በሱዳን ጦርነት ኢትዮጵያዊያንን ጨምሮ የተለያዩ አገራት ቅጥረኛ ተዋጊዎች እንዳሉ ተነገረ

የፎቶው ባለመብት, AFP
በሱዳን እየተካሄደ ባለው የእርስ በርስ ጦርነት ኢትዮጵያን ጨምሮ ከተለያዩ አገራት የመጡ ቅጥረኛ ተዋጊዎች እንደሚሳተፉ የሱዳን ባለሥልጣናት ተናገሩ።
በጦነርቱ ተሳታፊ የሆነው ፈጥኖ ደራሽ ኃይል ውጭ አገራት ቅጥረኛ ተዋጊዎችን እንደሚያሰልፍ እና የተያዙም እንዳሉ ባለሥልጣናት አሳውቀዋል።
የሱዳን ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግም የሱዳን ጦር ኃይልን በመቀናቀን ከሚዋጋው የፈጥኖ ደራሽ ኃይል ጋር ተሰልፈው ሲዋጉ ነበር ባላቸው ከ120 በላይ የውጭ አገር ቅጥረኛ ወታደሮች ላይ ክስ መሥርቷል።
በሱዳን ጦር ኃይል የሚመራው የሱዳን መንግሥት ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ኢንቲሳር አሕመድ አብደል ሙታአል የወንጀል ክስ የቀረበባቸው የውጭ አገራት ተዋጊዎች የተለያየ ዜግነት ያላቸው መሆናቸውን ገልጸዋል።
ዐቃቤ ሕጓ እንዳሉት ቅጥረኛ ተዋጊዎቹ ሦስት ዓመት ሊሞላው በተቃረበው የሱዳን የእርስ በርስ ጦርነት ውስጥ በጄኔራል ሐምዳን ዳጋሎ ከሚመራው ፈጥኖ ደራሽ ኃይል (አርኤስኤፍ) ጎን በመሰለፍ በመዋጋታቸው ነው ክሱ የቀረበባቸው።
የሱዳን ባለሥልጣናት ፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ ከሱዳን ጦር ሠራዊት ጋር በሚያካሂደው ጦርነት ውስጥ አባላቱን ለማጠናከር የሚዋጉለትን ቅጥረኛ ወታደሮች ከተለያዩ አገራት እየመለመለ ያሰልፋል ሲሉ ይከሳሉ።
ፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ ከጎረቤት አገራት ከኢትዮጵያ፣ ከደቡብ ሱዳን፣ ከቻድ እና ከደቡብ አሜሪካ ደግሞ ከኮሎምቢያ ቅጥረኛ ወታደሮችን እንደሚመለምል ባለሥልጣነቱ አመልክተዋል።
የሱዳን መንግሥት ጠቅላይ ዐቃቤ ሕጓ ጨምረው የተወሰኑ የውጭ ቅጥረኛ ወታደሮች ክስ ተመሥርቶባቸው ጥፋተኛ ሆነው ሞት የተፈረደባቸው እንዳሉ ገልጸዋል።
ነገር ግን በቅጥረኛ ተዋጊዎቹ ላይ የተላለፈው የቅጣት ውሳኔ ተግባራዊ ስለመሆኑ እና ሌሎች ዝርዝር ጉዳዮችን ከመግለጽ ተቆጥበዋል።
በሱዳን ጦር ኃይሎች አዛዥ በጄነራል አል ቡርሐን እና በፈጥኖ ደራሹ ኃይሉ መሪ በጄነራል ጋዳሎ መካከል በተፈጠረ የሥልጣን ፉክክር በተቀሰቀሰው የሱዳን የእርስ በርስ ጦርነት በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ሕይወት ሲጠፋ ሚሊዮኖች ደግሞ ተፈናቅለዋል።





















