በግዴታ ከዩናይትድ ኪንግደም ወደ አፍሪካ ተወስዶ በማደጉ "ዕድለኛ ነኝ" የሚለው ወጣት

ማርክ ዊልበርፎርስ ለንደን እያለ

የፎቶው ባለመብት, Mark Wilberforce

16 ዓመቴ ነበር። እናቴ ለእረፍት ከዩናይትድ ኪንግደም ወደ ጋና እንደምንሄድ ስትነግረኝ አንዳችም ጥርጣሬ አልገባኝም ነበር።

ሁሉም ነገር ፈጣን ነበር። ብዙም ያልታሰበበት የአጭር ጊዜ እርፍት ነበር የታቀደው። ይህ የእኔ ሃሳብ ብቻ ሊሆን ይችላል።

አንድ ወር ከቆን በኋላ ጉዱን አፍረጠረጠችው። እስካልተሻሻልኩ እና ትምህርቴን ለመቀጠል የሚያስችለኝ በቂ የሁለተኛ ደረጃ መልቀቂያ ፈተና ውጤት እስካሳካ ወደ ለንደን እንደማልመለስ ነገረችኝ።

ይህ ሁኔታ በቅርቡ ለትምህርት ወደ ጋና በመላኩ ምክንያት ወላጆቹን ለንደን በሚገኝ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የከሰሰው ብሪቲሽ-ጋናዊ ታዳጊ ጋር ተመሳሳይ ታሪክ ነበር።

ወላጆቹ የ14 ዓመቱ ልጃቸው "እንደሌላ ጥቁር ታዳጊ በለንደን ጎዳናዎች ላይ በስለት ተወግቶ ሲሞት" ማየት ባለመፈለጋቸው ከዚህ ውሳኔ መድረሳቸውን ለፍርድ ቤት ተናግረዋል።

እአአ በ1990ዎቹ አጋማሽ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት መምህር የነበረችው እናቴ በተመሳሳይ ስጋቶች እዚህ ውሳኔ ላይ ደርሳለች።

በለንደን ብሬንት ውስጥ ከሚገኙት ሁለት የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተባረርኩ። ምክንያቱ ደግሞ ጥሩ ካልሆኑ ሰዎች ጋር በመታየቴ እና ወደ አደገኛ መንገድ እየሄደ ነው በሚል ነው።

በወቅቱ የቅርብ ጓደኞቼ የነበሩት በጦር መሳሪያ በታገዘ ዝርፊያ ምክንያት እስር ቤት ገቡ። ለንደን ብቆይ ኖሮ በእርግጠኝነት አብሬያቸው እስር ቤት እገባ ነበር።

ወደ ጋና መላኬም የእስር ቅጣት ሆኖ ተሰማኝ።

በፍርድ ቤት ወላጆቹን ከስሶ "በሲኦል ውስጥ እየኖረ" እንደሚሰማው ከተናገረው ታዳጊ ጋር በተወሰነ ደረጃ እስማማለሁ።

21 ዓመት ሲሞላኝ እና እናቴ ያደረገችው ነገር ሳስበው መልካም ነገር እንደሆነ ተገነዘብኩ።

በለንደን ፍርድ ቤት ወላጆቹን ከስሶ ከተረታው ታዳጊ በተቃራኒ ጋና ወደሚገኝ አዳሪ ትምህርት ቤት አልተማርኩም።

እናቴ ሁለቱ የቅርብ ወንድሞቿ እንዲንከባከቡኝ አደረገች።

መጀመሪያ የነበርኩት የተባበሩት መንግሥታት የቀድሞ የአካባቢ ጥበቃ ባለሙያ ከነበረው ከአጎቴ ፊፊ ጋር በዋና ከተማዋ አክራ አቅራቢያ በምትገኝ ዳንሶማን በምትባል ከተማ ነበር።

የአኗኗር ዘይቤው ልዩነት በጣም ከባድ ነበር። ለንደን እያለሁ የራሴ መኝታ ክፍል፣ የልብስ ማጠቢያ ማሽን ነበረኝ። በግዴለሽነት ብጠቀምበትም በተወሰነ ደረጃ የነጻነት ስሜት ነበረኝ።

አክራ የሚገኝ ትምህርት ቤት አቅራቢያ ሰዎች ሲተላለፉ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

በጋና ያለው ሁኔታ ግን ከዚህ የተለየ ነው። ግቢውን ለመጥረግ እና ጭቃ የማያጣውን የአጎቴን መኪና እና የአክስቴ መኪና ለማጠብ ንጋት 11፡00 ሰዓት ከእንቅልፌ እነሳለሁ።

ኋላ ላይ ይህቺን የአክስቴን መኪና ሰርቄ ወጥቼ ጉድ ሆኛለሁ።

በትክክል መኪና ማሽከርከር አልችልም ነበር። መኪናዋን ይዤ ወጥቼ ከአንድ ከባድ ወታደር መርሴዲስ ጋር ተጋጨሁ።

ለማምለጥ ሞከርኩ። ወታደሩ ግን ያዘኝ። ቀደም ሲል ሰዎች ግብተው ይጠፉበት ወደ ነበረው በርማ ወደ ተሰኘው ታዋቂው የጦር ሰፈር እንደሚወስደኝ ዛተ።

ያ በግድየለሽነት ያደረግኩት የመጨረሻው ነገር ነው።

በጋና የተማርኩት ተግሳጽ ብቻ አልነበረም፤ አመለካከትም ጭምር ነበር።

ሕይወት ቀላል ነው ብዬ እንዳሰብኩ የገባኝ ጋና ስደርስ ነው።

ልብስ በእጅ ማጠብ እና ከአክስቴ ጋር ምግብ ማዘጋጀት ጥረቱን እንዳደንቅ አድርጎኛል።

ምግብን ጨምሮ ጋና ውስጥ ሁሉም ነገር ትዕግስት ይጠይቃል። ማይክሮዌቭ አልነበሩም፤ ፈጣን ምግብም አይዘጋጅም።

ባህላዊውን ሊጥ የሚመስለውን ፉፉ የተባለ ምግብ ማዘጋጀት በጣም አድካሚ ነው። የበሰለውን ያምስ ወይም ካሳቫ በሙቀጫ መውቀጥን ይጠይቃል።

በወቅቱ እንደ ቅጣት ቢሰማኝም አልፎ ስመለከተው ችግርን የመቋቋም አቅምን እየገነባሁ ነበር።

አጎቶቼ መጀመሪያ ላይ እንደጋና ኢንተርናሽናል ትምህርት ቤት ወይም ኤስኦኤስ-ሄርማን ጄሜኒየር ኢንተርናሽናል ኮሌጅ ባሉ ስመ ገናና ትምህርት ቤቶች ሊያስገቡኝ አስበው ነበር።

ብልህ ነበሩ። ሁከት እና ብጥብጥ ለመፍጠር አዲስ ቡድን እንደማቋቋም ያውቁ ነበር።

ሟቹ አባቴ የተማረበት እና የመንግሥት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በሆነው በአክራ አካዳሚ በግል ለመማር ተመዘገብኩ። ብዙ ጊዜ ብቻዬን ወይም ከአነስያለ ቁጥር ካላቸው ተማሪዎች ተማርኩ።

ማርክ እና አጎቱ ጆጆ

የፎቶው ባለመብት, Sulley Lansah

ትምህርቱ በእንግሊዘኛ ነበረ የሚሰጠው፤ ከትምህርት ቤት ውጪ በዙሪያዬ ያሉት ሰዎች ብዙ ጊዜ የአገር ውስጥ ቋንቋዎችን ይናገሩ ነበር። ይህንንም ቀላል ሆኖ አግኝቼዋለሁ።

ለንደን እያለሁ ፋንቴ በተሰኘው የእናቴ ቋንቋ የስድብ ቃላትን መማር እወድ ነበር። አቀላጥፌ ግን አልናገርም።

በኋላ ወደ ቴማ ከተማ ሄድኩኝ። ከምወደው አጎቴ ጆጆ (የግብርና ባለሙያ ነው) ጋር ለመኖር ነበር የሄድኩት። እዚያም ቴማ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በግል ለመማር ተመዝግቤ ትምህርቴን ቀጠልኩ።

የጋና የትምህርት ሥርዓት ደረጃውን የጠበቀ አይደለም በማለት መነጋጋሪያ ከሆነው እና ወላጆቹን ከከሰሰው ታዳጊ በተቃራኒ ሆኖ አገኘሁት።

ምንም እንኳን አካሄዴ እና ውሎዬ ጥሩ ባይሆንም፤ ዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ የትምህርት ተሰጥኦ እንዳለኝ እቆጠር ነበር። ጋና ስሄድ ግን ትምህርቱ ከባድ ሆኖ አግኝቼዋለሁ። እኩዮቼ እንደ ሂሳብ እና ሳይንስ ባሉ ትምህርቶች በጣም ቀድመውኝ ነበር።

የጋና የተምህርት ሥርዓት ጥብቅ መሆኑ ከለንደን በበለጠ ጠንክሬ እንዳጠና ገፋፍቶኛል።

ውጤቱስ? አምስቱ የሁለተኛ ደረጃ ማለፊያ ፈተና ውጤቴ ሲ እና ከዚያ በላይ ሆነ። በአንድ ወቅት ይህ የማይቻል የሚመስል ነገር ነበር።

ከትምህርት ስኬቶች ባሻገር የጋና ማኅበረሰብ ከእኔ ጋር ለሕይወት ዘመኔ የሚቆይ እሴቶችን አጽርሶብኛል።

ታላላቆችን ማክበር ለድርድር የሚቀርብ አልነበረም። በኖርኩባቸው ሰፈሮች ሁሉ ታላላቆችህን ብታውቃቸውም ባታውቃቸውም ሰላም ትላቸዋለህ።

ጋና በሥርዓት እና በአክብሮት እንድኖር ብቻ ሳይሆን ፍርሃት አልባ አድርጎኛል።

በዚህ የለውጥ ሂደት ውስጥ እግር ኳስ ትልቅ ሚና ተጫውቷል። ጠጠር እና ድንጋይ የሞላባቸው ሜዳዎች ላይ ጎሎችን በእንጨት እና በገመድ በመሥራት እንጫወት ነበር።

በዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ በጥሩ መልኩ ከተያዙት ሜዳዎች ጋር አይወዳደሩም። በማላስበው መንገድ ግን አጠነከረኝ። በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሚጫወቱ ታላላቅ የእግር ኳስ ተጫዋቾች ከምዕራብ አፍሪካ መምጣታቸው ምንም አያስደንቅም።

ጋና ውስጥ እግር ኳስ የሚጫወቱ ታዳጊዎች

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

በጋና እልህ የሚቀላቀልበት አጨዋወት ክህሎትን ብቻ ሳይሆን የመቋቋም እና ፅናትን ይጠይቃል። በማይመቸው ሜዳ ላይ መውደቅ መነሳትን ይጠበቃል።

እሑድ እሑድ በባሕር ዳርቻ ላይ እግር ኳስ እጫወት ነበር። አጎቶቼ ቤተ ክርስቲያን ከመሄድ ይልቅ ቤት እንድቆይ የሚፈቅዱልኝ ጊዜ ጥቂት ስለነበር ብዙ ጊዜ አረፍዳለሁ።

የቤተ ከክርስቲያኑ ሥርዓት ለዘላለም የሚቆይ ይመስል ይረዝማል። ይህ ግን ጋና ይህ ፈሪሐ እግዚአብሔር ያላት አገር ስለመሆኗ ምስክር ተደርጎ ይታያል።

የመጀመሪያዎቹ 18 ወራት በጣም ከባድ ነበሩ። እገዳው፣ የቤት ውስጥ ሥራዎቹ እና ተግሳጾቹ ይከብዱ ነበር። ያናድድኝም ነበር።

ወደ ለንደን ለመመለስ ፓስፖርቴን ለመስረቅ ሞከርኩኝ። እናቴ ግን ቀድማኝ ትገኛለች። ፓስፖርቱን እንዳላገኘው ደብቃዋለች። ። ማምለጫ አልነበረኝም።

ምርጫዬ መላመድ ብቻ ነበር። ጋናን እንደ እስር ቤት ማየት አቆምኩ። እንደ ደስታዬ ቤት መቁጠር ጀመርኩ።

በለንደን በሚኖሩ ወላጆቻቸው ወደ ጋና የተላኩ እንደ እኔ ያሉ ጥቂት ሰዎችን አውቃለሁ።

በ1990ዎቹ በ17 ዓመቱ ለትምህርት ወደ አክራ የተላከው ማይክል አዶም ልምዱን "መራራ" ሲል ገልጿል። እስከ 23 ዓመቱ በጋና ቆይቶ አሁን ለንደን ውስጥ እየሠራ ይገኛል።

ዋናው ቅሬታው ብቸኝነቱ ነበር። ቤተሰቦቹን እና ጓደኞቹን ናፈቀ። ንዴት እና አልተረዱኝም የሚል ስሜት የሚፈጠሩባቸው ጊዜዎች ነበሩ።

ዋነኛው ምክንያት ደግሞ ወላጆቹ ለንደን እያሉ እሱንም ሆነ ወንድም እህቶቹን የትኛውንም የአገርኛውን ቋንቋ ስላላስተማሯቸው ነው።

ይህም ለመጀመሪያዎቹ ሁለት ዓመታት ተኩል ባዳ ሆኖ እንዲሰማው አድርጎታል። ለምሳሌ የውጭ ዜጋ ተደርጎ በመቆጠሩ ምክንያት የዋጋ ጭማሪዎች ይደረጉበት ነበር።

"በሄድኩበት ቦታ ሁሉ ከሌላ ሰው ጋር ለመሄዴ እመርጥ ነበር" ይላል።

በኋላ ላይ ግን ቋንቋውን አቀላጥፎ መናገር ቻለ። አወንታዊው ነገርም ከአሉታዊ ጎኑ እንደሚበልጥ አየ። "ራሴን እንድችል አድርጎኛል" ብሏል።

"የጋና ቆይታዬ በሳል አድርጎኛል። በተሻለ ሁኔታ ለውጦኛል። እንደ ጋናዊ ስለ ባህሌ እና ስለቤተሰብ ታሪክ ያለኝን ግንዛቤ አጠናክሮልኛል።"

ማርከክ እና እናቱ ፔሰንስ ዊልበርፎርስ

የፎቶው ባለመብት, Mark Wilberforce

ይህ እኔንም ያስማማኛል። በሦስተኛው ዓመት ከባህሉ ፍቅር ያዘኝ። የሁለተኛ ደረጃ ፈተናን ካለፍኩ በኋላም ለሁለት ተጨማሪ ዓመታት ያህል ቆየሁ።

የአካባቢውን ምግብ ወደድኩት። ለንደን እያለሁ ስለምበላው ነገር አስቤ አላውቅም። በጋና ግን ምግብ ለሆድ ብቻ አልነበረም። እያንዳንዱ ምግብ የራሱ ታሪክ አለው። "ዋክዬ" ከተሰኘው ምግብ ፍቅር ይዞኝ ነበር።

ሙዚቃው፣ የሰዎች ፍቅር እና በማኅበረሰቡ ስሜት ተደስቻለሁ። ከአሁን በኋላ በጋና "ተጣብቄ" ብቻ አልነበርኩም፤ እያደግኩኝ ነበር።

እናቴ ፔሸንስ ዊልበርፎርስ በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይታለች። እሷ ከዓመታት በፊት ስላወሰነችው ውሳኔ በጥልቅ አስብ ነበር።

አድናኛለች። በጋና እንድቆይ ባታታልለኝ ኖሮ፣ የወንጀል ሪከርድ ያለብኝ ወይም በእስር ቤት የመሆን ዕድሌ በጣም ከፍተኛ ይሆን ነበር።

የቢቢሲ ራዲዮ 1 ኤክስትራን በተለማማጅነት ከመቀላቀሌ በፊት በ20 ዓመቴ በሰሜን ምዕራብ ለንደን ኮሌጅ ተማርኩኝ።

በሰሜን ምዕራብ ለንደን አብሬያቸው የማሳልፋቸው ሰዎች ያገኘሁትን ሁለተኛ ዕድል አላገኙም።

ጋና አስተሳሰቤን፣ ዕሴቶቼን እና የወደፊት ሕይወቴን ቀይራለች።

እንደዚህ ዓይነት ልምድ ለሁሉም ሰው ላይሠራ ቢችልም ወደ ዩናይትድ ኪንግደም ስመለስ ወደ ማኅበረሰቡ ለመቀላቀል የሚያስፈልገኝን ትምህርት፣ ተግሳጽ እና ክብር ሰጥቶኛል።

ለዚያም ለእናቴ፣ ለአጎቶቼ እና ላዳነችኝ አገር የዘላለም ውለታ አለብኝ።