽመጥ በጭነት መርከቦች ላይ ጥቃት የሚፈጽሙበትን ወታደራዊ አቅም የበለጠ ለማዳከም” የተፈጸሙ መሆናቸውን አስታውቋል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ አሜሪካ በኢራን ላይ ማካሄድ የቀጠለችው ጥቃት ኢራን በአጸፋ ጥቃት ዒላማ የምታደርጋቸውን ተቋማት እንድታሰፋ ሊያደርጋት እንደሚችል አስጠንቅቋል።

    በዚህም በአካባቢው የሚገኙ የአሜሪካ አጋር የሆኑ አገራት የነዳጅ እና የጋዝ ምርቶች ማውጫዎች፣ ማጣሪያዎች እና መተላለፊያዎች ዒላማ ሊሆኑ እንደሚችሉ ገልጿል።

    አሜሪካ በኢራን ላይ ባለፉት ቀናት ተከታታይ ጥቃቶችን እየፈጸመች ሲሆን፣ ኢራንም በምላሹ በዮርዳኖስ፣ በባህሬን፣ በኩዌት እና በአረብ ኤምሬትስ ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ የጦር ሰፈሮች ላይ ጥቃት እያደረሰች ነው።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተደረሰው የተኩስ አቁም ካበቃ በኋላ በቀጠለው ጥቃት በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ መርከቦች የጥቃት ዒላማ እየሆኑ ነው።

    አሜሪካ የኢራንን ጥቃት ለመከላከል በሆርሙዝ ላይ ጥበቃ እያካሄደች መሆኗን እና ወደ ኢራን የሚያቀኑ እና ከኢራን የሚነሱ ሁሉም መርከቦች በመተላለፊያው በኩል እንዳያቋርጡ ዕገዳ ጥላለች።