የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት እስራኤል ለሶማሊላንድ እውቅና መስጠቷን ተከትሎ አስቸኳይ ስብሰባ ጠራ

እስራኤል ከሶማሊያ ተነጥላ ነጻ አገርነቷን ላወጀችው ሶማሊላንድ ነጻ እና ሉዓላዊ አገርነት ዕውቅና ሰጥታለች። ይህ የእስራኤል ውሳኔ ከሦስት አስርት ዓመታት በላይ ከሶማሊያ ማዕከላዊ መንግሥት በመነጠል የነጻ አገርነት ዕውቅናን ስትጠብቅ ለቆየችው ሶማሊላንድ የመጀመሪያው የአገርነት ዕውቅና ነው። ነገር ግን ይህ የእስራኤል ዕውቅና የግዛቴ አለል ናት ከምትላት ከሶማሊያ ጀምሮ ከአፍሪካ ኅብረት፣ ከኢጋድ እና ከተለያዩ አገራት ጠንካራ ተቃውሞ ገጥሞታል።

ጭምቅ ሃሳብ

  • ሶማሊላንድ የመጀመርያውን የሉዓላዊ አገርነት ዕውቅና ከእስራኤል አግኝታለች
  • ከሶማሊያ በስተ ሰሜን የምትገኘው ሶማሊላንድ በኤደን ባሕረ ሰላጤ ላይ የምትገኝ ከፊል በረሃማ የሆነች አካባቢ ናት
  • የሶማሊያ ወታደራዊ መሪ የነበሩት ሲያድ ባሬ በአውሮፓውያኑ 1991 ከሥልጣን ከተወገዱ በኋላ ነጻ አገር መሆኗን አውጃለች

የቀጥታ ሽፋን

  1. ኤርትራ የሶማሊላንድ እውቅናን በተለመከተ የፀጥታው ምክር ቤት የማያሻማ ምላሽ ሊሰጥ ይገባል አለች

    የማስታወቂያ ሚኒስትሩ የማነ ገብረ መስቀል

    የፎቶው ባለመብት, MOI ERITREA

    ቤንያሚን ኔታኒያሁ ሀገራቸው እስራኤል ለሶማሊላንድ እውቅና መስጠታቸውን ተከትሎ የኤርትራ መንግሥት ባወጣው መግለጫ የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት የማያሻማ ምላሽ እንዲሰጠ ጠይቋል።

    የኤርትራ ማስታወቂ ሚኒስቴር በለቀቀው አጭር መግለጫ “ተውኔቱ ምስጢራዊ አይደለም ሲብላላ የቆየ እንጂ” ብሎ “አደገኛ ቀጣናዊ እና ዓለም አቀፋዊ ቀውስ እና መረበሽ” ይዞ ይመጣል ሲል አስጠንቅቋል።

    የማስታወቂያ ሚኒስትሩ የማነ ገብረ መስቀል የመንግሥታቸውን መግለጫ በኤክስ ገፃቸው አጋርተው የፀጥታው ምክር ቤት አባላት የማያሻማ ምላሽ ሊሰጡት እንደሚገባ አስምረዋል።

    መግለጫው “በተለይ ‘ከታይዋን’ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ያለውን ጉዳይ ከግምት በማስገባት ቻይና ትልቅ ኃላፊነት ልትወጣ እንደሚገባ” ገልጿል።

    ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር መቃቃር ውስጥ የገባው የፕሬዝደንት ኢሳያስ አፈወርቂ አገዛዝ ከሶማሊያ እና ግብፅ ጋር ልዩ የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት እንደደረሰ ይታወሳል።

    አርብ ዕለት የተሰማውን የሶማሊላንድ እውቅና ዜና ተከትሎ በርካታ የአረብ እና የአፍሪካ ሀገራት የእስራኤልን ውሳኔ እንደሚቃወሙ የሚገልፁ መግለጫዎች አውጥተዋል።

  2. ለሶማሊላንድ እውቅና የምትሰጥ ሁለተኛዋ ሀገር ማን ልትሆን ትችላለች?

    የሶማሊላንድ ፕሬዝደንት አብዱራህማን ኢሮ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    እስራኤል ለሶማሊላንድ ሀገርነት ይፋ እውቅና መስጠቷን ተከትሎ የሶማሊላንድ እና የሶማሊያ እንዲሁም የቀጣናው ዕጣ ፈንታ ምን ሊሆን ይችላል የሚለው ጥያቄ መነሳት ጀምሯል።

    ሶማሊያ፣ ቱርክ፣ ግብፅ፣ ጂቡቲ፣ የአፍሪካ ኅብረት እና ሌሎች የአረብ እንዲሁም የአፍሪካ ሀገራት ውሳኔውን በፅኑ ተቃውመውታል።

    በሌላ በኩል ሶማሊላንድ ሌሎችም ሀገራትም እስራኤልን ተከትለው እውቅና እንዲሰጡ የአቅሟን እያደረገች ትገኛለች።

    አንዳንድ ዘገባዎች እንደሚጠቁሙት የተወሰኑ የአፍሪካ እና ምዕራባዊያን እንዲሁም የአረብ ሀገራት ለሶማሊላንድ እውቅና ሊሰጡ ይችላሉ። ዩናይትድ ኪንግደም፣ ዩናይትድ አረብ ኤሜሬትስ፣ ኢትዮጵያና ደቡብ ሱዳን ከእነዚህ ሀገራት መካከል ይጠቀሳሉ።

  3. የአውሮፓ ኅብረት የሶማሊያ ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት እንዲከበር ጠየቀ

    የአውሮፓ ኅብረት ባንዲራ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአውሮፓ ኅበረት እስራኤል ለሶማሊላንድ የሰጠችውን እውቅና ተከትሎ በለቀቀው መግለጫ የሶማሊያ ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት መከበሩ አስፈላጊ ነው ብሏል።

    ኅብረቱ በቃል አቀባዩ በኩል በለቀቀው አጭር መግለጫ የሶማሊያ ሕገ-መንግሥት፣ የአፍሪካ ኅብረት እና የተባበሩት መንግሥታት ቻርተሮችን ተንተርሶ የሶማሊያ ሉዓላዊነት መከበር አለበት ብሏል።

    ይህ ለመላው የአፍሪካ ቀንድ ሰላም እና መረጋጋት ወሳኝ ነው ይላል የኅብረቱ መግለጫ።

    የአውሮፓ ኅብረት በሶማሊላንድ እና በሶማሊያ መንግሥት መካከል ያለውን ለረዥም ዓመታት የዘለቀ ልዩነት ለመፍታት ፍሬያማ የሆነ ውይይት እንዲደረግ እንደሚያበረታታ ገልጿል።

    ባለፈው አርብ ታኅሣሥ 19/2018 እስራኤል ለሶማሊላንድ እውቅና መስጠቷን ተከትሎ የሶማሊያ መንግሥት ተቃውሞውን ገልጿል።

  4. ግብፅ፣ ኢራን፣ ቱርክና ጆርዳንን ጨምሮ በርካታ ሀገራት የእስራኤልን እርምጃ ተቃውመው መግለጫ አወጡ

    የቱርክ፣ ኢራን እና ግብፅ ባንዲራ

    ጆርዳን፣ ሳዑዲ አራቢያ፣ ኳታር፣ ጂቡቲ፣ ኩዌት፣ ኢራን እና ኢራቅ እንዲሁም ናይጄሪያ እና ፓኪስታንን ጨምሮ በርካታ ሀገራት በጋራ ባወጡት መግለጫ እስራኤል ለሶማሊላንድ እውቅና መስጠቷን በፅኑ ተቃውመዋል።

    የጆርዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በማኅበራዊ ሚድያ ገፁ ባጋራው መግለጫ ሀገራቱ እስራኤል የሶማሊያ ክልል ለሆነችው ሶማሊላንድ የሰጠችውን እውቅና በሙሉ ድምፅ “እናወግዛለን” ብሏል።

    መግለጫው ሀገራቱ የእስራኤልን ውሳኔ ያወገዙት በአፍሪካ ቀንድ፣ በቀይ ባሕር እና በጠቅላላው በመላው ዓለም ሰላምና ፀጥታ ላይ ሊኖረው የሚችለውን አሉታዊ ተፅዕኖ ከግምት ውስጥ በማስገባት እንደሆነ አስታውቀዋል።

    መግለጫው ይህ “እስራኤል ለዓለም አቀፍ ሕግ ያላትን ንቀት የሚሳይ ነው” ይላል።

    ጥምር መግለጫው የተባበሩት መንግሥታትን ቻርተር እንዲሁም ዓለም አቀፍ ሕግን አጣቅሶ የሀገራት ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት መጠበቅ አለበት በማለት ውሳኔው “የእስራኤልን ተስፋፊነት የሚያሳይ ነው” ሲል ወቅሷል።

    ሀገራቱ ለሶማሊያ ሉዓላዊነት ያላቸውን ድጋፍ አንፀባርቀው የአፍሪካ ቀንዷን ሀገር አንድነት የሚፈታተን ማንኛውንም ውሳኔ እንደሚቃወሙ ገልፀዋል።

    አልፎም የእስራኤል ድርጊት ይዞት ሊመጣው የሚችለው መዘዝ ከፍተኛ ነው ብለዋል።

    ባለአምስት ነጥብ መግለጫ ያወጡት ሀገራት አክለው “የፍልስጤምን ሕዝግ በግድ ከመሬቱ ለማንሳት የሚደረግን ሙከራ በፅኑ እንቃወማለን” ይላል።

    እስራኤል ለሶማሊላንድ የሰጠችውን እውቅና ተከትሎ በርካታ ሀገራት ጥምር መግለጫ ሲያወጡ ይህ የመጀመሪያው አይደለም።

  5. የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት እስራኤል ለሶማሊላንድ የሰጠችውን እውቅና ተከትሎ አስቸኳይ ስብሰባ ሊያደርግ ነው

    በተባበሩት መንግሥታት የእስራኤል አምባሳደር

    የፎቶው ባለመብት, UNSC

    የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት በሚመጣው ሰኞ እስራኤል ለሶማሊላንድ የሰጠችውን እውቅና በተለመከተ አስቸኳይ ስብሰባ ሊያደርግ መሆኑ ተሰምቷል።

    ይህንን የገለፁት በተባበሩት መንግሥታት የእስራል አምባሳደር የሆኑት ዳኒ ዳኖን እስራኤል “ከፖለቲካዊ ውይይቶች አታፈገፍግም” ብለዋል።

    በኤክስ ገፃቸው ሐሳባቸውን ያሰፈሩት አምባሳደሩ ሀገራቸው “ከአጋር ሀገራት ጋር ትብብርን ለማጠናከር እና ቀጣናዊ መረጋጋትን ለማምጣት በሚል ኃላፊነት በተሞላበት እና ግልፅ በሆነ ሁኔታ” እንደምትንቀሳቀስ አሳውቀዋል።

    ባለፈው አርብ እስራኤል ለሶማሊላንድ እውቅና መስጠቷን ተከትሎ በርካታ የአረብ ሀገራት ተቃውሞዋቸውን አሰምተዋል።

    እስራኤል ለሶማሊላንድ ይፋ እውቅና የሰጠች የመጀመሪያዋ ሀገር ናት።

  6. ትራምፕ እስራኤልን ተከትለው ለሶማሊላንድ ዕውቅና እንደማይሰጡ ተናገሩ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት እስራኤልን ተከትለው “በፍጥነት” ለሶማሊላንድ ሉዓላዊ አገርነት ዕውቅና እንደማይሰጡ ተናገሩ።

    “ሁሉም ነገር ላይ ጥናት እየተደረገ ነው. . . እናጠናዋለን። ብዙ ነገር አጥንቼ ድንቅ ውሳኔ አስተላልፋለሁ። ውሳኔዎቼም ትክክል ናቸው” ሲሉ ከኒው ዮርክ ፖስት ጋር በስልክ ባደረጉት ቃለ ምልልስ ገልጸዋል።

    “ሶማሊላንድ ምን እንደሆነች በትክክል የሚያውቅ ሰው ግን አለ?” ሲሉም ትራምት ጠይቀዋል።

    ሶማሊላንድ፤ አሜሪካ ስትራቴጂክ በሆነው የኤደን ባሕረ ሰላጤ ላይ ይዞታ እንዲኖራት ሐሳብ ማቅረቧን በተመለከተ የተጠየቁት ትራምፕ “ትልቅ ነገር አይደለም” ሲሉ አጣጥለዋል።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ለሶማሊላንድ ዕውቅና መስጠታቸውን ይፋ ካደረጉ በኋላ፤ ሶማሊላንድ የአብርሃም ስምምነትን ለመቀላቀል እንደምትፈልግ ለትራምፕ እንደሚገልጹ ተናግረዋል።

    ትራምፕ ግን ሐሳቡ ብዙም እንዳልተዋጠላቸው ጠቁመዋል። ከኔታንያሁ ጋር በቀጣይ የሚኖራቸው ውይይት የሚያተኩረተው የጋዛ ሰርጥ ላይ እንደሆነም ገልጸዋል።

  7. “ግዛት የምታስፋፋው እስራኤል ለፍልስጤም አገርነት ዕውቅና ብትሰጥ ይሻላል”- ኳታር

    ኳታር፤ እስራኤል ለሶማሊላንድ የሰጠችውን ዕውቅና “በጽኑ እንደምታወግዝ” ገለጸች።

    “ግዛት የምታስፋፋው” ያለቻት እስራኤል እና ሶማሊላንድ “አንዳቸው ለሌላው የሰጡትን ዕውቅና” እንደማትቀበል አስታውቃለች።

    የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በማኅበራዊ ሚዲያ ገጹ ባወጣው መግለጫ “ይህ የተናጠል እርምጃ አደገኛ ነው፤ ዓለም አቀፍ ሕግን ይጥሳል፤ የሶማሊያን ሉዓላዊነት፣ አንድነት እና የግዛት ወሰን ይጣረሳል” ብሏል።

    የሶማሊያን “አንድነት” በሚጥስ መልኩ የሚፈጠር “ትይዩ አስተዳደርን” ኳታር እንደማትቀበል ገልጻለች። የሶማሊያን ደኅንነት እና መረጋጋት ለማስጠበቅ ቁርጠኛ እንደሆነችም አጽንኦት ሰጥታለች።

    ኳታር፤ “ከወንድሞቻችን ጎን እንቆማለን” በማለትም አቋሟን ይፋ አድርጋለች።

    የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መግለጫ “ግዛት የምታስፋፋው እስራኤል ለፍልስጤም አገርነት ዕውቅና ብትሰጥ ይሻላል” ይላል።

    “ፍልስጤማውያን በብሔራዊ ግዛታቸው አገር የመመሥረት መብታቸው ዓለም አቀፍ ድጋፍ ያለው ነው” ሲልም አክሏል።

    እስራኤል “ዓለም አቀፉን ማኅበረሰብ መናቋን እንድታቆም” እንዲሁም “ቀጣናዊ አለመረጋጋት የሚያስከትል ደንታ የለሽ ፖሊሲ ከመተግበር እንድትቆጠብ” ኳታር ጥሪ አቅርባለች።

  8. “በተናጠል የሚሰጥ ዕውቅና የተመድን ስምምነት ይጥሳል”- ኢጋድ

    የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) እስራኤል ለሶማሊላንድ የሰጠችው “የተናጠል” የሉዓላዊ አገርነት ዕውቅና የመንግሥታቱን ድርጅት እና የአፍሪካ ኅብረትን መርሕ እንደሚጥስ ገለጸ።

    በተጨማሪም ከኢጋድ ስምምነት ጋር እንደሚጣረስ አስታውቋል።

    በማኅበራዊ ሚዲያ ገጹ ባወጣው መግለጫ፤ “ሶማሊያ ሉዓላዊት የኢጋድ አባል አገር ናት” ያለ ሲሆን፤ “በተናጠል የሚሰጥ ዕውቅና” የዓለም አቀፍ ተቋማትን አሠራር ይጥሳል ብሏል።

    ለሶማሊያ መንግሥት ያለውን ድጋፍ ገልጾ፤ በቀጣናው ሰላም፣ መረጋጋት እና ትብብር እንዲሰፍን ለማድረግ ሲባል ዓለም አቀፍ ስምምነት እንዲከበር ጠይቋል። ለቀጣናዊ አካታች ፖለቲካዊ ሒደት እና ቀጣናዊ ትብብር ያለውን ቁርጠኛነትም ኢጋድ ገልጿል።

  9. እስራኤል ለሶማሊላንድ የሰጠችው ዕውቅና እና የፍልስጤም ስጋት

    በጋዛ መኖሪያቸው የፈረሰ ፍልስጤማውያን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በጋዛ መኖሪያቸው የፈረሰ ፍልስጤማውያን

    እስራኤል በጋዛ ውስጥ ለሁለት ዓመታት መጠነ ሰፊ ወደታራዊ ዘመቻ ባካሄደችበት ጊዜ ጋዛን ሙሉ ለሙሉ በመቆጣጠር ፍልስጤማውያንን ከግዛቲቱ የማስወጣት ፍላጎት እንዳላት በስፋት ሲነገር ነበር።

    ኋላ ላይም ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የጋዛ ነዋሪዎችን ወደ ሌሎች አገራት በማስፈር ጋዛን የባሕር ዳርቻ የመዝናኛ ስፍራ የማድረግ ዕቅድ እንዳቸላው ይፋ ሲያደርጉ ጉዳዩ መነጋገሪያ ሆኖ ነበር።

    ከዚሁ ሃሳብ ጋር ተያይዞ ከጋዛ የሚወጡት ፍልስጤማውያን ወደ ተለያዩ አገራት እንደሚሰፍሩ መነገሩን ተከትሎ የተለያዩ አገራት ስም ሲነሳ ነበር። ከእነዚህም መከካል ሶማሊላንድ አንዷ ነበረች።

    ይህ ፍልስጤማውያንን ከጋዛ አስወጥቶ ወደ ሌሎች አገራት የመውሰዱ ዕቅድ በይፋ ባይነገርም ከተለያዩ አገራት ከፍተኛ ተቃውሞ ገጥሞት ነበር።

    የሶማሊያ መንግሥት እና ራሷ የሶማሊላንድ አስተዳደር ጭምር ይህንን ሃሳብ እንደማያውቁት እንዲሁም በፍጹም እንደማይቀበሉት በወቅቱ ባወጧቸው በመግለጫዎች አሳውቀዋል።

    አሁን እስራኤል ለሶማሊላንድ የሉዓላዊ አገርነት ዕውቅና መስጠቷን ተከትሎ ይህ ሃሳብ በስጋት መልክ እየተንጸባረቀ ነው። እውቅናውን ተቃውመው መግለጫ ያወጡት የፍልስጤም አስተዳደር እና ቱርክ ይህነን ጉዳይ ጠቅሰውታል።

    ፍልስጤም ለሶማሊላንድ የተሰጠውን ዕውቅና እንደማትደግፍ ባስታወቀችበት መግለጫዋ “በተለይም ከጋዛ ሰርጥ ፍልስጤማውያንን በሌላ አገር ከማስፈር ጋር በተያያዘ የሶማሊላንድን ስም እስራኤል ስታነሳ ነበር” በማለት ስጋቷን አመልክታለች።

    የተሰተውን ዕውቅና ተከትሎ እስራኤል “በማንኛውም ሽፋን ተጠቅማ በግድ ሕዝባችንን እንድታፈናቅል አንፈቅድም” በማለት ከሶማሊላንድ ጋር ተያይዞ ከዚህ በፊት ሲነሳ የነበረውን ሃሳብ በድጋሚ ተቃውማለች።

    በተጨማሪም የቱርክ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የእስራኤልን የዕውቅና ውሳኔ በተቃወመበት መግለጫው ላይ እርምጃው ሕገወጥ እማ በቀጣናው ብሎም በዓለም ዙሪያ አለመረጋጋትን ሊያስከትል የሚችል ነው ብሏል።

    ቱርክ ጨምራም እስአኤል በፍልስጤም ግዛቶች ውስጥ የመስፋፋት ፖሊሲዋን በቀጠለችበት እና ፍልስጤም እንደ አገር ዕውቅና እንዳታገኝ ሁሉን ነገር እያደረግቸበት ባለቤእ ጊዜ ለሶማሊላንድ ዕውቅና መስጠቷ ግልጽ ጣልቃ ገብነት ነው ብላለች።

  10. ቻይና፣ ሳዑዲ አረቢያ እና ፍልስጤም ለሶማሊላንድ የተሰጠውን ዕውቅና ተቃወሙ

    ፍልስጤም፣ ቻይና እና ሳዑዲ አረቢያ እስራኤል ለሶማሊላንድ ዕውቅና መሰጠቷን በጽኑ አወገዙ።

    አገራቱ በተናጠል ባወጡት መግለጫ ለሶማሊያ ሉዓላዊነት ያላቸውን ድጋፍም ገልጸዋል።

    የሳዑዲ አረቢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ “ለሶማሊያ አንድነት እና የግዛት ሉዓላዊነት ያለንን ድጋፍ እንገልጻለን” ብሏል።

    እስራኤል ለሶማሊላንድ ዕውቅና መስጠቷ “የተናጠል እና አስገንጣይ እርምጃ” መሆኑን ጠቅሶ “ዓለም አቀፍ ሕግን” ይጻረራል ሲል ኮንኗል።

    ፍልስጤምም ለሶማሊላንድ የተሰጠውን ዕውቅና እንደማትደግፍ አስታውቃለች።

    “በተለይም ከጋዛ ሰርጥ ፍልስጤማውያንን በሌላ አገር ከማስፈር ጋር በተያያዘ የሶማሊላንድን ስም እስራኤል ስታነሳ ነበር” ስትል ፍልስጤም መግለጫ አውጥታለች።

    እስራኤል “በማንኛውም ሽፋን ተጠቅማ በግድ ሕዝባችንን እንድታፈናቅል አንፈቅድም” ብላለች።

    በሶማሊያ የቻይና ኤምባሲ በማኅበራዊ ሚዲያው ባወጣው መግለጫ የሁለቱ አገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች በስልክ ውይይት እንዳደረጉ ጠቅሶ፤ ለሶማሊያ ያለውን ድጋፍ ገልጿል።

    “ቻይና የሶማሊያን ሉዓላዊነት፣ ብሔራዊ አንድነት እና የግዛት ወሰን ትደግፋለች” ሲልም የኤምባሲው መግለጫ ያትታል።

  11. "የእስራኤል ውሳኔ አለመረጋጋትን ያስከትላል" ቱርክ

    ሃካን ፊዳን

    የፎቶው ባለመብት, @HakanFidan/x

    የምስሉ መግለጫ, ቱርክ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሃካን ፊዳን

    የሶማሊያ መንግሥት ወዳጅ የሆነችው ቱርክ እስራኤል ለሶማሊላንድ የሰጠችውን የአገርነት ዕውቅና በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ በኩል ባወጣችው መግለጫ ተቃወመች።

    የእስራኤል ውሳኔ “የኔታኒያሁ መንግሥት ሕገወጥ እርምጃ በቀጣናው እና በዓለም አቀፍ ደረጃ አለመረጋጋትን ለመፍጠር ያለመ ሌላ ምሳሌ ነው” በማለት ለሶማሊላንድ የተሰጠውን ዕውቅና ቱርክ ተቃውማለች።

    የፍልስጤም ጉዳይን በማንሳትም “ይህ እርምጃ የቀጠለውን የመስፋፋት ፖሊሲ እና ፍልስጤም እንደ አገር እንዳትታወቅ ሁሉንም ጥረት የምትዳረገው እስራኤል በሶማሊያ ውስጣዊ ጉዳይ በግልጽ ጣልቃ መግባትን የሚያመለክት ነው” ሲል መግለጫው ወቅሷል።

    ጨምሮም የሶማሊያ እና ሶማሊላንድ ክልል መጻኢ ዕጣ ፈንታን በተመለከተ የሚሰጥ ውሳኔ የሶማሊያውያንን ፍላጎት ሚያንጸባርቅ መሆን አለበት ብሏል።

    በአፍሪካ ቀንድ ሰላም እና ደኅንነት አስፈላጊ መሆኑን የገለጸው የቱርክ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መግለጫ ቱርክ የሶማሊያን የግዛት አንድነት በጽኑ እንደምትደግፍ እና ከሶማሊያ ሕዝብ ጎን እንደምትቆም ገልጻለች።

    የሶማሊያ ወዳጅ የሆነችው ቱርክ በኢትዮጵያ እና በሶማሊያ መካከል በሶማሊላንድ ምክንያት የተፈጠረውን አለመግባባት ያሸማገለች ሲሆን፣ ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ ከፍተኛ ምጣኔ ሀብታዊ እና ወታደራዊ ስምምነትን ከሶማሊያ መንግሥት ጋር ማድረጓ ይታወቃል።

  12. የአፍሪካ ኅብረት ለሶማሊላንድ ዕውቅና መሰጠቱን ነቀፈ

    የአፍሪካ ኅብረት ዋና መቀመጫ

    የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ማሕሙድ አሊ ዩሱፍ እስአኤል ለሶማሊላንድ ዕውቅና መሰጠቷን ነቀፉ።

    አርብ ማምሻውን በወጣው መግለጫ ኅብረቱ ለሶማሊያ አንድነት እና ሉዓላዊነት ቁርጠኛ መሆኑን በመጥቀስ እስራኤል ለሶማሊላንድ ዕውቅና መስጠቷ “እጅጉን እንደሚያሰጋ” ተገልጿል።

    የአፍሪካ ኅብረት እአአ በ1964 ባስተላለፈው ውሳኔ እንዲሁም ባለው የጋራ ስምምነት መሠረት ነጻነትን ማዕከል ያደረገ የአገራትን ድንበር ማክበር ዋጋ የሚሰጠው ጉዳይ እንደሆነ ተጠቅሷል።

    ኅብረቱ “ሶማሊላንድን እንደ ነጻ አገር ዕውቅና መስጠትን” እንደሚቃወም ገልጾ፤ ሶማሊላንድ የሶማሊያ “ቁልፍ አካል” መሆኗን አስታውቋል።

    “የሶማሊያን አንድነት፣ ሉዓላዊነት እና የግዛት ወሰን የሚያንኳስስ ውሳኔ ከአፍሪካ ኅብረት መርኅ ጋር ይጣረሳል” ይላል መግለጫው።

    ውሳኔው “ለመላው አህጉሪቱ ሰላም እና መረጋጋት አደጋ ይደቅናል” ሲልም ኅብረቱ አቋሙን ገልጿል።

    የሶማሊያ ባለሥልጣናት ሰላም ለማስከበር፣ የመንግሥት ተቋማትን ለማጠናከር እና አካታች አስተዳደርን ለማስቀጠል ለሚያደርጉት ጥረት የአፍሪካ ኅብረት ድጋፍ እንደሚሰጥም አክሏል።

  13. የግብፅ፣ የሶማሊያ፣ የቱርክ እና የጂቡቲ ተቃውሞ

    እስራኤል ለሶማሊላንድ ዕውቅና በሰጠች በሰዓታት ውስጥ የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከሶማሊያ፣ ከቱርክ እና ከጂቡቲ አቻዎቻቸው ጋር የስልክ ውይይት አድርገዋል።

    በውይይቱ የእስራኤል ውሳኔ በአፍሪካ ቀንድ አካባቢ ያለውን ውጥረት ያባብሰዋል በማለት ስጋታቸውን መግለጻቸው ተዘግቧል።

    የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ እስራኤል ሶማሊላንድን እንደ ሉዓላዊ አገር ዕውቅና መስጠቷን የአራቱ አገራት ባለሥልጣናት “ሙሉ ለሙሉ ውድቅ” በማድረግ አውግዘውታል ብሏል።

    በተጨማሪም አገራቱ ለሶማሊያ ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት ያላቸውን ድጋፍ በማጠናከር በተናጠል የሚወሰዱ እርምጃዎች የሶማሊያን መረጋጋት በማናጋት “ትይዩ አካላትን” የሚፈጥር ነው ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ይህ ለአንድ ሉዓላዊ አገር ግዛት ዕውቅና መስጠት ከዓለም አቀፍ ሕግ እና ከተበባሩት መንግሥታት ቻርተር አንጻር ያልነበረ ሁኔታን የሚፈጥር ነው ማለታቸውን መግለጫው ጠቅሷል።

  14. ኔታኒያሁ ለሶማሊላንድ የተሰጠውን ዕውቅና ይፋ ሲያደርጉ ምን አሉ?

    ኔታኒያሁ

    የፎቶው ባለመብት, @netanyahu/x

    የምስሉ መግለጫ, ኔታኒያሁ ውሳኔውን ከፈረሙ በኋላ

    የሶማሊላንድ ሪፐብሊክ ነጻ እና ሉዓላዊ አገር መሆኗን በይፋ ዕውቅና የሚሰጠውን ውሳኔ ዛሬ [አርብ] ይፋ አድርጌያለሁ።

    ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰአር፣ ከሶማሊላንድ ሪፐብሊክ ፕሬዝዳንት ጋር በመሆን የተስማማንበትን የጋራ ውሳኔ ተፈራርመናል።

    ይህ ውሳኔ በአብረሃም ስምምነት መሠረት በፕሬዝዳንት ትራምፕ አነሳሽነት የተፈረመ ነው።

    የሶማሊላንድ ፕሬዝዳንት፣ ዶ/ር አብዲራህማን ሞሐመድ አብደላ እንኳን ደስ አለዎ እያልኩ፤ በአመራራቸው መረጋጋት እና ሰላም ለማምጣት ያላቸውን ቁርጠኝነት አድናቆቴን እገልጻለሁ።

    ፕሬዝዳንቱ በእስራኤል ይፋዊ ጉብኝት እንዲያደርጉ ግብዣ አቅርቤያለሁ።

    ፕሬዝዳንቱም ለዚህ ታሪካዊ ውሳኔ ምስጋናቸውን አቅርበው፤ ሽብርተኝነትን በመዋጋት እና ለቀጣናዊ ሰላም ላስገኘሁት ውጤት አድናቆታቸውን ገልጸዋል።

    ለውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳአር፣ ለሞሳድ ኃላፊ ዴቪድ ባርኒ እና ለሞሳድ ለዛሬው ውሳኔ ላበረከቱት አስተዋጽኦ ምስጋናዬን አቀርባለሁ። ለሶማሊላንድ ሕዝብም ስኬት፣ ብልጽግና እና ነጻነትን እመኛለሁ።

    የእስራኤል መንግሥት ከሶማሊላንድ ሪፐብሊክ ጋር በእርሻ፣ በጤና፣ በቴክኖሎጂ እና በምጣኔ ሀብት በኩል ያለውን ግንኙነት በአስቸኳይ ለማስፋት አቅዷል።