የእስራኤል ፕሬዝዳንት አይዛክ ሄርዞግ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ጋር ለመነጋገር አዲስ አበባ ገቡ
የእስራኤል ፕሬዝዳንት አይዛክ ሄርዞግ ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት ዛሬ ጠዋት አዲስ አበባ መግባታቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ።
ፕሬዝዳንቱ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ እና በምክትላቸው አምባሳደር ብርሃኑ ፀጋዬ አቀባበል እንደተደረገላቸው ተገልጿል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ እንደሚያመለክተው፤ የእስራኤሉ ፕሬዝዳንት በኢትዮጵያ ቆይታቸው የሁለቱን አገራት ግንኙነት በሚያጠናክሩ ጉዳዮች ዙሪያ ከመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር ይወያያሉ ተብሎ ይጠበቃል።
የእስራኤል ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፕሬዝዳንቱ ጉብኝት አስመልክቶ ባሰራጨው መረጃ፤ ሄርዞግ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ጋር እንደሚገናኙ አስታውቋል። ከፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ጋርም እንደሚነጋገሩ ጠቅሷል።
እንደ የእስራኤል ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ‘ቤተ እስራኤላውያን’ ተብለው የሚጠሩት የኢትዮጵያ የአይሑድ ማኅበረሰብ አባላት መሪም ከፕሬዝዳንት ሄርዞግ ጋር ይገናኛሉ።
“ኢትዮጵያ አፍሪካ ውስጥ ወሳኝ አገር” እንደሆነች የገለጸው የእስራኤል ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፤ ጉብኝቱ "በእስራኤል እና በኢትዮጵያ መካከል ያለውን ትብብር፤ በአጠቃላይም ከአፍሪካ አገራት ጋር ያለውን ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር ትልቅ ምዕራፍ የሚከፍት ነው” ብሏል።
የእስራኤሉ ፕሬዝዳንት ወደ ኢትዮጵያ የመጡት የቱርክ ፕሬዝዳንት ረሲፕ ታይፕ ኤርዶዋን ወደ ኢትዮጵያ በመጡ በሳምንቱ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ደማቅ አቀባበል የተደረገላቸው የቱርኩ ፕሬዝዳንት በአዲስ አበባ በሰጡት መግለጫ እስራኤል ለሶማሊላንድ የሰጠችውን የአገርነት ዕውቅና መተቸታቸው ይታወሳል።
ኤርዶዋን፤ እስራኤል ለሶማሊላንድ የሰጠችው የአገርነት ዕውቅና "ለሶማሊላንድም ሆነ ለአፍሪካ ቀንድ ምንም ጥቅም" አይኖረውም ሲሉ ተደምጠዋል። ይህ ንግግራቸው ሶማሊላንድን አስቆጥቷል።
"የመላው ዓለም ዐይን ወደ የአፍሪካ ቀንድ” የዞረበት ጊዜ እንደሆነ የገለጹት ኤርዶዋን፤ ቱርክ በቀጣናው አዲስ ግጭት እንዲነሳ እንደማትፈልግ ተናግረው ነበር። "የዚህ ቀጣና ችግሮች በራሳቸው በቀጣናው አገራት ሊፈቱ እንደሚገባ እንዲሁም የአፍሪካ ቀንድ የውጭ ኃይሎች የጦር ሜዳ መሆን እንደሌለበት እናምናለን" ብለውም ነበር።
ከትናንት በስቲያ ሰኞ ደግሞ የሳዑዲ ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋሊድ አልኬሬጂ አዲስ አበባ መጥተው ከኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጋር ተነጋግረዋል።
ስለ ቀጠናዊ ሰላም እና ሁለቱን አገራት በሚመለከቱ የፀጥታ ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል የተባሉት ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣታቸው አንድ ሳምንት አስቀድሞ ወደ ኤርትራ ተጉዘው ከፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር ተነጋግረው ነበር።
ከሁለት ሳምንት በፊት ደግሞ የሳዑዲ አረቢያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ልዑል ፋይሰል ቢን ፋርሐን በአዲስ አበባ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ጋር በሁለትዮሽ እንዲሁም ቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል።