ዳግማዊት ንግሥት ኤልዛቤጥ እና አፍሪካ በምስል

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ንግሥት ኤልዛቤጥ ዳግማዊት በንግሥና ዘመናቸው ከ20 በላይ የአፍሪካ አገራትን ጎብኝተዋል። ንግሥቲቱ በሥልጣን ዘመናቸው በርካታ የአፍሪካ አገራት ከብሪታኒያ ቅኝ አገዛዝ ነጻ በመውጣት የራሳቸውን አስተዳደር ሲመሰርቱ አይተዋል።
የቀድሞዎቹን በብሪታኒያ ሥር የነበሩ በርካታ አገራትን በአንድ ያስተሳሰረውን የኮመንዌልዝ አገራት ማኅበርንም መርተዋል።
የአፍሪካ አገራት ከቅኝ አገዛዝ ነጻ ከወጡ በኋላ ከብሪታኒያ ንጉሣዊ ሥርዓት ጋር የቀረበ፣ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ የተወሳሰበ ግንኙነት ነበራቸው።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ንግሥት ኤልዛቤጥ ልዕልት በነበሩበት ጊዜ ደቡብ አፍሪካ ኬፕ ታውን ውስጥ 21ኛ ዓመት የልደት በዓላቸው ሲከበር የኮመንዌልዝ አገራትን ለማገልገል ቃል ገብተው ነበር።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ልዕልት ኤልዛቤት እአአ በ1952 ከባለቤታቸው ከኤደንብራው አልጋ ወራሽ ጋር ኬንያ ውስጥ ጉብኝት እያደረጉ። ይህ ፎቶ በተነሳበት ዕለት የአባታቸውን ንጉሥ ጆርጅ አምስተኛ ሞት የሰሙ ሲሆን ወዲያውኑም ንግሥት ሆኑ።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በ1956 ንግሥቲቱ ለመጀመሪያ ጊዜ ናይጄሪያን ጎብኝተው በዚህ ፎቶ ሌጎስ ውስጥ ከናይጄሪያው ባሕላዊ መሪ ኦባአ ዴንጄ ሁለተኛ ጋር ይታያሉ። ንግሥቲቱ በርካታ የአገሪቱን ግዛቶች ጎብኝተዋል።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ዳግማዊት ንግሥት ኤልዛቤጥ የአፍሪካ ፀረ ቅኝ ግዛት ንቅናቄ መሪ ከሆኑት እና የጋና የመጀመሪያው ፕሬዝዳንት ከነበሩት ክዋሜ ንክሩማህ ጋር ሲደንሱ። ይህ ፎቶ ጋና ነጻ አገር ከሆነች ከአራት ዓመት በኋላ በ1961 የተነሳ ነው።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ንግሥት ኤልዛቤጥ እና ባለቤታቸው ልዑል ፊሊፕ ኢትዮጵያን እአአ በ1965 በጎበኙበት ጊዜ ከአጼ ኃይለ ሥላሴ ጋር።
የጣሊያን ወረራ አብቅቶ ወደ መንበራቸው እስኪመለሱ ድረስ ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ በዩናይትድ ኪንግደም ቆይተው ነበር።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ንግሥቲቱ እአአ በ1965 ሱዳንን በጎበኙበት ጊዜ ከፕሬዝዳንት ኤል ቲጋኒ ኤል ማሂ ጋር በካርቱም አውሮፕላን ማረፊያ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ንግሥቲቱ እና የታንዛኒያው ፕሬዝዳንት ጁሊየስ ኔሬሬ እአአ በ1979። ከታንጋኒካ ነጻ መውጣት በኋላ ኔሬሬ ፀረ ብሪታኒያ እና ፀረ አውሮፓ አቋም ያራምዱ ነበር። ነገር ግን የዩናይትድ ኪንግደም መንግሥት በግጭት ውስጥ ባለው አካባቢ ኔሬሬ የማረጋጋት ሚና አላቸው ብሎ ያምን ነበር።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የዚምባብዌው ፕሬዝዳንት ሮበርት ሙጋቤ በአውሮፓውያኑ በ1994 ዘውዳዊ የክብር ማዕረግ በተሰጣቸው ጊዜ።
ነገር ግን ሙጋቤ በጀመሩት የመሬት ባለቤትነት ፕሮግራማቸውና በሰብአዊ መብት ጉዳዮች ከዩናይትድ ኪንግደም መንግሥት ጋር ፍጥጫ ውስጥ ገብተው ከኮመንዌልዝ ማኅበር ወጥተዋል። የተሰጣቸውም የክብር ማዕረግ ተነሳ።

የፎቶው ባለመብት, AFP
ንግሥት ኤልዛቤጥ እና የደቡብ አፍሪካው የመጀመሪያ ጥቁር ፕሬዝዳንት ኔልሰን ማንዴላ የቀረበ ወዳጅነት እንዳላቸው ይነገራል።
ንግሥቲቱ ለፕሬዝዳንት ማንዴላ ደብዳቤ ሲጽፉ “የልብ ወዳጅህ፣ ኤልዛቤጥ” በማለት ከቅርበታቸው የተነሳ “ማንዴላ” ሲሉ ይጠሯቸው ነበር።
ማንዴላም የንጉሣውያንን ሥርዓት ባልጠበቀ ሁኔታ ንግሥቱቱን “ኤልዛቤጥ” በሚል ነበር የሚጠሯቸው።

የፎቶው ባለመብት, EPA
ንግሥቲቱ በ2003 (እአአ) ለሁለተኛ ጊዜ ናይጄሪያን ጎብኝተዋል። ንግሥት ኤልዛቤጥ እና ፕሬዝዳንት ኦሉሴጎን ኦባሳንጆ አቡጃ ውስጥ በተካሄደው የኮመንዌልዝ አገራት ስብሰባ መክፈቻ ላይ በተገኙበት ወቅት የተነሳ ፎቶ።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በብሪታኒያ ታሪክ ለረጅም ጊዜ በንግሥና ላይ የቆዩት ንግሥት ኤልዛቤጥ በ2007 (እአአ) ወደ አፍሪካ ባደረጉት የመጨረሻ ጉዟቸው፣ በአፍሪካ በሥልጣን ላይ ለረዥም ጊዜ ከቆዩት መሪዎች መካከል አንዱ የሆኑትን የኡጋንዳውን ፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቪኒን አግኝተዋል።
ንግሥቲቱ በ1954 ወደ አፍሪካ የመጀመሪያቸውን ይፋዊ ጉብኝት ባደረጉበት ጊዜ ኡጋንዳን ጎብኝተው ነበር።












