እስራኤል በጋዛ ላይ የምታካሂደውን ዘመቻ አጠንክራ እንደምትቀጥል አስታወቀች

የእስራኤሉ የመከላከያ ሚኒስትር ዮአቭ ጋላንት የአገራቸው ሠራዊት በጦርነቱ የሚያካሂደው ዘመቻ ያለበት ደረጃ “መቀየሩን” በመግለጽ፣ “ተጨማሪ መረጃ አስኪሰጥ ድረስ” ዘመቻው ይቀጥላል ብለዋል። አርብ ምሽት ሠራዊቱ በወሰደው እርምጃ “የጋዛ ምድር ተንቀጥቅጣለች” በማለት የመከላከያ ሚኒስትሩ ለአንድ ቴሌዥን ጣቢያ ተናግረዋል።

የቀጥታ ሽፋን

  1. እስራኤል በጋዛ ላይ የምታካሂደውን ዘመቻ አጠንክራ እንደምትቀጥል አስታወቀች

    የእስራኤል ኤፍ16 ቦምብ ጣይ ጀት

    የፎቶው ባለመብት, Israeli Defence Forces (IDF

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል ኤፍ16 ቦምብ ጣይ ጀት

    የእስራኤሉ የመከላከያ ሚኒስትር ዮአቭ ጋላንት የአገራቸው ሠራዊት በጦርነቱ የሚያካሂደው ዘመቻ ያለበት ደረጃ “መቀየሩን” በመግለጽ፣ “ተጨማሪ መረጃ አስኪሰጥ ድረስ” ዘመቻው ይቀጥላል ብለዋል።

    አርብ ምሽት ሠራዊቱ በወሰደው እርምጃ “የጋዛ ምድር ተንቀጥቅጣለች” በማለት የመከላከያ ሚኒስትሩ ለአንድ ቴሌዥን ጣቢያ ተናግረዋል።

    “ከመሬት ላይ እና በአየር ጥቃት ፈጽመናል። በሁሉም ደረጃ የሚገኙ ሽብርተኞች ላይ በያሉበት ጥቃት ፈጽመናል።

    ለሠራዊታችን የተሰጠው መመሪያ ግልጽ ነው፡ ተጨማሪ መግለጫ አስከሚሰጥ ድረስ ዘመቻው ይቀጥላል” ብለዋል።

    ከአርብ ምሽት ጀምሮ በተጠናከረ ሁኔታ የእስራኤል ጦር ኃይል በጋዛ ላይ የሚያካሂደው ጥቃት ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን፣ ወደ ተወሰኑ የጋዛ ክፍሎች የእስራኤል ወታደሮች ዘልቀው መግባታቸው ተነግሯል።

  2. ከአርብ ሌሊት የእስራኤል ድብደባ በኋላ ጋዛ ላይ ከፍተኛ ውድመት ደረሰ

    ጋዛ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    እስራኤል ሌሊቱን ካካሄደችው ከፍተኛ ድብደባ በኋላ ጋዛ ላይ የደረሰውን ውድመት የሚያሳዩ ምስሎች እየወጡ ነው።

    እነዚህ ምስሎች በጋዛ ከተማ ከሚገኘው አል-ሻቲ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ አቅራቢያ የተነሱ ናቸው።

    እዚህ ገጽ ላይ ለማሳየት እጅግ አሰቃቂ ከሆኑ ምስሎች በአንዱ አንድ ጎልማስ የታዳጊ ልጅ አስክሬን ታቅፎ ሲያለቅስ ያሳያል።

    ምሽቱን እስራኤል ባደረሰችው ከባድ ጥቃት ምክንያት በሰው ላይ የደረሰው ጉዳት እስካሁን ግልጽ አይደለም። እስራኤል የስልክ ማማዎችን ዒላማ በማድረጓ የግንኙነት መስመሮች በጋዛ ተቋርጠዋል።

    የእስራኤል ሲም ካርዶች ያሏቸው ሰዎች ስልክ ብቻ እንደሚሰሩ እየወጡ ያሉ መረጃዎች ይጠቁማሉ።

    ጋዛ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    ጋዛ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    ጋዛ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

  3. የእስራኤል ጦር አሁንም ድረስ በጋዛ እንዳለ ተገለጸ

    ጋዛ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የእስራኤል ጦር ቃል አቀባይ ዳንኤል ሃጋሪ ጦራቸው እስከ ቅዳሜ ረፋድ በጋዛ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።

    ቃል አቀባዩ ቅዳሜ ረፋድ ላይ ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡ ሲሆን በመግለጫቸው የሚከተሉትን ተናግረዋል።

    • የእስራኤል መከላከያ ኃይል ወደ ሰሜናዊ ጋዛ የገባ ሲሆን የምድር ጦሩ በአየር ኃይሉ እና በባሕር ኃይሉ ድጋፍ ጥቃቶችን አድርሷል።
    • እስራኤል በዚህ ዘመቻ የሐማስ ከፍተኛ አዛዥን ገድላለች።
    • ዛሬ ምግብ፣ ውሃ፣ መድሃኒት የጫኑ የሰብዓዊ ድርጅቶች ተሸከርካሪዎች ወደ ጋዛ እንዲገቡ ይፈቀድላቸዋል
    • ሄዝቦላ ወደ እስራኤል ሚሳኤል መተኮሱን ተከትሎ የእስራኤል ጦር የአጸፋ እርምጃ ወስዷል።
    • እስካሁን ድረስ 311 የእስራኤል ወታደሮች መገደላቸውን ቃል አቀባዩ ተናግረዋል።
    • በሐማስ የታገቱትን ነጻ አውጥቶ ለቤታቸው ማብቃት የጦሩ ዋነኛ ዓላማ ነው።
  4. ከከባድ የቦምብ ድብደባ ምሽት በኋላ በጋዛ “ትምርስ” ሆኗል

    ጋዛ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በጋዛ የሚገኘው የቢቢሲ ዘጋቢ ሩሽዲ አቡአሉፍ ሰሜናዊ የጋዛ ሰርጥ ምሽቱን እስካሁን ታይቶ በማይታቅ መጠን ከፍተኛ ድብደባ አስተናግዳለች ብሏል።

    በዚህም ሰሜናዊ ጋዛ ሙሉ በሙሉ ትርምስ ውስጥ ገብታለች ብሏል።

    የእስራኤል ጦር ከአርብ ለቅዳሜ ንጋት የሚያካሂደውን ዘመቻ አስፋፍቶ 150 የሐማስ ዒላማዎችን መደብደቡን ገልጿል።

    ትናንት ምሽት የነበረው ጥቃት በአየር ኃይል፣ በታንክ እና በእግረኛ ኃይል የታጀበ ስለመሆኑ ተገልጿል።

    የእስራኤል አየር ኃይል የዘመቻዎች ኃላፊ ብርጋዲዬር ጀነራል ጊላድ ኬኢናን እንዳሉት ወደ 100 የሚጠጉ ተዋጊ ጀቶች በጋዛ ሰርጥ የሐማስ ዒላማዎችን ሲደበድቡ አድረዋል።

    የሐማስ ወታደራዊ ክንፍ የሆነው አል ቃሳም ብርጌድም በሰሜናዊ ጋዛ ሰርጥ ከእስራኤል የምድር ኃይል ጋር እየተዋጋ ስለመሆኑ መግለጫ ሰጥቷል።

  5. 100 ተዋጊ ጀቶች ጋዛን ሲደበድቡ ማደራቸውን ተገለጸ

    ጋዛ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የእስራኤል ባለስልጣናት አርብ ሌሊት ወደ 100 የሚጠጉ ተዋጊ ጀቶች በጋዛ ድብደባ ሲፈጽሙ ማደራቸውን አስታወቁ።

    የእስራኤል አየር ኃይል የዘመቻዎች ኃላፊ ብርጋዲዬር ጀነራል ጊላድ ኬኢናን እንዳሉት ወደ 100 የሚጠጉ ተዋጊ ጀቶች በጋዛ ሰርጥ የሐማስ ዒላማዎችን ሲደበድቡ አድረዋል።

    የእስራኤል ጦር የአየር ኃይሉን የዘመቻዎች ኃላፊን ጠቅሶ ባወጣው መግለጫ የአየር ጥቃቶቹ ዓላማ “የሐማስ እጅ ያረፈበትን እያንዳንዱ ነገር ማውደም ነው”።

  6. በጋዛ የስልክ እና የኢንተርኔት አግልግሎት ተቋረጠ

    በጋዛ የእስራኤል የተጠናከረው ድብደባ እንደቀጠለ ነው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በጋዛ የእስራኤል የተጠናከረው ድብደባ እንደቀጠለ ነው

    በጋዛ ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል መልኩ የግንኙነት መስመሮች ተቋርጠዋል።

    እንደ የፍልስጤም ቴሌኮሚኒኬሽን ኩባንያ ከሆነ የእስራኤል ጦር የስልክ ማማዎችን እና መስመሮችን መልሶ መላልሶ በመደብደቡ በጋዛ የስልክ እና የኢንተርኔት አግልግሎት ተቋርጧል።

    በግንኙነት መስመር መቋረጥ ምክንያት የሰብዓዊ ድርጅቶችና መገናኛ ብዙሃን በጋዛ ካሉ ሠራተኞቻቸው ጋር መገናኘት አለመቻላቸውን እየገለጹ ይገኛሉ።

  7. ሐማስ በሰሜናዊ ጋዛ ከእስራኤል ጦር ጋር እየተዋጋው ነው አለ

    የእስራኤል ጦር አባላት በሐማስ ጥቃት የወደመ ቤት ሲቃኙ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል ጦር አባላት በሐማስ ጥቃት የወደመ ቤት ሲቃኙ

    የሐማስ ወታደራዊ ክንፍ የሆነው አል ቃሳም ብርጌድ በሰሜናዊ ጋዛ ሰርጥ ከእስራኤል የምድር ኃይል ጋር እየተዋጋው ነው አለ።

    ቡድኑ በጋዛ ቤኢት ሃኑን እንዲሁም ቡሬጂ በተባሉ አካባቢዎች ውጊያ እየገጠመ መሆኑን ከመግለጽ ውጭ የሰጠው ተጨማሪ መረጃ የለም።

    ሐማስ በጋዛ ከእስራኤል እግረኛ ጦር ጋር የተኩስ ልውውጥ እያደረጉ ነው ያለው እስራኤል ዘመቻዎቿን ማስፋቷን ከገለጸች በኋላ ነው።

    የእስራኤል ጦር ቃል አቀባይ ለኒው ዮርክ ታይምስ እግረኛ ወታደሮች እና ታንኮች በጋዛ ሰርጥ ይገኛሉ ሲሉ ተናግረዋል።

  8. ቤተ-እስራኤላዊው አቨራ መንግሥቱ እና ለዓመታት በሐማስ እገታ ሥር ያሉ ሌሎች እስራኤላውያን

  9. እስራኤል የሐማስ የአየር ዘመቻ ኃላፊን ገደልኩ አለች

    የእስራኤል መከላከያ ኃይል የሐማስ ቡድን የአየር ላይ ጥቃቶች አዛዥ የሆነውን ኃላፊ ገደልኩ አለች።

    ግለሰቡ መስከረም 26 በተፈጸመው ጥቃት የሐማስ ተዋጊዎች በአየር እስራኤል ዘልቀው እንዲገቡ እቅድ መንደፉ ተገልጿል። ከዚህ በተጨማሪም አሴም አቡ ራካብ የተባለው ግለሰብ በድሮኖች የእስራኤል ወታደራዊ ኃይል ላይ የሚፈጸመውን ጥቃት ሲያቀናጅ ነበር ተብሏል።

    የእስራኤል ጦር አቡ ራካብ ገደልኩ ያለው ጦሩ ለሊቱን ባካሄደው የአየር ድብደባ ነው።

    እስራኤል ከፍተኛ የሐማስ አባልን ከደልኩ ስትል ይህ የመጀመሪያዋ አይደለም። ትናንት የእስራኤል ጦር የቡድኑን የድኅንነት ቢሮ ምክትል ኃላፊን መግደሉን አስታውቆ ነበር።

    ጦሩ ገደልኩት ያለው ሻዲ ባሩድ የተባለው ግለሰብ፣ የሐማስ የደኅንነት ቢሮ ምክትል ኃላፊ እንደነበረ እና በእስራኤል ላይ የተከፈተውን ድንገተኛ ጥቃት ዕቅድ ካወጡት መካከል አንዱ ነው ብሏል።

  10. አሜሪካ በሌባኖስ ያሉ ዜጎቿ ከአገር እንዲወጡ አዘዘች

    አሜሪካን የሚያወግዝ የተቃውሞ ሰልፍ በቤይሩት ተካሂዶ ነበር።

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, አሜሪካን የሚያወግዝ የተቃውሞ ሰልፍ በቤይሩት ተካሂዶ ነበር።

    አሜሪካ በሌባኖስ ያሉ ዜጎቿ በተቻላቸው ፍጥነት ከአገሪቱ እንዲወጡ አሳሰበች።

    የአሜሪካ መንግሥት በአካባቢው ያለውን የደኅንነት ሁኔታ መገመት አስቸጋሪ ስለሆነ የመንገደኞች አውሮፕላን አገልግሎት እስካለ ድረስ ዜጎች ከሌባኖስ እንዲወጡ ጠይቋል።

    ከሐማስ ጥቃት በኋላ መቀመጫውን ሌባኖስ ባደረገው የሺያ ሙስሊም ሚሊሻ ቡድን በሆነው ሄዝቦላ እና በእስራኤል ጦር መካከል የሚደረገው የተኩስ ልውውጥ በየዕለቱ እየጨመረ ይገኛል።

    ይህን ተከትሎ እስራኤል ሠራዊቷን እና ብረት ለበስ ወታደራዊ ተሸርካሪዎቿን ወደ ሌባኖስ ድንበር አስጠግታለች።

    በሌባኖስ ያለው ሁኔታ ያሳሰበው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚንስቴር መንግሥት ቀውስ በሚፈጠር ግዜ ዜጎችን ማውጣት ስለመቻሉ ምንም ማረጋገጫ ስለሌለ አሜሪካውያን ሁኔታዎች በፈቀዱ ወቅት ከሌባኖስ እንዲወጡ አሳስቧል።

  11. ጋዛ በከባድ ፍንዳታ እየተናጠች ባለበት የእስራኤል እግረኛ ሠራዊት ዘመቻውን እያሰፋ ነው

    ምሽት ላይ ጋዛን ያናወጠው ፍንዳታ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የምስሉ መግለጫ, ምሽት ላይ ጋዛን ያናወጠው ፍንዳታ

    አርብ ምሽት ጋዛ ሰርጥን ያናወጡ ከባድ ፍንዳታዎችን ተከትሎ የእስራኤል እግረኛ ሠራዊት የሚያካሂደውን “ዘመቻ እያሰፋ” መሆኑን የጦሩ ቃል አቀባይ ዳንኤል ሃጋሪ ተናገሩ።

    ለዚህ ጥቃት ምላሽ ነው በማለት ሐማስ ወደ እስራኤል ሮኬቶችን መተኮሱን መግለጹን የፈረንሳዩ የዜና ወኪል ኤኤፍፒ ዘግቧል።

    በተጨማሪም የእስራኤል ሠራዊትን በጋዛ ላይ “ተከታታይ ጥቃቶችን” እየፈጸመ መሆኑ ለኤኤፍፒ ገልጿል።

    ሠራዊቱ በጋዛ ላይ የሚያካሂደውን ወታደራዊ ዘመቻ እያስፋፋ መሆኑን መግለጹን ተከትሎ፣ የጋዛ ከተማ ነዋሪዎች ወደ ደቡብ የጋዛ ክፍል ለቀው እንዲወጡ አዟል።

    ረቡዕ ሌሊት የእስራኤል ታንኮች ወደ ሰሜናዊ ጋዛ ክፍል ዘልቀው በመግባት የተመረጡ እርምጃዎችን ወስደው እንደወጡ መገለጹ ይታወቃል።

    ይህም ጥቃት ሠራዊቱ በጋዛ ላይ ለሚያካሂደው የቀጣይ ምዕራፍ ዘመቻ አመቺ ሁኔታዎችን ለመፍጠር የታለመ መሆኑን የእስራኤል ጦር ኃይሎች ባለሥልጣናት ተናግረዋል።

    ሐማስ በእስራኤል ላይ የፈጸመውን ድንገተኛ ጥቃትን ተከትሎ የተቀሰቀሰው ጦርነት ነገ ቅዳሜ ሦስተኛ ሳምነቱን የሚይዝ ሲሆን፣ እስራኤል እግረኛ ሠራዊቷን ወደ ጋዛ ለማስገባት እየተዘጋጀች መሆኑ ሲነገር ቀይቷል።

  12. ዛሬ አርብ የተከሰቱ ዋና ዋና ነገሮች በአጭሩ

    ቴል አቪቭ ውስጥ በሚገኝ የመኖሪያ ሕንጻ ላይ የተፈጸመ የሮኬት ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ቴል አቪቭ ውስጥ በሚገኝ የመኖሪያ ሕንጻ ላይ የተፈጸመ የሮኬት ጥቃት

    በእስራኤል እና በጋዛ መካከል የሚካሄደው ጦርነት ዛሬ አርብ 20ኛ ቀኑን ይዟል። በግጭቱ ከሁለቱም ወገን በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ሕይወት ጠፍቷል። በዛሬው ዕለት ምን ዋና ዋና ነገሮች ተከሰቱ?

    • የሕክምና ሠራተኞች እንዳሉት በእስራኤሏ ከተማ ቴል አቪቭ ውስጥ በሚገኝ የመኖሪያ ሕንጻ ላይ በተፈጸመ የሮኬት ጥቃት ሦስት ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል።
    • መስከረም 26/2016 ዓ.ም. በተቀሰቀሰው ግጭት አስከ ዛሬ ድረስ ጋዛ ውስጥ 7,028 ሰዎች የተገደሉ መሆናቸውን የዓለም ጤና ድርጅት የገለጸ ሲሆን፣ ከእነዚህም ውስጥ ወደ 3,000 የሚጠጉት ልጆች ናቸው።
    • ከሦስት ሳምንት በፊት ሐማስ በደቡባዊ እስራኤል ላይ በፈጸመው ድንገተኛ ጥቃት ቢያንስ 1,400 ሰዎች የተገደሉ ሲሆን፣ 229 የሚሆኑት ደግሞ በታጣቂው ቡድን ታግተው ተወስደዋል ተብሎ ይታሰባል።
    • ውሃ፣ ምግብ እና ሕክምና አቅርቦቶችን የጫኑ ተሽከርካሪዎች ከሕክምና ቡድን ጋር በመሆን ወደ ጋዛ እንዲገቡ ተፈቅዶላቸዋል፣ ነገር ግን የረድኤት ድርጅቶች ከዚህ የበለጠ እርዳታ እንደሚያስፍልግ ጥሪያቸውን ማቅረብ ቀጥለዋል።
    • ጦርነቱ ከተጀመረበት ዕለት አንስቶ ወደ ጋዛ ነዳጅ እንዲገባ አልተፈቀደም፣ የፍልስጤም ቀይ ጨረቃ ማኅበር ለቢቢሲ እንደገለጸው ለአምቡላንሶች የሚያስፈልገው ነዳጅ እያለቀ ሲሆን፣ ሕይወት አድን ማሽኖች ብቻ ናቸው እየሰሩ ያሉት።
    • የመንግሥታቱ ድርጅት የፍልስጤም የስደተኞች ድርጅት የሰብአዊ እርዳታ አቅርቦት ተኩስ አቁም እንዲደረግ በድጋሚ ጥሪ ያቀረበ ሲሆን፣ ግጭቱ ከቀጠለ ሥራውን ከአምስት ቀናት በላይ ሊቀጥል እንደማይችል አሳውቋል። ደርጅቱ ቢያንስ 57 ሠራተኞቹ ጋዛ ውስጥ ተገደለውበታል።
    • አሜሪካ ሶሪያ ውስጥ የኢራን እና የምትደግፋቸው ሚሊሻዎቸ የሚጠቀሙባቸውን ወታደራዊ ተቋማትን በአውሮፕላን ደብድባለች። ይህም በቅርቡ ሶሪያ እና ኢራን ውስጥ በሚገኙ ወታሮቿ ላይ ለተፈጸሙ ጥቃቶች ምላሽ መሆኑን አሳውቃለች።
  13. አሜሪካ በሶሪያ ላይ የፈጸመችው የአየር ጥቃት ከእስራኤል-ጋዛው ጦርነት ጋር ግንኙነት የለውም አለች

    የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስትር ሎይድ ኦስቲን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስትር ሎይድ ኦስቲን

    አሜሪካ በምስራቃዊ ሶሪያ ውስጥ በሚገኙ ሁለት ወታደራዊ ተቋማት ላይ የፈጸመችው የአየር ድብደባ ከእስራኤል- ጋዛ ጦርነት ጋር ግንኙነት እንደሌለው አስታወቀች።

    በኢራቅ እና በሶሪያ የሚገኙ የአሜሪካ ጦር አባላት ላይ በኢራን የሚደገፉ የሚሊሻ ቡድኖች እየሰነዘሩት ላለው ጥቃት ምላሽ እንደሆነም የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስትር ሎይድ ኦስቲን ተናግረዋል።

    አገራቸው የፈጸመቻቸው እነዚህ ጥቃቶች "በእስራኤል እና በሃማስ መካከል እየተካሄደ ካለው ግጭት የማይገናኙ እና የማይያዙ ናቸው" ሲሉም በመግለጫቸው አክለዋል።

    የመከላከያ ሚኒስትሩ ሁሉም መንግሥታትም ሆኑ መንግሥታዊ ያልሆኑ ሃይሎች ወደ ቀጣናዊ ግጭት ሊያሸጋግር የሚችል እርምጃም እንዳይወስዱም አሳስበዋል።

    በአገሬው ሰዓት አቆጣጠር አርብ ንጋት ላይ የአሜሪካ ኤፍ-16 የጦር ጄቶች ከኢራቅ ጋር በምትሰዋነው በአቡከማል ከተማ አቅራቢያ የአየር ጥቃት ፈጽመዋል።

    በዚህ የአየር ጥቃት ኢራን የጦር መሳሪያ እና ተተኳሽ ለማከማችት የምትጠቀምበት ስፍራ ወድሟል ተብሏል። በጥቃቱ የተጎዱ ሰዎች እንዳሉ እስካሁን የታወቀ ነገር የለም።

  14. በጋዛ ከተገደሉት ከ40 በመቶ በላይ የሚሆኑት ህጻናት ናቸው- የዓለም ጤና ድርጅት

    የጋዛ አየር ጥቃት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    እስራኤል በጋዛ እየፈጸመችው ባለው የማያባራ የአየር ጥቃት ከተገደሉት ከ40 በመቶ በላይ የሚሆኑት ህጻናት መሆናቸውን የዓለም ጤና ድርጅት አስታወቀ።

    በጋዛ ሰርጥ እስካሁን 7 ሺህ 28 ፍልስጥኤማውያን መገደላቸውን የጋዛ ጤና ሚኒስቴርን ዋቢ ያደረገው ተቋሙ በአየር ጥቃቱ ስለተገደሉት ሰዎች ዝርዝር መረጃ እንደደረሰው ገልጿል።

    በተጨማሪም ሌት ተቀን እየተፈጸመ ባለው የአየር ጥቃት 18 ሺህ 482 የአካል ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን ከነዚህም አብዛኛዎቹ ህጻናት መሆናቸውን ነው ተቋሙ በዛሬው ዕለት ያስታወቀው።

    በጋዛ ካሉ 35 ሆስፒታሎች ውስጥ 23ቱ አሁንም በከፊል አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸውን ጠቁሞ ሌሎቹ እንዲሁም የማህበረሰብ ክሊኒኮች ተዘግተዋል ብሏል።

    በጋዛ ውስጥ 1 ሺህ ያህል ፍልስጥኤማውያን የኩላሊት እጥበት (ዲያሊሲስ) እንደሚያስፈልጋቸው፣ 30 ያለጊዜያቸው የተወለዱ ህጻናት በማሞቂያ ክፍል ውስጥ እንደሚገኙ እና 2 ሺህ የካንሰር ህሙማን አስቸኳይ ህክምና ያስፈልጋቸዋል ብሏል።

    ሆኖም የነዳጅ እጥረት ክፉኛ ባጋጠማት ጋዛ ሆስፒታሎች አገልግሎታቸውን በጄኔሬተር እንዲሰጡ ለማድረግ ነዳጅ እንዲገባ መፈቀድ እንዳለበትም ነው ያስታወቀው።

    በሆስፒታሎች ውስጥ ያለውን አሳዛኝ ሁኔታ ያብራሩት የዓለም ጤና ድርጅት ባለስልጣን በጠና የተጎዱ ህሙማን ያለ ማደንዘዣ ቀዶ ህክምና በመተላለፊያዎች ላይ እንደሚደረግላቸው፣ “የተቆራረጡ የህጻናት አካላት” በየስፍራው የሚታዩበት እና የሞት ጥላ ያንዣበበት መሆኑንም ገልጸዋል።

  15. ቤተሰቡ በእስራኤል አየር ጥቃት የተገደሉበት የአልጀዚራው ጋዜጠኛ

  16. 20 ቀናትን ያስቆጠረው የእስራኤል-ጋዛ ጦርነት

    በደቡባዊ ጋዛ ኻን ዮኒስ ከተማ በተፈጸመው የአየር ጥቃት ቤተሳበቸውን ያጡ ፍልስጥኤማውያን እናቶች ሐዘናቸውን እየገለጹ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በደቡባዊ ጋዛ ኻን ዮኒስ ከተማ በተፈጸመው የአየር ጥቃት ቤተሳበቸውን ያጡ ፍልስጥኤማውያን እናቶች ሐዘናቸውን እየገለጹ

    በእስራኤል- ጋዛ የተቀሰቀሰው ጦርነት 20 ቀናት ሞላው።

    ሐማስ በእስራኤል ላይ በፈጸመው መብረቃዊ ጥቃት ከ1 ሺህ 400 በላይ እስራኤላውያን ተገድለዋል፤ ከ200 በላይ ሰዎች ታግተዋል።

    እስራኤል በጋዛ ሰርጥ ላይ የማያባራ ጥቃት እየፈጸመች ሲሆን ከ7 ሺህ በላይ ፍልስጥኤማውያን ተገድለዋል፤ ከነዚህም አብዛኞዎቹ ህጻናት እና ሴቶች መሆናቸውን የጋዛ ጤና ሚኒስቴር መረጃ ያሳያል።

    በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችም በፍርስራሽ ስር ተቀብረዋል።

    በተጨማሪም እስራኤል ጋዛን በሙሉ ከበባ በማስገባት ነዳጅ፣ ውሃ፣ ኤሌክትሪክ አቅርቦት እንዲቋረጥ አድርጋለች።

    የባለፉትን 20 ቀናት በምስል እንቃኛቸው፦

    በኻን ዮኒስ ከተማ በእስራኤል አየር ጥቃት በፈራረሱ ክምሮች ውስጥ አስከሬን እየፈለጉ ያሉ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በኻን ዮኒስ ከተማ በእስራኤል አየር ጥቃት በፈራረሱ ክምሮች ውስጥ አስከሬን እየፈለጉ ያሉ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች
    የእስራኤል ታንኮች በሊባኖስ ድንበር አቅራቢያ በወታደራዊ ልምምድ ላይ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል ታንኮች በሊባኖስ ድንበር አቅራቢያ በወታደራዊ ልምምድ ላይ
    በግብጽ ራፋህ የድንበር ማቋረጫ በኩል ወደ ጋዛ ሰርጥ ለመግባት በመጠባበቅ ላይ ያሉ እርዳታ የጫኑ መኪናዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, በግብጽ ራፋህ የድንበር ማቋረጫ በኩል ወደ ጋዛ ሰርጥ ለመግባት በመጠባበቅ ላይ ያሉ እርዳታ የጫኑ መኪናዎች
  17. አሜሪካ በሶሪያ ላይ የፈጸመችውን ጥቃት ተከትሎ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳየ

    አሜሪካ በምሥራቃዊ ሶሪያ ውስጥ በሚገኙ ሁለት ወታደራዊ ተቋማት ላይ የአየር ደብድባ መፈጸሟን ተከትሎ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳየ።

    የአሜሪካ ጥቃት የእስራኤል እና ሐማስ ግጭትን በመካከለኛው ምሥራቅ ያሉ አገራትን የሚያሳትፍ ግጭት እንዲሆን ሊያደርግ ይችላል በሚል ስጋት ነው የዋጋ ጭማሪው የተከሰተው ሲል ሮይተርስ ዘግቧል።

    በዚህም ምክንያት የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ በ1.16 ዶላር በመጨመር 89.09 ዶላር እየተሸጠ ነው።

    በመካከለኛው ምሥራቅ ግጭቱ የሚስፋፋ ከሆነ ነዳጅ አምራች ከሆኑ የአካባቢው አገራት በሚወጣው የነዳጅ አቅርቦት ሰንሰለት ላይ ችግር ሊፈጥር ይችላል።

    የአሜሪካ መከላከያ አርብ ንጋት ላይ በአየር የደበደባቸው ወታደራዊ ተቋማት በኢራን እና የኢራን ተባባሪ በሆኑ ቡድኖች ጥቅም ላይ ሲውሉ የነበሩ ተቋማት ናቸው ተብሏል።

  18. ተመድ ወደ ጋዛ እርዳታ እንዲገባ ተማጽኖውን አቀረበ

    ምግብ የያዘች ህጻን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በከበባ ላይ ባለችው የጋዛ ሰርጥ ተጨማሪ እርዳታ እንዲገባ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ተማጽኖውን አቀረበ።

    "ጋዛ ታንቃ ነው ያለችው" እንዲሁም ህዝቦቿ "የተጣሉ፣ የተገለሉ እና የተተው እንደሆነ እየተሰማቸው ነው" ሲሉም የተባባሩት መንግሥታት የፍልስጥኤም ስደተኞች ኤጀንሲ ኮሚሽነር ጄነራል ፊሊፕ ላዛራኒ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    በርካታ ነዋሪዎች ምግብ እና ውሃ እየተመናመነባቸው፣ በሽታዎች እያንዣበበቡ እንደሆነ እንዲሁም ጋዛ በከፍተኛ የጤና አደጋ አፋፍ ላይ እንደምትገኝም ገልጸዋል።

    በጋዛ ውስጥ ሰዎች እየረገፉ እንዲሁም መሰረታዊ አገልግሎቶች እየፈራረሱ መሆናቸውንም ኮሚሽነሩ አጽንኦት በመስጠትም ነው የተናገሩት።

    የሰብዓዊ እርዳታ ወደ ጋዛ እንዲገባ የአቅርቦት መስመሮችን ለመክፈት ከፍተኛ ድርድር ቢደረግም እስካሁን እንዲገቡ የተፈቀደላቸው "በጣት የሚቆጠሩ እርዳታ የጫኑ መኪናዎች መሆናቸውን"ም ገልጸዋል።

    "ብዙዎቻችን እነዚህ እርዳታ የጫኑ አሽከርካሪዎች ሲገቡ የተስፋ ጭላንጭል አይተን ነበር። ነገር ግን ከፍርፋሪ ያለፈ አልነበረም፤ በጋዛ ላይ ያለውንም ትኩረት የከፋፋለ ነው" ሲሉም ተደምጠዋል።

    አሁን ያለው አሰራር መቀየር እንዳለበት ገልጸው እርዳታ ወደ ጋዛ እንዲገባም የሰብዓዊ ተኩስ አቁም ስምምነት ሊደረስ ይገባል ብለዋል።

    "ይህንን መጠየቅ እንደ ትልቅ ጥያቄ መታየት የለበትም" ብለዋል ኮሚሽነሩ።

    "በርካቶች በችጋር ላይ ያሉበትን ሁኔታ በቀጥታ እያየን ባለንበት ወቅት ሰብዓዊ እርዳታ ላይ ጥያቄ መነሳቱ ህመም የሚፈጥር ነው" ሲሉም አክለዋል። ተመድ ምንም አይነት ሰብዓዊ እርዳታዎችን ላልተገባ አካልም እንደማያዞርም ተናግረዋል።

  19. አሜሪካ በእስራኤል እና በሐማስ መካከል "የተኩሰ አቁም እንዲደረግ አልደግፍም" አለች

    እስራኤል በጋዛ ሰርጥ እያካሄደች ባለችው ጥቃት ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሕዝብ ተፈናቅሏል።

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, እስራኤል በጋዛ ሰርጥ እያካሄደች ባለችው ጥቃት ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሕዝብ ተፈናቅሏል።

    አሜሪካ ሐማስ መልሶ እንዲደራጅ ዕድል የሚሰጥ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረስ አልደግፍም አለች።

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ቃል አቀባይ ለቢቢሲ ሲናገሩ አገራቸው ሐማስ “እረፍት አድርጎ፣ እራሱን አደራጅቶ እስራኤል ላይ የሽብር ዘመቻዎችን እንዲቀጥል” የሚፈቅድ የተኩስ አቁም ስምምነትን አትደግፍም ብለዋል።

    ማቲው ሚለር መስከረም 26/2016 ዓ.ም. ሐማስ እስራኤል ከፈጸመውን ጭካኔ የተሞላበት ድንገተኛ ጥቃት በተጨማሪ ቡድኑ “ሰላማዊ እስራኤላውያንን ዒላማ ያደረጉ ሮኬቶችን በየዕለቱ ያስወነጭፋል” ሲሉ ተናግረዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ሐማስ የተኩስ አቁም ስምምነት ሳይደረስ አግቼ የያዝኳቸውን ታጋቾች አለቅም ብሏል።

    በሞስኮ ጉብኝት እያደረጉ ያሉ ከፍተኛ የሐማስ አመራሮች እስራኤል በጋዛ ሰርጥ እያደረገች ያለው የአየር ደብደባ ሳይቆም ሐማስ የያዛቸውን ሰዎች እንደማይለቅ ለሩሲያ መገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል።

    ማቲው ሚለር የሰብዓዊ እርዳታ ለማድረስ ሲባል ሁለቱ አካላት ተኩስ እንዲያቆሙ ግን አሜሪካ ፍላጎት እንዳላት አመልክተዋል።

    የተባበሩት መንግሥታት ጠቅላላ ጉባኤ ዛሬ አርብ ጥቅምት 16/2016 ዓ.ም. በጋዛ አስቸኳይ የተኩስ አቁም እንዲደረግ በሚጠይቅ የውሳኔ ሃሳብ ላይ ድምጽ ይሰጣል።

  20. ኤርትራ በዳህላክ የእስራኤል ወታደራዊ ጣቢያ ላይ ጥቃት ተፈጸመ መባሉን ሐሰት ነው አለች