ቀጥታ, የማርበርግ ቫይረስ ሙሉ በሙሉ ከኢትዮጵያ “መወገዱን” የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ

ቫይረሱ ከኢትዮጵያ “ጨርሶ እንደተወገደ” ይፋ ተደረገው በዓለም የጤና ድርጅት አሰራር መሰረት ላለፉት “42 ተከታታይ ቀናት ምንም አዲስ ታካሚ ባለመመዝገቡ” እንደሆነ የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስ ዳባ ገልጸዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ከሚኒያፖሊስ ግድያ በኋላ “ሁሉንም ነገር እየገመገሙ” እንደሆነ ትራምፕ ተናገሩ

    የአሜሪካው ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደራቸው በሚኒያፖሊስ ያለውን ሁኔታ እየገመገመ እንደሆነ ተናገሩ።

    ፕሬዚደንቱ ይህን ያሉት ቅዳሜ እለት በሚኒያፖሊስ የ37 ዓመቱ ነርስ አሌክስ ፕሪቲ በኢሚግሬሽን መኮንኖች በተተኮሰበት ጥይት ከተገደለ በኋላ በተነሳ ተቃውሞ ሰበብ ነው።

    ትራምፕ እሁድ ዕለት ለዎል ስትሪት ጆርናል ሲናገሩ ፕሪቲን ተኩሶ የገደለው መኮንን ስለወሰደው እርምጃ ትክክለኛነት በተደጋጋሚ ቢጠየቁም ቀጥተኛ መልስ ሳይሰጡ ቀርቷል።

    በምትኩ አስተዳደራቸው “ሁሉንም ነገር እየገመገመ እንደሆነ እና ከውሳኔ ጋር እንደሚመጡ” ተናግረዋል።

    ትራምፕ ለጋዜጣው ሲናገሩ ማንኛውንም ዓይነት ተኩስ እንደማይወዱ እና ማንም ቢሆን በጣም ኃይለኛ እና ሙሉ ጥይት የጎረሰ ሽጉጥ ታጥቆ ወደ ተቃውሞ መሄዱ ደስ እንደማይላቸው . . . ይህም ጥሩ ነገር እንደማያስከትል ተናግረዋል።

    አስተዳደራቸው ቀደም ብሎ ፕሪቲን የገደለውን መኮንን የተከላከለ ሲሆን፣ የአገር ውስጥ ደኅንነት ኃላፊ ክሪስቲ ኖም፣ ፕሪቲ የተገደለው "ሽጉጡን ሲያሳይ" እንደነበር ተናግረዋል።

    የአካባቢው ባለሥልጣናት ግን ይህን አስተባብለዋል።

    ባለሥልጣናቱ የሟች ሽጉጥ በሕጋዊ መንገድ የተመዘገበ እንደሆነ ገልጸው፤ የተተኮሰበትም መሣሪያውን ከተነጠቀ በኋላ እንደሆነ ተናግረዋል።

  2. የኢትዮጵያ አየር መንገድ በማርበርግ ምክንያት ያቋረጠውን በረራ ሊጀምር ነው

    በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጂንካ ውስጥ ተከስቶ የነበረው የማርበርግ ቫይረስ ሙሉ ለሙሉ በቁጥጥር ሥር መዋሉን ተከትሎ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አቋርጦት የነበረውን በረራ እንደሚጀምር አስታወቀ።

    በኅዳር ወር መጀመሪያ ላይ በተከሰተው ወረርሽኝ በጂንካ ሆስፒታል ስድስት ሰዎች መሞታቸውን ተከትሎ ነው በሽታው ማርበርግ መሆኑን መንግሥት ያስታወቀው።

    በዚህም ሳቢያ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ጂንካ ያደርግ የነበረውን በረራ አቋርጦ የቆየ ሲሆን፣ በአካባቢው በሕዝብ ትራንስፖርት ላይ ሳይቀር ዕገዳ ተጥሎ ነበር።

    ከሦስት ወራት በፊት ለመጀመሪያ ጊዜ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጂንካ ዞን የተከሰተው የማርበርግ ቫይረስ አሁን በቁጥጥር ሥር መዋሉን የጤና ሚኒስቴር ዛሬ ጥር 18/2018 ዓ.ም. አስታውቋል።

    ይህንንም ተከትሎ አየር መንገዱ ለክልሉ እና ለዞኑ ተቋማት በጻፈው ደብዳቤ ከአዲስ አበባ ጂንካ እና ከጂንካ አዲስ አበባ አቋርጦት የነበረውን በረራ አርብ ጥር 22/2018 ዓ.ም. እንደሚጀምር ከአየር መንገዱ የተጻፈውን ደብዳቤ አያይዞ የዞኑ ኮሚዩኒኬሽን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጹ አሳውቋል።

    የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስ ዳባ እንደተናገሩት ቫይረሱ ከኢትዮጵያ “ጨርሶ እንደተወገደ” ይፋ የተደረገው በዓለም የጤና ድርጅት አሠራር መሠረት ላለፉት “42 ተከታታይ ቀናት ምንም አዲስ ታካሚ ባለመመዝገቡ” ነው።

    ማርበርግ ቫይረስ በኢትዮጵያ ውስጥ መከሰቱ ከታወቀ በኋላ በነበሩት ወራት 14 ሰዎች በበሽታው እንደተያዙ በላብራቶሪ ምርመራ ተረጋግጧል። ከመካከላቸውም የዘጠኙ ሕይወት ሲያልፍ አምስት ሰዎች ከበሽታው አገግመዋል።

  3. በአየር ሁኔታ ምክንያት በአሜሪካ ከ10 ሺህ በላይ በረራዎች ተሰረዙ

    በአሜሪካ እየከፋ በመጣው የበረዶ ወጀብ እና ቅዝቃዜ ምክንያት ሰኞ ዕለት ብቻ ከ10 ሺህ በላይ የአውሮፕላን በረራዎች መሰረዛቸውን የበረራ መረጃዎችን የሚያመለክተው ፍላይትአዌር አስታወቀ።

    ከፍተኛው የአየር ትራንስፖርት መስተጓጎል ያጋጠማት ኒው ዮርክ ስትሆን፤ በከተማዋ ከሚገኙት ጄኤፍኬ፣ ላጉዋርዲያ እና ኒዋርክ አየር ማረፊያዎች ይነሱ የነበሩ 379 በረራዎች ሲሰረዙ ከ30 የሚበልጡት ደግሞ እንዲዘገዩ ተደርገዋል።

    የክረምቱ የበረዶ ወጀብ በቦስተን ሎጋን ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ እንዲሁም በዋሽንግተን ዳላስ፣ ሬጋን እና ባልቲሞር አየር ማረፊያዎች በርካታ በረራዎች እንዲሰረዙ ምክንያት ሆኗል።

    በተጨማሪም የአየር ሁኔታው ከአሜሪካ ባሻገር በካናዳ ቶሮንቶ ፒርሰን አየር ማረፊያ በርካታ የአገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ በረራዎች ላይ መዘግየት ወይም መሰረዝን አስከትሏል።

  4. በአሜሪካ ከተከሰተው ከባድ የአየር ሁኔታ ጋር በተያያዘ ሰዎች እየሞቱ ነው

    በበርካታ የአሜሪካ ግዛቶች ውስጥ በተከሰተው እጅግ ከባድ ቅዝቃዜ ያለበት የአየር ሁኔታ ምክንያት በተለያዩ ቦታዎች የሰዎች ሕይወት እየጠፋ መሆኑ ተዘገበ።

    ካለፈው ሳምንት ማብቂያ ቀናት አንስቶ ባጋጠመው የበረዶ ወጀብ ምንም እንኳን የአንዳንዶቹን ምክንያት በትክክል ለማረጋገጥ ገና ቢሆንም እስካሁን ቢያንስ 14 ሰዎች በተለያዩ ግዛቶች ውስጥ ሞተዋል።

    እስካሁን የተመዘገቡት የሚከተሉት ናቸው:

    • የቴኒሲ ግዛት ባለሥልጣናት ከአየር ሁኔታው ጋር በተያያዘ ሦስት ሰዎች መሞታቸውን አረጋግጠዋል
    • ከበረዶው ወጀብ ጋር በተያያዘ የሁለት ሰዎች ሞት በሉዊዚያና ግዛት ውስጥ ተመዝግቧል
    • ቴክሳስ ውስጥ በአንድ ነዳጅ ማደያ ውስጥ ሞቶ የተገኘ ግለሰብ ምክንያቱ የጤና ወይም ከቅዝቃዜው ጋር የተገናኘ ሊሆን እንደሚችል ፖሊስ ገልጿል
    • እዚያው ቴክሳስ አንዲት የ16 ዓመት ታዳጊ በረዶ ላይ ስትንሸራተት በገጠማት አደጋ ሕይወቷ አልፏል
    • ማሳቹሴትስ ውስጥ አንዲት ሴት በረዶ ተደርምሶባት ሞታለች
    • ካንሳስ ውስጥ ደግሞ አንዲት ሴት በበረዶ ተሸፍና ሞታ ተገኝታለች
    • የሞታቸው ምክንያት ገና ባይረጋገጥም ኒው ዮርክ ውስጥም አምስት ሰዎች ሕይወታቸውን አጥተዋል
  5. በሜክሲኮ ታጣቂዎች የእግር ኳስ ሜዳ በመግባት በከፈቱት ተኩስ ቢያንስ 11 ሰዎች ተገደሉ

    እሁድ ዕለት በሜክሲኮ ሳላማንካ ከተማ በሚገኝ የእግር ኳስ ሜዳ ላይ በተሰባሰቡ ነዋሪዎች ላይ ታጣቂዎች በከፈቱት ተኩስ ቢያንስ 11 ሰዎች ሲገደሉ በርካቶች ጉዳት ደረሰባቸው።

    ታጣቂዎቹ በበርካታ ተሽከርካሪዎች ተጭነው ቦታው ላይ እንደደረሱ እና ማንንም ሳይለዩ ያገኙት ላይ ሲተኩሱ እንደነበር የዐይን እማኞች ተናግረዋል።

    ጥቃቱ ሲፈፀም በርካታ ቤተሰቦች ከአካባቢው የእግር ኳስ ቡድኖች ግጥሚያ በኋላ ለመገናኘት ከጀርባ ተሰባስበው ነበር። ከተገደሉት መካከልም ቢያንስ አንዲት ሴት እና አንድ ሕጻን ይገኙበታል።

    የጥቃቱ ዓላማ ምን እንደሆነ እስካሁን ግልጽ አይደለም።

    በሎማ ዲ ፍሎርስ ሰፈር አቅራቢያ የሚገኘው ካባናስ የእግር ኳስ ሜዳ ላይ ታጣቂዎቹ ጥቃት በፈጸሙበት ጊዜ ቢያንስ 100 ያህል የተኩስ ድምጽ እንደሰሙ በአቅራቢያው የነበሩ ሰዎች ተናግረዋል።

    የአካባቢው እና የፌደራል የፀጥታ ኃይሎች የሰዎች ሕይወት የጠፋበትን ግድያ እየመረመሩ ነው።

    ይህ ጥቃት የተፈፀመው በከተማዋ በአጠቃላይ አምስት ወንዶች የተገደሉበት እና ሌላ የታገተበት በርካታ ጥቃቶች ከተፈጸሙ ከአንድ ቀን በኋላ ነው።

    ሳላማንካ ከተማ የሚገኝበት ጉዋናጁዋቶ ግዛት ባለፈው ዓመት ከመላው ሜክሲኮ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የግድያ ወንጀል ተመዝግቦበታል።

  6. በአሜሪካዋ ግዛት ሜይን በከባድ የአየር ሁኔታ ምክንያት የግል ጄት ተከሰከሰ

    በአሜሪካዋ ግዛት ሜይን ስምንት ሰዎችን ያሳፈረ የግል ጄት ከባንጎር ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ሲነሳ መከስከሱን የአቪየሽን ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    ቦምባርድ ቻሌንጀር 600 ስሪት የሆነው ጄቱ እሑድ ዕለት ሌሊት 9፡45 ላይ መከስከሱን የፌዴራል አቪየሽን ገልጿል።

    የተሳፋሪዎቹ ሁኔታ እና ማንነት አልታወቀም።

    አደጋው የደረሰው አደገኛ የሆነው የክረምት የበረዶ ወጀብ በአብዛኛው የአሜሪካ ክፍል ከተከሰተ በኋላ ነው።

    የአየሩ ሁኔታ እስካሁን ሰባት ሰዎችን የገደለ ሲሆን፣ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን ያለ መብራት አስቀርቷል።

    የጄቱ አብራሪዎችም አደጋው ከማጋጠሙ በፊት በአየር ማረፊያው አካባቢውን ለማየት ሲቸገሩ እንደነበር ተነግሯል።

    ባንጎር አየር ማረፊያ በክረምቱ ከባድ የአየር ሁኔታ ምክንያት እስከ ማክሰኞ ድረስ ማስጠንቀቂያ የተሰጠው ሲሆን፣ ከባድ በረዶ መዝነቡ እንደሚቀጥልም ተተንብይዋል።

    አየር ማረፊያውም አደጋውን ተከትሎ መዘጋቱን እና የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ምላሽ እየሰጡ እንደሆነ ገልጾ፣ ነዋሪዎች ከአካባቢው እንዲርቁ አሳስቧል።

  7. ሪፐብሊካኖች በሚኒያፖሊስ በተፈፀመው ሁለተኛ ግድያ ላይ ሙሉ ምርመራ እንዲደረግ ጠየቁ

    በአሜሪካ፣ ሜኒሶታ ግዛት ፣ሚኒያፖሊስ ከተማ በፈደራል ወኪሎች ሁለተኛው ግድያ ከተፈፀመ በኋላ ዋይት ሃውስ ምርመራ እንዲከፍት ጫና እየተደረገበት ነው።

    ይህንን ጥሪ ያቀረቡት ዲሞክራቶች ብቻ ሳይሆኑ የተወሰኑ ሪፐብሊካኖችም ሕይወት በጠፋበት ተኩስ ላይ ምርመራ እንዲደረግ እየቀረበ ያለውን ጥሪ ተቀላቅለዋል።

    የአላስካ ተወካይ የሆኑት የሪፐብሊካን ሴናተር ሊሳ ሙርኮውስኪ የተሟላ እና ገለልተኛ የሆነ ምርመራ ያስፈልጋል ብለዋል።

    ሴናተሯ ምርመራው "እምነትን እንደሚገነባ" አክለዋል። "የአይስ ወኪሎች ሥራቸውን በሚሰሩበት ወቅት የሚፈልጉትን የማድረግ መብት የላቸውም" ብለዋል ሴናተሯ።

    የሰሜን ካሮላይና የሪፐብሊካን ሴናተር ቶም ቲሊስ እንዲሁም የፔንሲልቫኒያው ሴናተር ዳቭ ማክኮርሚክም በተመሳሳይ ገለልተኛ ምርመራ እንዲደረግ ከጠየቁት መካከል ይገኙበታል።

    የኔብራስካ ሴናተር ፒር ሪኬትስ በበኩላቸው ግድያውን "ሰቅጣጭ" ሲሉ "ግልፅነት የተሞላበት" ምርመራ እንዲደረግ ጠይቀዋል።

  8. በአሜሪካ ከባድ ተቃውሞ የቀሰቀሰው ግድያ

    በሚኒሶታ ግዛት ሚኒያፖሊስ ከተማ ውስጥ ባለፈው ቅዳሜ የስደት እና ጉምሩክ ተቆጣጣሪ ፖሊሶች በግዛቲቱ የሚካሄደውን ስደተኞችን የማሳደድ ድርጊት ከተቃወሙ ነዋሪዎች መካከል አንዱ የሆነው አሌክስ ፕሬቲን ተኩሰው መግደላቸው ተቃውሞ ቀስቅሷል።

    ይህ ግድያ በሳምንታት ውስጥ ሁለተኛው መሆኑም ተቃውሞ እንዲበረታ ምክንያት ሆኗል። ግድያው የተፈጸመበት ቅጽበትን የሚያሳይ ቪዲዮ ወጥቷል። ምን ነበር የተከሰተው?

  9. የሚኒሶታውን ግድያ ተከትሎ ተቃውሞ የበረታባቸው ፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተዳደራቸው “ሁሉንም ነገር እንደሚገመግም” ተናገሩ

    የፌደራል የኢሚግሬሽን ኃይሎች ቅዳሜ ዕለት በሚሊያፖሊስ ከተማ የ37 ዓመት አሜሪካዊን መግደላቸውን ተከትሎ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደራቸው “ሁሉንም ነገር እንደሚገመግም” ገለጹ።

    ትራምፕ ለዎል ስትሪት ጆርናል ጋዜጣ በሰጡት ቃለ መጠይቅ፤ የፌደራል ኃይሎች በሂደት ከተማዋን ለቅቀው እንደሚወጡ አስታውቀዋል። የፀጥታ ኃይሎቹ ለቅቀው የሚወጡበትን ጊዜ በተመለከተ ግን ምንም አልተናገሩም።

    የጽኑ ህክምና ነርስ የሆነው ኤሌክስ ፕሬቲ ግድያን ተከትሎ እሁድ ዕለት በተለያዩ የአሜሪካ ከተሞች ተቃውሞዎች ቀጥለው ውለዋል። የሚኒሶታ ገዢው ቲም ዋልዝ አሜሪካ “የእጥፋት ነጥብ” ላይ እንደሆነች በመጥቀስ አስጠንቅቀዋል።

    በሳምንታት ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ በፌደራል ኃይሎች የተፈጸመውን ግድያ በተመለከተ የሚሰጡ ማብራሪያዎች እያከራከሩ ነው። የፌደራል እና የግዛቱ ባለሥልጣናትም በዚህ ምክንያት አዲስ መካረር ውስጥ ገብተዋል።

    ዎል ስትሪት ጆርናል ባወጣው ዘገባ፤ ዶናልድ ትራምፕ የፀጥታ ኃይሎቹ የወሰዱት እርምጃ ትክክለኛ ነው ብለው ያምኑ እንደሆነ ሁለት ጊዜ በቀጥታ ጥያቄ እንዳቀረበ አስፍሯል። ምላሽ ለዚህ ጥያቄ ምላሽ ሲሰጡ “እየተመለከትነው ነው፤ ሁሉንም ነገር እየገመገምን ነው፤ ውሳኔ ላይ እንደርሳለን” ብለዋል።

    "ማንኛውንም ዓይነት ተኩስ አልወድም፤ አልወደውም" ሲሉ ለጋዜጣው ተናግረዋል።

    አክለውም "ነገር ግን አንድ ሰው በጣም ኃይለኛ እና ሙሉ በሙሉ ጥይት የተሞላ ሽጉጥ፣ እንዲሁም ሁለት ጥይት የተሞሉ ተጨማሪ ካርታዎችን ይዞ ወደ ተቃውሞ ሲወጣ ደስ አይለኝም። ይህም ቢሆን በበጎ የሚታይ አይደለም" ብለዋል።

    የትራምፕ አስተዳደር ከተወሰኑ ታዋቂ ሪፐብሊካኖች ጭምር ጫና እየደረሰበት ነው። ሪፐብሊካኑ በክስተቱ ዙሪያ ሰፊ ምርመራ እንዲካሄድ በመጠየቅ ተቃዋሚዎቹን ዴሞክራቶች ተቀላቅለዋል።

    ትራምፕ ለጋዜጣው በሰጡት ቃል “የሆነ ጊዜ ላይ እንወጣለን። ጨርሰናል፤ አስገራሚ ሥራ አከናውናል” ሲሉ የፌደራል ኃይሎች ከሚኒያፖሊስ እንደሚወጡ ጠቁመዋል።

  10. የማርበርግ ቫይረስ ሙሉ በሙሉ ከኢትዮጵያ “መወገዱን” የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ

    ከሦስት ወራት በፊት በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጂንካ ዞን የተገኘው የማርበርግ ቫይረስ ሙሉ በሙሉ በቁጥጥር ሥር መዋሉን የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

    ቫይረሱ ከኢትዮጵያ “ጨርሶ እንደተወገደ” ይፋ የተደረገው በዓለም የጤና ድርጅት አሠራር መሠረት ላለፉት “42 ተከታታይ ቀናት ምንም አዲስ ታካሚ ባለመመዝገቡ” እንደሆነ የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስ ዳባ ገልጸዋል።

    የጤና ሚኒስቴር በሽታው በቁጥጥር ሥር መዋሉን ይፋ ያደረገው ዛሬ ሰኞ ጥር 18/2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከተማ እያካሄደ ባለው የማብሰሪያ መርሃ ግብር ላይ ነው።

    በዝግጅቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስ ዳባ፤ “ምንም እንኳ የዘጠኝ ወገኖቻችንን ሕይወት ብናጣም፤ ወረርሽኙ ሊያደርስ ከሚችለው ከባድ እና ውስብስብ ችግር አንጻር አገር እና ሕዝባችንን መታደግ ችለናል። እንኳን ደስ አላችሁ፤ እንኳን ደስ አለን” ሲሉ ወረርሽኙ በቁጥጥር ሥር መዋሉን አብስረዋል።

    የጤና ሚኒስቴር የማርበርግ ቫይረስ ለመጀመሪያ ጊዜ ኢትዮጵያ ውስጥ መገኘቱን ይፋ ያደረገው በኅዳር መጀመሪያ ነበር። በእነዚህ ጊዜያት ውስጥ 14 ሰዎች በበሽታው እንደተያዙ በላብራቶሪ ምርመራ የተረጋገጠ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ ዘጠኙ ሕይወታቸው አልፏል። አምስት ሰዎች ደግሞ አገግመዋል።

    በሽታው በኢትዮጵያ ሲገኝ ለመጀመሪያ ጊዜ እንደነበር ያስታወሱት የጤና ሚኒስትሯ፤ “በወቅቱ ከበሽታው ባህሪ ከአደገኝነቱ አኳያ ክስተቱ ለሁላችንም አሳሳቢ ነበር” ብለዋል።

    የማርበርግ ወረርሽኝ በቁጥጥር ሥር መዋሉ የተበሰረው የዓለም የጤና ድርጅት እንዲሁም የኢትዮጵያን የወረርሽኝ ቅኝት እና ምላሽ መመሪያ አሠራር መሠረት በማድረግ እንደሆነ ዶ/ር መቅደስ አስረድተዋል።

    “የመጨረሻው ታካሚ በላብራቶሪ ከበሽታው ነጻ መሆኑ ከተረጋገጠበት 42 ተከታታይ ቀናት ምንም ዓይነት አዲስ ታካሚ ባለመመዝገቡ ወረርሽኑ በቁጥጥር ሥር መዋሉን በይፋ በምናደርግበት የዛሬው ቀን ላይ ደርሰናል” ብለዋል።

    “ይህ 42 ቀን ዝም ብሎ የሚቆጠር ቁጥር ወይም ቀን አይደለም” ያሉት ሚኒስትሯ፤ “ከቁጥሩ ጀርባ ስጋትን በትጋት የቀለበስንበት፣ የብርቱ ጥረት ስኬት የተገኘበት” ወቅት እንደሆነ አንስተዋል።

    “የጤና ባለሙያዎቻችን፣ የጤና እንክብካቤ ሠራተኞቻችን የማርበርግ ቫይረስ ወይም ወረርሽኙን ለመቋቋም ሕዝባችን ለስጋት እና ከሕልፈተ ሕይወት ለመታደግ ራሳቸውን፣ የማይተካ ሕይወታቸውን ጭምር በመስጠት ሌት ተቀን ከሕዝብ ጎን በመቆም ከቫይረሱ ጋር ፊት ለፊት ተጋፍጠው አሸንፈዋል” ሲሉ አመስግነዋል።

    በጂንካ ከተማ የተገኘው የማርበርግ ቫይረስ በቅድሚያ የተሰራጨው ከመጀመሪያው ታማሚ ጋር ግንኙነት በነበራቸው የቤተ ክርስቲያን አባቶች ዘንድ ነበር። ቢቢሲ የመጀመሪያውን ታማሚ እና የቫይረሱን ስርጭት በተመለከተ ከዚህ ቀደም ያወጣው ዘገባ ለማንበብ ይህንን ሊንክ ይጫኑ፦ ማርበርግ ቫይረስ: የመጀመሪያው ታማሚ እና ሦስት መሪዎቿን ያጣችው የጂንካ ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን

  11. በአሜሪካ በተከሰተ ከባድ የበረዶ አውሎ ነፋስ ቢያንስ ሰባት ሰዎች ሲሞቱ 800 ሺህ ነዋሪዎች ኤሌክትሪክ ተቋረጠባቸው

    በአሜሪካ በተከሰተ አደገኛ የበረዶ አውሎ ነፋስ ምክንያት ቢያንስ የሰባት ሰዎችን ሕይወት እንዳለፈ እና በመቶ ሺዎች ሚቆጠሩ ቤቶች ከኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ውጪ እንዲሆኑ እንዳደረገ ተገለጸ።

    በቴክሳት እና ኒው ኢንግላድ መካከል በሚገኙ አካባቢዎች ባለው "ለሕይወት አስጊ" የሆነ የአየር ሁኔታ የተነሳ ቤቶች እና መንገዶች እንዲዘጉ እንዲሁም በረራዎች እንዲሰረዙ መደረጉን የአገሪቱ ብሔራዊ የአየር ሁኔታ አገልግሎት አስታውቋል።

    በሉዊዚያና ግዛትቢያንስ ሁለት ሰዎች በከባድ ቅዝቃዜ (hypothermia) ምክንያት የሞቱ ሲሆን በቴክሳስ፣ በቴነሲ እና በካንሳስ ግዛቶችም ከአውሎ ነፋሱ ጋር የተያያዙ ሌሎች ሞቶች ተመዝግበዋል።

    የኤሌክትሪክ መቋረጥን የሚመዘግበው ድረ ገጽ (poweroutage.us) ያወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ እስከ እሁድ ከሰዓት ድረስ ብቻ ከ800 ሺህ በላይ ቤቶች የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ተቋርጦባቸዋል። ‘ፈላይትአዌር’ ያወጣው መረጃ ደግሞ ከ11,000 በላይ በረራዎች መሰረዛቸውን አሳይቷል።

    ሰፊ የሆነ ከባድ በረዶ፣ የበረዶ ዝናብ እንዲሁም የቀዘቀዙ የዝናብ ጠብታዎች እንዳረፉ ወዲያውኑ ወደ በረዶነት የሚቀየሩበት "ፍሪዚንግ ሬይን" የተባለው አደገኛ ክስተት በዚህ ዓይነት ሁኔታ ለቀናት ሊቆዩ ይችላሉ።

    አየር ሁኔታው ያስከተለው አውሎ ነፋስምወደ 180 ሚሊዮን የሚጠጉ አሜሪካውያንን ወይም ከአገሪቱ ሕዝብ ከግማሽ በላዩ ላይ ተጽዕኖ ሊያደርግ ይችላል።

    የኒው ዮርክ ክፍለ ግዛት ገዢ ካቲ ሆቹል ነዋሪዎች ከቤት እንዳይወጡ እና ከመንገዶች እንዲርቁ አስጠንቅቀዋል።

    የአየር ሁኔታ ባለሙያዎች በበኩላቸው አውሎ ነፋሱ ከሚፈጥራቸው አደጋዎች ዋነኛው የበረዶ ክምር እንደሆነ አስጠንቅቀዋል። ክምሩ ዛፎችን የመስበር፣ የኤሌክትሪክ መስመሮችን የመጣል እና መንገዶችን ለአደጋ የማጋለጥ አቅም እንዳለው ገልጸዋል።

  12. ቬንዙዌላ በርካታ የፖለቲካ እስረኞችን መፍታቷን የሰብአዊ መብቶች ተሟጋች ቡድን አስታወቀ

    ቬንዙዌላ በአሜሪካ የደረሰባትን ጫና ተከትከሎ ቢያንስ 80 የፖለቲከኛ እስረኞችን መልቀቋን የአገሪቱ ዋነኛ የሰብአዊ መብቶች ተሟጋች ቡድን አስታወቀ።

    ‘ፎሮ ፔናል’ የተባለው ተሟጋች ቡድን ኃላፊ የሆኑት አልፍሬዶ ሮሜሮ፤ ቅዳሜ ዕለት በመላ አገሪቱ ከሚገኙ የተለያዩ እስር ቤቶች የተለቀቁትን ሰዎች ማንነት እያጣሩ እንደሆነ ተናግረዋል። ሌሎች ታሳሪዎችም ሊፈቱ የሚችሉበት ዕድል መኖሩን ጠቁመዋል።

    አሜሪካ በወታደራዊ ኦፕሬሽን የቬንዙዌላውን ፕሬዝዳንት በመያዝ፤ በዕፅ ዝውውር ወንጀል በኒው ዮርክ የሚገኝ ፍርድ ክስ ካቀረበች ወዲህ አገሪቱ ታሳሪዎችን እየለቀቀች ነው።

    አርብ ዕለት የቬንዙዌላ ጊዜያዊ ፕሬዝዳንት ዴልሲ ሮድሪጌዝ ከ600 በላይ እስረኞች መፈታታቸውን ተናግረዋል። ተሟጋች ቡድኑ ‘ፎሮ ፔናል’ ግን ቁጥሩ እንደተጋነነ በመግለጽ ተችቷል።

    የቡድኑ ኃላፊ ሮሜሮ የታሳሪዎቹን መፈታት ይፋ ያደረጉት በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባጋሩት ልጥፍ ነው። ከነሐሴ 2024 አንስቶ በዋና ከተማዋ ካራካስ በሚገኝ እስር ቤት ውስጥ ታስሮ የነበረውን የተሟጋች ቡድኑ ባልደረባ የሆነው ኬኔዲ ቴጄዳ ፎቶም አጋርቷል።

    የተፈቱት ሰዎች ቁጥር ከ80 በላይ ሊሆን እንደሚችል በኤክስ ገጻቸው የገለጹት የቡድኑ ጠበቃ የሆኑት ጎንዛሎ ሂሚኦብ፤ ትክክለኛውን ቁጥር “እያጣራን ነው” ብለዋል።

    ቅዳሜ ዕለት ተጨማሪ ሰዎች ከመለቀቃቸው አስቀድሞ ባሉት ቀናት 156 ታሳሪዎች እንደተፈቱ ቡድኑ አረጋግጧል።

    ባለፉት ሳምንታት ከተለቀቁት ሰዎች ውስጥ አብዛኛዎቹ የተመሠረተባቸው ክስ እንዳልተቋረጠ የሰብአዊ መብቶች ተሟጋች ቡድኑ ከዚህ ቀደም ገልጾ ነበር።

    ክሱ አለመቋረጡ ወደ አደባባይ ወጥተው እንዳይናገሩ የሚያደርግ የሕግ ሸምቀቆ ውስጥ እንዳስገባቸውም አስታውቋል።

  13. በአሜሪካ ሚኒሶታ ሰልፍ እና ተቃውሞ ሲበረታ፤ ገዢው ትራምፕ የፌደራል ኃይሎችን ከግዛቱ እንዲያስወጡ ጠየቁ

    የአሜሪካ የፌደራል ኃይሎች በቀናት ልዩነት ቅዳሜ ዕለት ሁለተኛ ሰው መግደላቸውን ተከትሎ፤ ሚኒሶታ ውስጥ የምትገኘው ሚኒያፖሊስ ከተማ ነዋሪዎች እና አመራሮች ከፌደራል የጸጥታ አካላት ጋር መጋጨት ቀጥለዋል።

    የሚኒሶታ ገዢ ቲም ዋልዝ፤ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሚኒሶታ ውስጥ ያሰማሯቸውን “3,000 ያልሰለጠኑ ኃይሎች” እንዲያስወጡ ጠይቀዋል።

    ቅዳሜ ዕለት ከፌደራል ኃይል በተተኮሰ ጥይት የተገደለው አሌክስ ፕሪቲ የተባለው ግለሰብ የጽኑ ሕክምና ክፍል ነርስ እንደነበር ተገልጿል። የሚኒያፖሊስ ከተማ ነዋሪዎች የ37 ዓመቱን አሜሪካዊ ግድያ በመቃወም ሰልፍ ወጥተዋል።

    ሰልፈኞቹ መጀመሪያ ላይ ከጸጥታ ኃይሎች ጋር ተጋጭተው የነበረ ቢሆንም ኋላ የተደረጉት ተቃውሞዎች ግን ሰላማዊ ሆነው ቀጥለዋል። ነዋሪዎች ከሰልፍ እና ተቃውሞው በተጨማሪ መንገዶች ላይ ሟቹን ግለሰብ የሚዘክሩ መታሰቢያዎችን እያኖሩ ነው።

    የሚኒሶታ ግዛት እና የፌደራል ባለሥልጣን የግለሰቡን ሞት በተመለከተ በጋዜጣዊ መግለጫዎች የሚሰጧቸው ማብራሪያዎች አንዳቸው ከሌላው ጋር የሚጣረሱ ናቸው።

    ሟቹ ግለሰብ ይዞት ነበር ከተባለው ሽጉጥ ጋር በተያያዘም የመሣሪያ መያዝ መብት ጉዳይ የሕግ አውጪዎችን አቋም ከፋፍሏል። የአሜሪካ የአገር ውስጥ ደኅንነት ሚኒስትር የሆኑት ክሪስቲ ኖም ፕሪቲ፤ ግለሰቡ የተተኮሰበት ሽጉጥ "እያወዛወዘ" ስለነበር ነው ሲሉ ከስሰዋል።

    ሽጉጡ በሕጋዊ መንገድ የተመዘገበ እንደሆነ የሚናገሩት የሚኒሶታ ግዛት ባለሥልጣናት ግን፤ ሟቹ መሣሪያውን እያወዛወዘ እንዳልነበረ እና የፌደራል ኃይሎች የተኮሱበት ሽጉጡን ከወሰዱ በኋላ መሆኑን ገልጸዋል።

    በድርጊቱ ውስጥ የተሳተፉት የፌዴራል ኃይሎች አሁንም በሥራ ላይ ቢሆኑም ለደኅንነታቸው ሲባል ከሚኒያፖሊስ እንዲወጡ መደረጉን የድንበር ጥበቃ አዛዥ የሆኑት ግሬግ ቦቪኖ ተናግረዋል። የግለሰቡን ሞት በሚያሳዩት ቪዲዮዎች ላይ የታየውን ሁኔታ በሚመለከት ግን ቀጥተኛ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥበዋል።

    የሚኒሶታ ገዢ ቲም ዋልዝ በበኩላቸው የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ያሰማሯቸውን "3,000 ያልሰለጠኑ ኃይሎች" ከግዛቱ እንዲያስወጡ በድጋሚ ጥሪ አቅርበዋል።

    "እኛ በሰላም እናምናለን፤ [የፌደራል ኃይሎች] ሌላ ሰው ከመግደላቸው በፊት ዶናልድ ትራምፕ እነዚህን 3,000 ያልሰለጠኑ ኃይሎች ማስወጣት እንዳለባቸው እናምናለን" ብለዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ በአንጻሩ የሚኒሶታ ባለሥልጣናት ግዛቱ ውስጥ የሚካሄደውን የፋይናንስ ማጭበርበር ምርመራ ጋር በተያያዘ "የወንጀል ሽፋን" ውስጥ ተሳትፈዋል ሲሉ ያለማስረጃ ከስሰዋል። የዋይት ሃውስ የፕሬስ ፀሐፊ ካሮሊን ሌቪትም የሚኒሶታ ገዢ "ዋልዝ ሁከትን ይፈልጋል" ወንጅለዋል።