የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ሁለት
ወር ሊደፍን የተቃረበውን ጦርነት የሚቋጭ ድርድር ማድረግ የምትፈልግ ከሆነ በስልክ መነጋገር እንችላን አሉ።
ትራምፕ እሁድ ዕለት ለፎክስ ኒውስ በሰጡት ቃለ መጠይቅ “መነጋገር ከፈለጉ፤ ማውራት እንችላለን። ሰዎችን ግን አንልክም” ብለዋል።
ፕሬዝዳንቱ ከፎክስ ኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለ
መጠይቅ ይህንን የተናገሩት አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረግ ጉዞ ላይ እንደጣለችው ገደብ ያሉ የስምምነት እንቅፋቶች እንዲወገዱ
ከጠየቀች በኋላ ነው።
ፕሬዝዳንት ትራምፕ ቅዳሜ ዕለት ተደራዳሪዎቻቸው
ስቲቭ ዋትኮፍ እና ጃሬድ ኩሽነርን ወደ ፓኪስታን ዋና ከተማ ኢስላማባድ እንደሚልኩ ከተናገሩ በኋላ ሁለቱ አገራት በድጋሚ ድርድር
ይጀምራሉ የሚል ተስፋ ጭሮ ነበር።
አርብ ዕለት ፓኪስታን ገብተው የነበሩት የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራግቺ ግን የአሜሪካኑ
ልዑካን ከመድረሳቸው አስቀድሞ ወደ ኦማን ተጉዘዋል።
ትናንት እሁድ ለአጭር ቆይታ ተመልሰው ወደ ፓኪስታን
ተጉዘው የነበረ ቢሆንም የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ተደራዳሪዎቻቸውን የመላክ እቅዳቸውን አስቀድመው ሰርዘዋል።
አራግቺ ከፓኪስታን ወጥተው ወደ ሩሲያ አምርተዋል።
በዚያም ከፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር እንደሚገናኙ ይጠበቃል።
የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከዚህ ቀደም ኢራን
እና አሜሪካን ስታደራድር ወደ ነበረችው ኦማን ባደረጉት ቆይታ ስለ ወሳኙ የባሕር መተላለፊያ ሆርሙዝ እንደተነጋገሩ ተገልጿል።
ትራምፕ በፎክስ ቃለ መጠይቃቸው “መነጋገር ከፈለጉ ወደ እኛ መምጣት ወይም ሊደውሉልን
ይችላሉ። ታውቃለህ፤ ቴሌፎን አለ። ጥሩ፣ ደኅንነቱ የተጠበቀ መስመር አለን” ሲሉ በድጋሚ ልዑካን እንደማይልኩ ጠቁመዋል።
አክለውም፤ “ስምምነቱ ውስጥ ምን መኖር እንዳለበት
ያውቃሉ። በጣም ቀላል ነው፤ የኒውክሌር መሣሪያ ሊኖራቸው አይችልም። ይህ ካልሆነ የምንገናኝበት ምክንያት አይኖርም” ማለታቸውን ሮይተርስ
የዜና ወኪል ዘግቧል።
ከቆይታ በኋላ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ “ማድረግ
ያለባቸው መደወል ነው” በማለት ጽፈዋል።
ትራምፕ ይህንን ያሉት የፓኪስታን የፖለቲካ እና
ወታደራዊ አመራሮች በቴህራን እና ዋሽንግተን መካከል የተኩስ አቁም እንዲፈረም እየጣሩ ባሉበት ወቅት ነው።
የዜና ወኪሉ አሶሺዬትድ
ፕሬስ ያነጋገራቸው አንድ የፓኪስታን ባለሥልጣን ቀጥተኛ ያልሆኑ ንግግሮች መቀጠላቸውን ገልጸዋል።
አሜሪካ እና ኢራን ለሁለት ሳምንት እንዲቆይ
የተስማሙት ተኩስ አቁም ባለፈው ሳምንት ረቡዕ ቢጠናቀቀም፤ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ላልተወሰነ ጊዜ አራዝመውታል። ይህም የካቲት ላይ
የተጀመረው ውጊያ እንዲገታ አድርጓል።
በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የተገደሉበት እና የዓለምን
ኢኮኖሚ ቀውስ ውስጥ የከተተውን ጦርነት በዘላቂነት የሚቋጭ መፍትሔ ላይ ግን እስካሁን አልተደረሰም።