ኢራን ከፍተኛ የጦር አዛዧ መገደላቸውን አረጋገጠች

የፎቶው ባለመብት, Iran government
እስራኤል በፈጸመችው ጥቃት የአገሪቱ ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ ሳኢድ ኢዛዲ መገደላቸውን የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ማረጋገጡን የአገሪቱ ሚዲያ ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።
ኢዛዲ የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ቅርንጫፍ የሆነው 'ቁድስ ፎርስ' ከፍተኛ አዛዥ ነበሩ።
ይህ ቅርንጫፍ በቀጣናው ያሉ የኢራን አጋር ታጣቂዎችን ድጋፍ ማድረግን ጨምሮ በውጭ አገራት ያሉ እንቅስቃሴዎችን በበላይነት የሚያይ ነው።
አዛዡ ከሐማስ እና ከሌሎች የፍልስጤም ታጣቂ ቡድኖች ጋር የማስተባበር ኃላፊነት የሳቸው ነበር።
አብዮታዊ ዘቡ አዛዡ መቼ እንደተገደሉ ያለው ነገር ባይኖርም የእስራኤል መከላከያ ሰኔ 14 / 2017 ዓ.ም መገደላቸውን አስታውቋል።
ዩናይትድ ኪንግደም "በመካከለኛው ምስራቅ ሰላም እና ደህንነት ስጋቶችን በመፍጠር" እንዲሁም "በዩኬ መሬት ላይ ግለሰቦችን ለመግደል በማሴር" በሚል በአዛዡ ላይ በአውሮፓውያኑ 2023 ማዕቀብ ጥላባቸው ነበር።
አሜሪካ በአውሮፓውያኑ 2019 ለሐማስ በሚሊዮን የሚቆጠር ዶላር ሰጥተዋል በሚል በጦር አዛዡ ላይ ማዕቀብ ጥላባቸዋለች።















