አሜሪካ የኢራን ባለሥልጣናትን ዒላማ ለማድረግ ማቀዷ ተነገረ
አሜሪካ በኢራን ውስጥ ለምትፈጽመው ወደታራዊ ጥቃት የአገሪቱን አመራሮች በተናጠል ዒላማ ማድረግን ጨምሮ የመንግሥት ለውጥን ለማካሄድ ዕቅድ መውጣቱን ሁለት የአሜሪካ ባለሥልጣናት ለሮይተርስ ተናገሩ።
ባለሥልጣናቱ ከዕቅዱ ምሥጢራዊነት የተነሳ ስማቸው እንዲገለጽ ያልፈቀዱ ሲሆን፣ ተጨማሪ ዝርዝር ከመናገር ተቆጥበዋል። ነገር ግን ይህ ዕቅድ ተግባራዊ የሚሆነው ከፕሬዝዳንት ትራምፕ ትዕዛዝ ሲተለላፍ መሆኑን ገልጸዋል።
እየተደረገ ያለው ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ውጤት ካላስገኘ አሜሪካ ወደ ወታደራዊ እርምጃ ፊቷን እንደምታዞር እየተነገረ ሲሆን፣ የኢራንን የደኅንነት ተቋማት እና የኒውክሌር ማዕከላት ዒላማ ለሚያደርጉ ለተከታታይ ለሳምንታት የሚዘልቁ ዘመቻዎች የአሜሪካ ሠራዊት እየተዘጋጀ መሆኑ ሲዘገብ ቆይቷል።
ባለፉት ሳምንታት ትራምፕ ከፍተኛ መጠን ያላቸውን የጦር መሣሪያዎቻቸውን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ እንዲንቀሳቀሱ አድርገዋል። ነገር ግን ዋነኛው ኃይሏ በግዙፍ የጦር መርከቦች እና በተዋጊ አውሮፕላኖች ላይ የተመሠረተ ነው።
አሜሪካ ወታደራዊ እርምጃ በኢራን ላይ ከከፈተች ከፍተኛ የአገሪቱ ባለሥልጣናት ዒላማ እንደሚደረጉ እየተነገረ ነው። እስራኤል ባለፈው ዓመት በኢራን ላይ ጥቃት ባካሄደችበት ጊዜ ጥቂት የማይባሉ ወደታራዊ እና ፖቲካዊ አመራሮች ላይ ጉዳት አድርሳለች።
በኢራን ላይ ስለሚካሄደው ዘመቻ ዕቅድ ለሮይተርስ የገለጹት ባለሥልጣናት፣ አሜሪካ የኢራን መሪዎችን ዒላማ ለማድረግ የሚያስችል ምን ያህል አስተማማኝ የመረጃ ምንጭ እንዳላቸው አልገለጹም።
የአሜሪካ ዕቅድን በተመለከተ ሮይተርስ ከዋይት ሐውስ እና ከመከላከያ ሚኒስቴር አስተያየት ለማግኘት ጥያቄ አቅርቦ ወዲያውኑ መልስ አላገኘም።