ባቡር ላይ የተወለደችው ህጻን ለ25 ዓመታት ነጻ የባቡር ትኬት ተሰጣት

የእናቱን እጅ የያዘ ህጻን

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

በአየር ላንድ ባቡር ውስጥ የተወለደችው ጨቅላ ለ25 ዓመታት በባቡር በነጻ ለመጓዝ የሚያችል ስጦታ ተበርክቶላታል።

ከጋልዌይ ወደ አየር ላንድ መዲና ደብሊን ይጓዝ በነበረው ባቡር ላይ ተሳፍራ የነበረችው ነብሰ ጡር እናት ድንገት ምጥ ይዟት ባቡሩ ላይ ሴት ልጅ በሰላም ተገላግላለች።

በባቡሩ ላይ ተሳፍረው የነበሩ አንድ ዶክተር እና ሁለት ነርሶች እናቲቷን አዋልደዋታል።

በመልካም ጤንነት ላይ እንደሚገኙ የተነገረላቸው እናቲቱ እና አዲስ የተወለደችው ህጻን፤ ደብሊን ከደረሱ በኋላ ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል።

የአየር ላንድ ምድር ባቡር ተወካይ ህጻኗ ከልጅነት እሰከ 25 ዓመት እስኪሞላት ድረስ ምድር ባቡሩ የነጻ የትራንስፖርት አገልግሎት ይሰጣታል ብለዋል።

በባቡሩ ላይ የምግብ አገልግሎት አቅራቢ ከሆኑት መካከል አንዷ ለመገናኛ ብዙሃን ስትናገር፤ ከመጸዳጃ ቤት ውስጥ አንዲት ሴት ስታቃስት ስሰማ አንድ ችግር እንዳለ ተረዳሁ ትላለች።

የመጸዳጃ ቤቱን በር ስትከፍት በምጥ የተያዘች ሴት ማየቷን እና እርዳታ እንደታገኝ ለባቡሩ ሹፌር እና ከተሳፋሪዎች መካከል ሃኪሞች ካሉ በሚል ጥሪ ማድረጓን ታስረዳለች።

ባቡሩ ከጋልዌይ ወደ አየር ላንድ መዲና ደብሊን እየተጓዘ ነበር።

የፎቶው ባለመብት, RTE

የምስሉ መግለጫ, ባቡሩ ከጋልዌይ ወደ አየር ላንድ መዲና ደብሊን እየተጓዘ ነበር።

በባቡሩ ከተሳፈሩት መካከል የህክምና ዶክተሩ አለን ዲቫይን ይገኙበታል።

ዶክተር አለን አርቲኢ ለተሰኘ መገናኛ ብዙሃን ሲናገሩ ''ዘግይቼ ነበር የደረሰኩት፤ በቦታው ስደርስ ሁለት ነርሶች ለወላዷ ጥሩ ድጋፍ እያደረጉላት ነበር'' ብለዋል።

ከ20 ደቂቃ ምጥ በኋላ እንደተገላገለች የሚናገሩት ዶክተሩ፤ በባቡሩ ላይ ተሳፋሪ የነበሩት ነርሶች ሙያዊ ስነ-ምግባርን በጠበቀ መልኩ አስደናቂ ሥራ ሰርተዋል ሲሉ አሞካሽተዋቸዋል።

የባቡር ጣቢያው ተወካይም ሰራተኞቻችን እና ደንበኞቻችን እናቲቱ በሰላም እንድትገላገል ባደረጉት ትብብር እጅጉን ተደስተናል ብለዋል።