በናይጄሪያ አንድ መንደር ላይ በተፈጸመ ጥቃት ቢያንስ 30 ሰዎች ተገደሉ

የፎቶው ባለመብት, Zakari Kontagora
በናይጄሪያ ኒጀር ግዛት ውስጥ በሚገኝ መንደር የታጠቁ ኃይሎች በፈጸሙት ጥቃት ቢያንስ 30 ሰዎችን መገደላቸውን እና ንብረት መዘረፉን የክልሉ ባለስልጣናት ተናገሩ።
ጥቃት ፈጻሚዎቹ ቅዳሜ ዕለት ከካሱዋን-ዳጂ መንደር አቅራቢያ ከሚገኝ ጫካ ወጥተው የአካባቢውን ገበያ ማቃጠላቸውን፣ ሱቆችን መዝረፋቸውን እና ቁጥራቸው ያልታወቀ ሰዎችን አፍነው መውሰዳቸውን ፖሊስ አስታውቋል።
"ታጣቂዎቹ በሞተር ሳይክሎች መሳሪያ ይዘው ወደ ከተማው ከገቡ በኋላ ሰዎችን በመክበብ ረሽነዋቸዋል፤ ሌሎቹ ደግሞ በጥይት ተመትተው ሞተዋል።" ሲል የአካባቢው ነዋሪ ለቢቢሲ ሃውሳ ተናግሯል።
ናይጄሪያ ውስጥ ሽፍቶች በመባል የሚታወቁት የታጠቁ የወንጀል ቡድኖች የሚፈጽሟቸው ጥቃቶች እና አፈናዎች ለዓመታት እንደቀጠሉ ናቸው።
የኒጀር ግዛት የአደጋ ጊዜ አስተዳደር ኤጀንሲ ባለሥልጣን የሆኑት አብዱላሂ ሮፊያ የነዋሪዎችን እማኝነት በመጥቀስ የመንደሩ ነዋሪዎች ከበባ ከተፈጸመባቸው በኋላ መገደላቸውን አረጋግጠዋል።
የአካባቢው ማኅበረሰብ ጥቃቱን ተከትሎ በጣም ፈርቶ እንደነበር የተናገሩት ባለሥልጣኑ "ተደብቀው ነው ያሉት፤ ከማንም ጋር ለመነጋገር በጣም ይፈራሉ" ሲሉ አክለዋል።
የኒጀር ግዛት የፖሊስ ቃል አቀባይ ዋሲዩ አቢዮዱን ጉዳት የደረሰባቸውን ነዋሪዎች ለመርዳት የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ወደ አካባቢው መሰማራታቸውን እና የጸጥታ ኃይሎች የታገቱትን ለማስለቀቅ እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል።
ናይጄሪያ ውስጥ መንግሥት አሸባሪ ብሎ በፈረጃቸው የወንጀል ቡድኖች የታገቱ ሰዎችን ለማስለቀቅ ገንዘብ መክፈል ሕገ-ወጥ ድርጊት ነው።
























