ኢራን ዩራኒየም የማበልጸግ መብቷ ላይ “እንደማትደራደር ወይም ከአቋሟ ፈቀቅ እንደማትል” ገለጸች
የኢራን ዩራኒየም የማበልጸግ መብት “ድርድር የሚደረግበት ወይም ከአቋም ፈቀቅ የሚባልበት ጉዳይ” እንዳልሆነ የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ተናገሩ።
ቃል አቀባዩ ኢስማኢል ባቃኢ ዛሬ ሰኞ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤ ጦርነቱን ለመቋጨት በፓኪስታን አማካኝነት የሚደረገው ንግግር መቀጠሉን ገልጸዋል።
ኢራን ባለ 14 ነጥብ የስምምነት ዕቅድ ወደ አሜሪካ ልካ እንደነበር ያስታወሱት ቃል አቀባዩ፤ ዋሽንግተንም ሆነ ቴህራን በዕቅዱ ላይ የራሳቸውን ሐሳብ ማንሳታቸውን ተናግረዋል።
“የአሜሪካው ወገን ይህ [ባለ 14 ነጥብ] ዕቅድ ውድቅ መደረጉን ባለፈው ሳምንት በይፋ ቢያስታውቅም፤ ያቀረቧቸው ነጥቦች እና የማስተካከያ አስተያየቶች ዝርዝር ግን በፓኪስታን አማካኝነት ደርሶናል” ብለዋል።
“ዕቅዳችንን በላክን ማግስት ከሌላኛው ወገን የቀረቡ ተከታታይ ዕቅዶች ደርሰውናል። ዕቅዶቹ ባለፉት ጥቂት ቀናት ውስጥ የተገመገሙ ሲሆን የእኛ ምላሽም ቀርቧል። በፓኪስታን አማካኝነት የሚደረገው ድርድር ቀጥሏል" ሲሉም ንግግሩን የማስጀመር ሂደቱ ያለበትን አረስድተዋል።
ይህም ቢሆን ግን ኢራን ዩራኒየም የማበልጸግ መብቷን ለድርድር እንደማታቀርብ ባቃኢ ተናግረዋል።
"በእርግጠኝነት መናገር የሚቻለው፤ [ዩራኒየም የማበልጸግ] መብት ልንደራደርበት ወይም ከአቋም ፈቀቅ የምንልበት ጉዳይ አይደለም። ኢራን ዩራኒየም ለማበልጸግ ያላት መብት የኒውክሌር መሣሪያዎች ላለማስፋፋት በተፈረመው ስምምነት መሠረት እውቅና የተሰጠው ነው" ብለዋል።
እንደ ቃል አቀባዩ ገለጻ ኢራን የምትፈልጋቸው የድርድር ነጥቦች በግልጽ ተቀምጠዋል። እንዳይንቀሳቀሱ የታገዱ የኢራን ሀብቶች መለቀቅን በማሳያነት ያነሱት ቃል አቀባዩ፤ "እናንተ እኛ [ለድርድር] ያስቀመጥነው ቅድመ ሁኔታ እንደሆነ ትናገራላችሁ፤ እኛ የመብት ጥያቄ እንደሆነ እንናገራለን” ብለዋል።