እስራኤል ጋዛ ውስጥ በፈጸመችው ጥቃት 11 ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ
እስራኤል ዛሬ እሁድ ጠዋት በጋዛ በፈጸመችው ጥቃት 11 ፍልስጤማውያን መገደላቸውን የፍልስጤም ሲቪል መከላከያ እና የጤና ባለስልጣናት ገለጹ።
የፍልስጤም ቀይ ጨረቃ ማህበር እንደገለጸው በሰሜናዊ ጋዛ በሚገኝ የድንኳን መጠለያ ላይ በተፈጸመው ጥቃት ቢያንስ ስድስት ሰዎች ተገድለዋል። በደቡባዊ ጋዛ በደረሰ ሌላ ጥቃት ደግሞ አምስት ሰዎች መገደላቸውን አስታውቋል።
የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት በበኩሉ ጥቃቱ የተፈጸመው ሐማስ የተኩስ አቁም ስምምነቱን በመጣሱ እንደሆነ ገልጿል። ከዋሻ ውስጥ ወጥተው የእስራኤል ጦር በሚቆጣጠረው የጋዛ ሰርጥ አካባቢ የተገኙ ታጣቂዎች በጥቃቱ መገደላቸውንም ተናግሯል።
እስራኤል እና ሐማስ የተፈራረሙት የተኩስ አቁም ስምምነት በጥቅምት መጀመሪያ ተግባራዊ መሆን ከጀመረ አንስቶ አንዳቸው ሌላኛቸውን ስምምነቱን በመጣስ ሲከስሱ ቆይተዋል።
የጋዛ ጤና ሚኒስቴር መረጃ እንደሚያመለክተው የተኩስ አቁም ስምምነቱ ከጀመረ ወዲህ ቢያንስ 600 ሰዎች በእስራኤል ተገድለዋል። ከእነዚህ ውስጥ 32 ያህሉ የተገደሉት እስራኤል ከሁለት ሳምንት በፊት በፈጸመቻቸው ተከታታይ የአየር ጥቃቶች ነው።
እስራኤል የዛሬውን ጥቃት የፈጸመችው በአሜሪካ አደራዳሪነት የተፈረመው የተኩስ አቁም ስምምነት ሁለተኛ ምዕራፍ ትግበራ ሊጀመር ዝግጅት እየተደረገ ባለበት ወቅት ነው።
የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የተኩስ አቁም ስምምነቱን አፈጻጸም የሚከታተል የሰላም ቦርድ ባለፈው ወር ማቋቋማቸው ይታወሳል።
በተባበሩት መንግስታት የጸጥታ ምክር ቤት ስልጣን የተሰጠው ይህ ቦርድ፤ በጋዛ የድንበር አካባቢዎችን የሚጠብቅ ዓለም አቀፍ ኃይል የማቋቋም ኃላፊነት ተጥሎበታል። የሃማስን ትጥቅ የመፍታት ሂደት የመቆጣጠር ሥልጣንም አለው።
ቦርዱ የመጀመሪያ ስብሰባውን በሚቀጥለው ሳምንት ዋሽንግተን ውስጥ እንደሚያደርግ የሚጠበቅ ሲሆን በባለሙያዎች የሚመራ ፍልስጤም መንግስት ምስረታን እንዲሁም የጋዛ የመልሶ ግንባታ ሥራን ይቆጣጠራል።