“አውሮፓን ማስገደድ አይቻልም”- የዴንማርክ ጠቅላይ ሚኒስትር

የፎቶው ባለመብት, Reuters
የዴንማርክ ጠቅላይ ሚኒስትር ሜቴ ፍሬድሪክሰን “አውሮፓን ማስገደድ አይቻልም” ሲሉ ለፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዛቻ ምላሽ ሰጡ።
ትራምፕ፤ አሜሪካ ግሪንላንድን ለመጠቅለል የምታደርገውን ሙከራ የሚያሰናክሉ ከሆነ ስምንት የአውሮፓ አገራት ታሪፍ እንደሚጣልባቸው ዝተዋል።
ትራምፕ ከፊል ራስ ገዝ የሆነችው የዴንማርክ ግዛት ግሪንላንድን እንደሚጠቀልሉ መግለጻቸውን ተከትሎ፤ ዕቅዳቸውን የማይቀበሉ አገራት ላይ ታሪፍ እንደሚጥሉ ማስታወቃቸው በአውሮፓ ውዝግብ አስከትሏል።
ታሪፍ ይጣልባቸዋል የተባሉት ስምንት አገራት በጋራ ባወጡት መግለጫ የትራምፕ ዕቅድ “አደገኛ አካሄድ ነው” ሲሉ ኮንነዋል።
“ታሪፍ ለመጣል መዛት ግንኙነትን ያሻክራል። ዴንማርክን እንዲሁም የግሪንላንድ ሕዝብን ሙሉ በሙሉ እንደግፋለን” ብለዋል።
የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃልኪዳን (ኔቶ) አባል አገራቱ “የአርክቲክን ደኅንነት ለመጠበቅ ቁርጠኛ ነን” ሲሉም አቋማቸውን ገልጸዋል።
የአሜሪካ አጋር የሆኑት ዴንማርክ፣ ፊንላንድ፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ኔዘርላንድስ፣ ኖርዌይ፣ ስዊድን እና ዩናይትድ ኪንግደም በጋራ ካወጡት መግለጫ ባሻገር የዴንማርክ ጠቅላይ ሚኒስትር በተናጠል ባስተላለፉት መልዕክት የትራምፕን ዕቅድ አጥብቀው አውግዘዋል።
በፌስቡክ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍም “ግጭት የፈለግነው እኛ አይደለንም። እኛ ትብብር ነው የምንሻው። የተቀረው አውሮፓ ስለደገፈን ደስተኛ ነኝ። አውሮፓን ማስገደድ አይቻልም” ብለዋል።

