ማክሮን እስራኤል ሕጻናት እና ሴቶችን በቦምብ ከመደብደብ ትቆጠብ አሉ

የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን እስራኤል በጋዛ ያሉ ሕጻናት እና ሴቶችን በቦምብ ከመደብደብ መቆጠብ አለባት አሉ። ፕሬዝዳንቱ ይህን ያሉት በሐማስ የሚመራው የጋዛ የጤና ሚኒስቴር በጦርነቱ አስካሁን የተገደሉ ሰዎች ቁጥር ወደ 11,078 ከፍ ማለቱን ይፋ ካደረገ በኋላ ነው። በእስራኤል ጥቃት ከተገደሉት ፍልስጤማውያን መካከል አብዛኛውን ቁጥር የሚይዙት ሕጻናት እና ሴቶች ናቸው።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በእስራኤል ጦር የተከበበው ሆስፒታል ነዳጅ ጨርሶ ሥራ አቆመ

    አል-ሺፋ ሆስፒታል ከሦስት ቀናት በፊት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, አል-ሺፋ ሆስፒታል ከሦስት ቀናት በፊት

    በእስራኤል ጦር ከበባ ስር የገባው አል-ሺፋ ሆስፒታል ነዳጅ በመጨረሱ ስራ ማቆሙን በሐማስ የሚተዳደረው ጤና ሚንስቴር አስታወቀ።

    ከትናንት አርብ ምሽት ጀምሮ የእስራኤል ወታደሮች በጋዛ ከተማ የሚገኘውን ሆስፒታል ከበው መያዛቸው ተዘግቧል።

    የጤና ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ሆስፒታሉ ነዳጅ በመጨረሱ ስራ አቁሟል ብለዋል። “በማሞቂያ ክፍል ውስጥ የነበረ ጨቅላ ሕይወቱ አልፏል። ሌሎች 45 ጨቅላዎች በሆስፒታሉ አሉ” ሲሌ አሽራፍ አል-ቂድራ ተናግረዋል።

    የድምበር የለሽ የሃኪሞች ቡድን አባል የሆኑት ሐኪም የተኩስ አቁም ካልተደረገ ወይም የሕክምና እርዳታ እንዲገባ ካልተደረገ “በሆስፒታሉ ያሉ ታካሚዎች በሙሉ አልቀው ሆስፒታሉ ወደ መቃብር ስፍራነት ይቀየራል” ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    ዶ/ር መሐመድ አቡ የተባሉት ሐኪም ለቢቢሲ ሲናገሩ በሆስፒታሉ የሕጻናት ክፍል ውስጥ ይሰሩ የነበሩ የድንበር የለሽ የሃኪሞች ቡድን ባለሙያዎች በሽተኞችን ጥለው ለመሸሽ ተገደዋል።

    ሐኪሙ ጨምረው እንደተናገሩት የሕክምና ግብዓቶች ከፍተኛ እጥረት ስላለ ቀዶ ሕክምናዎች ያለ ማደንዘዣ እየተከናወኑ ነው ብለዋል።

  2. በለንደን ለፍልስጤም ድጋፍ ለሚሰጥ ትልቅ ሰልፍ ሊደረግ ነው

    ከአንድ ሳምንት በፊትም በለንደን ከተማ ለፍልስጤማውያን ድገፍ የሚሰጥ ሰልፍ ተካሂዶ ነበር።

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ከአንድ ሳምንት በፊትም በለንደን ከተማ ለፍልስጤማውያን ድገፍ የሚሰጥ ሰልፍ ተካሂዶ ነበር።

    የለንደን ፖሊስ በከተማዋ ትልቅ ለፍልስጤም ድጋፍ የሚሰጥ ስልፍ ሊደረግ መሆኑን ገለጸ።

    ሰልፉ በከተማዋ ከሚገኘው ግዙፉ ሃይድ ፓርክ እስከ የአሜሪካ ኤምባሲ የሚደረግ መሆኑን ፖሊስ ገልጿል።

    ጠቅላይ ሚንስትር ሪሺ ሱናክ ለፍልስጤማውያን ድጋፍ ለመስጠት የሚወጡ ሰዎች በአይሁድ እና በሙስሊሙ ማኅብረሰብ ውስጥ ያለው ስጋት እና ጭንቀት እንዳይዘነጉ ጠይቀዋል።

    ከአንድ ሳምንት በፊትም በለንደን ከተማ ለፍልስጤማውያን ድገፍ የሚሰጥ ሰልፍ ተካሂዶ ነበር።

  3. በአውስትራሊያ በፍልስጤም እና እስራሌል ደጋፊዎች መካከል ግጭት ተከሰተ

    በአውስትራሊያዋ ሁለተኛዋ ትልቋ ከተማ ሜልበርን በፍልስጤም እና በእስራኤል ደጋፊዎች መካከል ግጭት መፈጠሩ ተዘገበ።

    የአገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ ኤቢሲ በግጭቱ ወቅት ሰዎች በውሃ የተሞሉ ፕላስቲክ ጠርሙሶችን መወራወራቸውን እና ሃይማኖታዊ ይዘት ያላቸው ስድቦች መሰንዘራቸውን ዘግቧል።

    በሁሉቱም ወገን ከ400 ያላነሱ ሰዎች አደባባይ መውጣታቸው ፖሊስ ያስታወቀ ሲሆን ግጭቱን ተከትሎ አንድ ሰው በቁጥጥር ስር መዋሉን ጨምሮ አስታውቋል።

    በግጭቱ በሰው ላይ የደረሰ ጉዳት ስለመኖሩ የተባለ ነገር የለም።

  4. በምስል፡ ለፍልስጤማውያን ድጋፍ በኒው ዮርክ

    በአሜሪካዋ ኒው ዮርክ ለፍልስጤማውያን ድጋፍ ለመግለጽ ሰልፍ ተካሄደ።

    ሰልፈኞቹ በጋዛ የተኩስ አቁም እንዲደረግ መጠየቃቸውን አሶሽዬትድ ፕሬስ ዘግቧል።

    ኒው ዮርክ ታይምስ ጋዜጣ ዘገባዎቹ ለእስራኤል ያደሉ ናቸው ሲሉ ሰልፈኞቹ ድምጻቸውን ከመስራ ቤቱ ፊት ለፊት አሰምተዋል።

    ሰልፍ

    የፎቶው ባለመብት, AP

    ሰልፍ

    የፎቶው ባለመብት, AP

    ሰልፍ

    የፎቶው ባለመብት, AP

  5. አረብ እና ሙስሊም አገራት ዛሬ በሳዑዲ ሊመክሩ ነው

    ሪያድ

    ሳዑዲ አረቢያ የአረብ ሊግ አባል አገራትን እና የእስላማዊ ትብብር ድርጅት አባላትን ለአስቸኳይ ስብበሳ ዛሬ ሪያድ ላይ ጠርታለች።

    የአረብ እና ሙስሊም አገራቱ የስብሰባ አጀንዳ በጋዛ ያለው ጦርነት እና እርሱን ተከትሎ የመጣው የሰብዓዊ ቀውስ ይሆናል ሲል ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የስብሰባው ዓላማ ለፍልስጤማውያን ድጋፍ መስጠት እና እስራኤል በጋዛ እያደረገች ያለችው ወረራ እና ድብደባ እንድታቆም ዓለም አቀፍ ጫናን ማሳደር ነው ተብሏል።

    የስብሰባው ተሳታፊዎችም ሪያድ እየገቡ ነው።

  6. የሔዝቦላ መሪ ነስራላህ ዛሬ ንግግር ያደርጋሉ ተባለ

    የሔዝቦላ መሪ ሐሰን ነስራላህ

    የፎቶው ባለመብት, JAMARAN

    የምስሉ መግለጫ, የሔዝቦላ መሪ ሐሰን ነስራላህ

    የሔዝቦላ መሪ ሐሰን ነስራላህ ዛሬ ለደጋፊዎቻቸው ንግግር ያደርጋሉ ተባለ።

    መቀመጫውን ሌባኖስ ያደረገው የጠንካራው ሔዝቦላ መሪ ዛሬ ከሰዓት የሚያደርጉት ንግግር የእስራኤል-ሐማስ ጦርነት ከተቀሰቀሰ በኋላ ሁለተኛው ይሆናል።

    በእስራኤል-ጋዛ ጦርነት ሔዝቦላህ በቀጣይ ምን ሊያደርግ እንደሚችል ሐሰን ናስራላህ ዛሬ በሚያደርጉት ንግግራቸው ሊጠቁሙ ይችላሉ ተብሏል።

    ከአንድ ሳምንት በፊት በነበረው ንግግራቸው ጦርነቱን በመለከተ “ሁሉም አማራጭ በጠረቤዛ ላይ ነው” ብለው ነበር።

    ስለ ሔዝቦላው መሪ የተመለከተውን ዘገባ እነዚህ ያንብቡ፡የእስራኤል ስጋት የሆነው የሔዝቦላህ መሪው ሐሰን ናስራላህ ማን ናቸው?

  7. የእስራኤል ታንኮች ከጋዛ ሆስፒታሎች አቅራቢያ ታዩ

    ጋዛ

    የፎቶው ባለመብት, BBC Verify

    ትናንት አርብ የእስራኤል ታንኮች ከጋዛ ሆስፒታሎች አቅራቢያ መገኘታቸውን ተከትሎ በጤና ተቋሟቱ ውስጥ እና አቅራቢያ ፍንዳታዎች እንደነበሩ የዓይን እማኞች ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    ታንኮቹ አል-ሺፋ፣ አል-ቁዱስ፣ አል-ራንቲሲ እና ከኢንዶኔዢያ ሆስፒታል አቅራቢያ ታይተዋል።

    እስራኤል ቀደም ሲል ሐማስ በሰላማዊ ሰዎች መሠረተ ልማቶች ስር ዋሻዎችን ቆፍሯል ብላለች።

    ቢቢሲ አል-ናስር ከሚባል ሆስፒታል የሚሸሹ ሰዎች በእስራኤል ጦር እንዳይመቱ ነጭ ጨርቅ ሲያውለበልቡ የሚያሳየውን ምስል ትክክለኛነት አረጋገጧል።

    በሐማስ የሚመራው የጋዛ የጤና ሚኒስቴር በጦርነቱ እስካሁን የተገደሉ ሰዎች ቁጥር ወደ 11,078 ከፍ ማለቱን ይፋ አድርጓል።

    እንደ ጤና ሚኒስቴሩ ከሆነ በእስራኤል ጥቃት ከተገደሉት ፍልስጤማውያን መካከል አብዛኛውን ቁጥር የሚይዙት ሕጻናት እና ሴቶች ናቸው።

  8. ማክሮን እስራኤል ሕጻናት እና ሴቶችን በቦምብ ከመደብደብ ትቆጠብ አሉ

    ፕሬዝዳንት ማክሮን
    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ማክሮን

    የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን እስራኤል በጋዛ ያሉ ሕጻናት እና ሴቶችን በቦምብ ከመደብደብ መቆጠብ አለባት አሉ።

    ፕሬዝዳንቱ ከቤተ-መንግሥታቸው ሆነው ለቢቢሲ በሰጡት ቃለ መጠይቅ ለድብደባዎቹ “ምንም አይነት ማሳመኛ” የለም ያሉ ሲሆን የተኩስ አቁም ቢደረግ ተጠቃሚዋ እስራኤል ነች ብለዋል።

    የእስራኤልን እራስን የመከላከል መብት ብናምንም፤ በጋዛ “እያደረጉት ያሉትን ድብደባ እንዲያቆሙ እንጠይቃለን” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንት ማክሮን አገራቸው የሐማስን “የሽብር” ተግባራት “በግልጽ ትቃወማለች” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ አሜሪካ እና ዩኬን ጨምሮ ሌሎች አገራትም የተኩስ አቁም እንዲደረግ ጥሪ ያቀርባሉ ብዬ እጠብቃለሁ ብለዋል።

    ይህ የፕሬዝዳንቱ ንግግር እስራኤልን አላስደሰተም። ጠቅላይ ሚንስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ መንግሥታት ማውገዝ ያለባቸው ሐማስን እንጂ እስራኤልን መሆን የለበትም ብለዋል።

    ጠቅላይ ሚንስትሩ ጦራቸው ሰላማዊ ሰዎች ለመለየት ቢጥርም ሐማስ ግን እነርሱን መሸሸጊያ አድርጓል ብለዋል።

    “ዛሬ በሐማስ-አይሲሲ የተፈጸመው ወንጀል ነገ በፓሪስ፣ ኒው ዮርክ እና በመላው ዓለም ይፈጸማል” ሲሉ ኔታኒያሁ ባወጡት መግለጫ አስጠንቅቀዋል።

    ፈረንሳይ ልክ እንደ እስራኤል፣ አሜሪካ፣ ዩናይትድ ኪንግደም እና ሌሎች ምዕራባውያን አገራት ሐማስን አሸባሪ ድርጅት ስትል ፈርጃለች።

  9. ጋዛ ውስጥ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር ከ11 ሺህ በላይ መሆኑ ተነገረ

    የፈራረሰ ሕንጻ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በሐማስ የሚመራው የጋዛ የጤና ሚኒስቴር ዛሬ አርብ ከሰዓት በኋላ ባወጣው መግለጫ በጦርነቱ አስካሁን የተገደሉ ሰዎች ቁጥር ወደ 11,078 ከፍ ማለቱን አመለከተ።

    ሰላሳ አምስት ቀናት ባስቆጠረው እስራኤል በጋዛ ሰርጥ ላይ እያካሄደችው ባለው ወታደራዊ ዘመቻ ከተገደሉት ፍልስጤማውያን መካከል አብዛኛውን ቁጥር የሚይዙት ሕጻናት እና ሴቶች ናቸው።

    የጤና ባለሥልጣናቱ ካወጡት 11,078 የሟቾች አሃዝ ውስጥ 4,506ቱ ሕጻናት እና ከ3,000 በላይ የሚሆኑት ደግሞ ሴቶች መሆናቸው ተጠቅሷል።

    በሐማስ የበላይነት የሚመራው የጤና ሚኒስቴር በቴሌግራም ገጹ ላይ ባሰራጨው መረጃ ላይ ከተገደሉት ከ11 ሺህ በላይ ሰዎች በተጨማሪ ሌሎች ከ27,000 የሚልቁት ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጦርነቱን ሰለባዎች ከዚህ በፊት ከተደረጉት ግጭቶች ጋር በማነጻጸር እንዳለው የአሁኑ የሟቾች ቁጥር ከፍተኛ ነው።

    ሐማስ ጋዛን ከተቆጣጠረበት ከ2007 (እአአ) በኋላ በተለያዩ ጊዜያት በተካሄዱ ግጭቶች በጋዛ ሰርጥ ውስጥ የተገደሉት ሰዎች ቁጥር 5,400 ያህል ነበር። የአሁኑ ግን ከዚህ በእጥፍ ከፍ ማለቱን ድርጅቱ አመልክቷል።

    አሜሪካ እና አስራኤል የሟቾችን አሃዝ በተመለከተ በሐማስ ከሚመራው የጤና ሚኒስቴር የሚወጣው መረጃ በጥንቃቄ ሊታይ ይገባል ሲሉ፣ የዓለም የጤና ድርጅት ግን ቁጥሩ የሚታመን ነው ብሏል።

  10. በጦርነቱ 35ኛ ቀን ዛሬ አርብ በጋዛ ዋና ዋና ክስተቶች

    ከተጀመረ 35 ቀናትን ያስቆጠረው የጋዛ-እስራኤል ጦርነት ተባብሶ ቀጥሎ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን ሕይወት በመቅጠፍ፣ ጋዛ ውስጥ ከባድ ሰብዓዊ ቀውስን አስከትሏል። የዛሬ አርብ ዋና ዋና ክስተቶች. . .

    በሐማስ የሚመራው የጤና ሚኒስቴር አስካሁን ድረስ 11,078 ሰዎች ጋዛ ውስጥ መገደላቸውን እና ከ27,000 በላይ ሰዎች መቁሰላቸውን አሳውቋል።

    የዐይን እማኞች ለቢቢሲ እንደተናገሩት የእስራኤል ኃይሎች ጋዛ ውስጥ ወደሚገኙ ወደ ዋና ዋናዎቹ የአል-ሺፋ፣ የአል-ቁዱስ እና የኢንዶኔዢያ ሆስፒታሎች እየተቃረቡ ነው። በተጨማሪም ከሆስፒታሎቹ ውስጥ ወይም አቅራቢያ ፍንዳታዎች እንደተከሰቱ ዘገባዎች እየወጡ ነው።

    እስራኤል በበኩሏ ጦር ሠራዊቷ በአል-ሺፋ አቅራቢያ ዘመቻ እያካሄደ መሆኑን አረጋግጣ፣ ነገር ግን በሆስፒታሉ አቅራቢያ እየተካሄደ ስላለው ነገር መረጃ ከመስጠት ተቆጥባለች።

    ከጋዛ ከተማ የወጣ አንድ የቪዲዮ ምስል እንዳሳየው የእስራኤል ታንኮች ከአል-ራንቲሲ የሕጻናት ሆስፒታል ውጪ ቦታ ይዞ አሳይቷል። ወታደሮች በድምጽ ማጉያ ከሆስፒታሉ ውስጥ ሠራተኞች ወይም ታካሚዎች ያልሆኑ ሰዎች ለቀው እንዲወጡ ሲጠይቁ እንደነበር የዐይን እማኞች ተናግረዋል።

  11. “ሐሎ! ከእስራኤል ደኅንነት ቢሮ ነው የምደውለው። ቤትህን ልናጋየው ትዕዛዝ ተሰጥቶናል”

    ዶ/ር ማሕሙድ ሻሒን

    የፎቶው ባለመብት, BBC/GETTY

    የምስሉ መግለጫ, ዶ/ር ማሕሙድ ሻሒን

    ዶ/ር ማሕሙድ ሻሒን የጥርስ ሐኪም ነው።

    ሐሙስ ጥቅምት 8/2016 ዓ.ም. ድንገት ስልኩ ጠራ። የሞት ጥሪ ይሆናል ብሎ አልጠበቀም።

    በዚያ ላይ ገና ከጠዋቱ 12፡30 ነው።

    ሲፈራ ሲቸር፤ ስልኩን አነሳው።

    “ሐሎ፣ ከእስራኤል ደኅንነት ቢሮ ነበር የምደውለው። ያለህበትን ሕንጻ ልናጋየው ትዕዛዝ ተሰጥቶናል።”

    ዶ/ር ማሕሙድ ይህን ጥሪ ቀልድ ነው ማለትን መረጠ። ነገር ግን ከዚያች ዕለት በፊት ለተከታታይ 12 ቀናት እስራኤል በጋዛ ያሉ ሕንጻዎችን ወደ ትቢያነት ስትቀይር ነበር።

    ስለዚህ የስልክ ጥሪው ቀልድ ተብሎ ሊታለፍ አይችልም።

    የዶ/ር ማሕሙድ ሰፈራቸው አል ዛሕራ ይባላል። በጣም ሰላማዊ ሰፈር ነው። መካከለኛ ገቢ ያላቸው ጋዛውያን የሚኖሩበት ሰፈር ነው።

    እሱ የሚኖረው በሦስተኛው ወለል፣ ሦስት መኝታ ቤት ባለው አንድ አፓርትመንት ነው።

    እስከዚያች የስልክ ጥሪ ዕለት ድረስ በጋዛ ያሉ ሁሉ ውድመት ሲደርስ በሰፈራቸው አንዲት ሕንጻ አልተነካችም ነበር።

    “ከእስራኤል ደኅንነት ነው የምንደውልልህ፣ ዶክተር። መፍጠን ይኖርብሃል።”

    ይህ ጥሪ ዶ/ር ማሕሙድ በሕይወቱ ከተቀበላቸው የስልክ ጥሪዎች አስፈሪው ነበር። ሙሉውን እዚህ ያንብቡ

  12. እስራኤል ሥጋ በል አእዋፋትን በመከተል የሞቱ ዜጎቿን አስክሬን እያነሳች ነው

    ንስር

    የፎቶው ባለመብት, RSPB

    የእስራኤል ጦር የሥጋ በል አእዋፋት እንቅስቃሴን በመከተል የሟች ዜጎችን አስክሬን ፈልጎ እያገኘ መሆኑ ተሰማ።

    ሐማስ መስከረም 26/2016 ዓ.ም. በእስራኤል ላይ የተፈጸመውን ድንገተኛ ጥቃት ተከትሎ ከ1400 በላይ እስራኤውያን ተገድለዋል መባሉ ይታወሳል።

    ታዲያ የአገሪቱ ጦር እስካሁን በተለያዩ ቦታዎች ወድቀው የሚገኙ አስክሬኖችን እያነሳ ስለመሆኑ ተመልክቷል።

    የአስክሬኖች መገኛን ለመጠቆም የእስራኤል የተፈጥሮ እና ፓርክ ባለሥልጣን ባልደረባ የሆኑት ኦሃድ ሃትዞፍ እንደ ንስር ያሉ ሥጋ በል አእዋፋትን የበረራ አቅጣጫ በመከተል እንዲሁም የሚቆሙባቸውን ቦታ በመለየት መረጃውን በማጋራት ጦሩ አስክሬኖችን እንዲያነሳ እየረዱ ነው።

    አእዋፋቱ ላይ የአቅጣጫ ጠቋሚ (ጂፒኤስ) የተገጠመ ሲሆን፣ የበረራ አቅጣጫቸውን በመከተል ባለፉት ሁለት ሳምንታት የአራት ሰዎች አስክሬን መነሳቱን ባለሙያው ገልጸዋል።

  13. የዩናይትድ ስቴትስ እና አጋሮቿ ባለፉት ሦስት ሳምንታት 46 ጥቃቶች ተፈጽሞባቸዋል- ፔንታጎን

    ፔንታጎን በመካከለኛው ምስራቅ በሚገኙ የአሜሪካ ወታደሮች ላይ የደረሱ ጥቃቶችን በተመለከተ መረጃ አጋርቷል።

    ከጥቅምት 6 ጀምሮ በአሜሪካ እና በጥምር ኃይሎች ላይ "አንድ ጊዜ የተደረጉ የሰው አልባ አውሮፕላን እና የሮኬት ጥቃቶችን ጨምሮ ቢያንስ 46 ጊዜ" ጥቃት እንደደረሰባቸው አስታውቀወል።

    ጠቃቶቹ በኢራቅ 24 ጊዜ እና በሶሪያ 22 ጊዜ መድረሳቸው ተገልጿል።

    በእነዚህ ጥቃቶች 56 ሰዎች መጎዳታቸውን ፔንታጎን አክሎ ገልጿል።

  14. በጋዛ የሚገኙ የውጭ ሚዲያ ጋዜጠኞች ስለሐማስ ጥቃት ቀድመው ያውቁ ነበር ስትል እስራኤል ከሰሰች

  15. ትምህርት ቤት ላይ በድሮን ጥቃት ያደረሰውን ቡድን መምታቷን እስራኤል ገለጸች

    ሐሙስ ዕለት በደቡባዊ እስራኤል በሚገኝ ትምህርት ቤት ላይ ከደረሰው የሰው አልባ አውሮፕላን ጥቃት ጀርባ ይገኛል ያለውንና መቀመጫውን በሶሪያ ያደረገውን ድርጅት መምታቱን የእስራኤል ጦር አስታወቀ።

    ሰው አልባ አውሮፕላኑ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤትን ቢመታም ምንም ጉዳት አላደረሰም።

    "ከሶሪያ የመጣው ድሮን በኤላት ትምህርት ቤት ላይ ላደረሰው ጥቃት ምላሽ ለመስጠት የእስራኤል መከላከያ ሰራዊት ጥቃቱን ያደረሰውን ድርጅት መትቷል" ሲል ኤክስ ላይ አስፍሯል።

    ጦሩ የቡድኑን ማንነት ባይገልጽም፤ "ከግዛቱ ለሚነሱት የሽብር እንቅስቃሴዎች የሶሪያን አስተዳደር ሙሉ ኃላፊነቱን ይወስዳል" ብሏል።

    ሶሪያ ለእስራኤል መግለጫ እስካሁን ምላሽ አልሰጠችም።

  16. ኳታር ምዕራባውያን አሸባሪ ያሉትን ሐማስ ለምን አስጠለለች? ማደራደሩስ ይሳካላታል?

  17. ተመድ 99 ሠራተኞቹ በጋዛ መገደላቸውን ገለጸ

    ጁሊዬት ቱማ

    የእስራኤል ሐማስ ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ በጋዛ ሰርጥ 99 የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሠራተኞች መገደላቸው ተገለጸ።

    የተመድ የፍልስጤማውያን ስደተኞች ኤጀንሲ ተቋም ቃል አቀባይ 99 ባለደረቦች መገደላቸውን ተናግረዋል።

    ጁሊዬት ቱማ ለቢቢሲ ሲናገሩ የተመድ ተቋም በ150 መጠለያ ጣቢያዎች ከ700 ሺህ ያላነሱ ፍልስጤማውያንን እየረዳ ቢሆንም ባልደረቦቻችን ግን አሁንም መገደላቸው ቀጥሏል ብለዋል።

    ቃል አቀባይዋ ተቋማቸው የሰብዓዊ እርዳታ ለማድረስ የግብዓት ችግር በከፍተኛ መጠን እያጠረው መሆኑንንም ጨምረው ተናግረዋል።

    እርዳታ ለማድረስ ሁለት ነገር ያስፈልገናል ብለዋል ጁሊዬት፤ ነዳጅ እና ለሰብዓዊነት ሲባል የሚደረግ የተኩስ አቁም።

    ሐማስ እስራኤል ላይ መስከረም 26 ጥቃት ካደረሰ ወዲህ ወደ ጋዛ ነዳጅ እንዲገባ አልተፈቀደም። እስራኤል በጋዛ ሰርጥ ሐማስ ደብቆ ይዞ እንጂ በቂ ነዳጅ አለ ትላለች።

  18. ኔታኒያሁ ጋዛን የመውረር፣ መያዝ ወይም የማስተዳደር ፍላጎት የለንም አሉ

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚንስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የእስራኤል ጠቅላይ ሚንስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚንስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ አገራቸው ከሐማስ ጋር የምታደርገው ጦርነት ካበቃ በኋላ የጋዛ ሰርጥን ወርራ የመያዝ፣ ተቆጣጥሮ የመቆየት ወይም የማስተዳደር ፍላጎት የላትም አሉ።

    ጠቅላይ ሚንስትሩ ለፎክስ ኒውስ ሲናገሩ “ጋዛን የመውረር ፍላጎት የለንም፣ ጋዛን የመቆጣጠር ፍላጎት የለንም፣ ጋዛን የማስተዳደር ፍላጎት የለንም” ካሉ በኋላ ጋዛን የሚያስተዳደር የሲቪል መንግሥት ግን መቋቋም አለበት ብለዋል።

    ጠቅላይ ሚንስትሩ ወደፊት የመስከረም 26 አይነት ጥቃት ተመልሶ እንደማይከሰት እስራኤል ማረጋገጥ ትፈልጋለች ብለዋል።

    “አሳማኝ ኃይል ሊኖረን ይገባል፤ አስፈላጊ ከሆነ ጋዛ ገብተን ገዳዩን መግደል መቻል አለብን። ምክንያቱም ይህ አይነቱ እርምጃ እንደ ሐማስ ያሉ ቡድኖች መልሰው እንዳይመጡ ያደርጋል” ብለዋል።

    ኔታኒያሁ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ የሰጡት አስተያየት አገራቸው የጋዛ የደኅንነት ሁኔታ ትቆጣጠራለች የሚል ነበር።

  19. እስራኤል በየቀኑ ለአራት ሰዓታት የተኩስ አቁም ፋታ ልትሰጥ ነው

    ጋዛ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    እስራኤል በሰሜናዊ ጋዛ ጥቃት ከመፈጸም ለአራት ሰዓታት ተቆጥባ ፋታ ልስትሰጥ መሆኑን አሜሪካ አስታወቀች።

    የዋይት ሐውስ ቃል አቀባይ ጆን ኪርቢ በሰሜናዊ የጋዛ አካባቢዎች እስራኤል በየቀኑ ለአራት ሰዓታት ተኩስ ታቆማለች ሲሉ ለሪፖርተሮች ተናግረዋል።

    እስራኤል ፋታ በምትሰጥባቸው አራት ሰዓታት ምንም አይነት ወታደራዊ ዘመቻዎችን እንደማትፈጽም አሳውቃናለች ብለዋል ቃል አቀባዩ።

    የእስራኤል ጦር ቀደም ሲል በጋዛ ለሚኖሩ ፍልስጤማውያን የሰብዓዊ እርዳታ ለማድረስ ፋታ እንደሚሰጥ ገልጾ ነበር።

    የጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ መንግሥት በምንም መልኩ የተኩስ አቁም እንደማያደርግ ግን አስታውቋል።

    የተኩስ አቁም ስምምነት በሁለቱም ተዋጊ ወገን መካከል ተፈጻሚ የሚሆን፤ ለረዥም ጊዜ የሚከበር እና የፖለቲካዊ ሂደት አካል ነው።

    ለሰብአዊ እርዳታ ሲባል የሚደረግ ግጭት የማቆም ፋታ ግን ለአጭር ጊዜ ብቻ የሚቆይ ነው።

  20. ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ነዋሪዎች ከሰሜን ወደ ደቡብ ጋዛ ተፈናቀሉ

    ተፈናቃዮች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በሺዎች የሚቆጠሩ ፍልስጤማውያን ቀያቸውን ጥለው ከሰሜን የጋዛ ክፍል ወደ ደቡባዊው መፈናቀላቸው ተዘገበ።

    እስራኤል በምድር፣ በአየር እና በባሕር ኃይል የታገዘ ጥቃት በሰሜን ጋዛ ላይ አጠናክራ ስታካሂድ ቆይታለች።

    የእስራኤል ጦር ሰላማዊ ሰዎች ለደኅንነታቸው ሲባል ከሰሜናዊ ጋዛ ወደ ደቡብ ጋዛ እንዲያመሩ በተደጋጋሚ ሲያሳስብ ቆይቷል።

    ሰዎች ወደ ደቡባዊ የጋዛ ሰርጥ እንዲሸጋገሩ የእስራኤል ጦር መንገዶችን ለስድስት ሰዓታት ክፍት ማድረጉን ተከትሎ በሺዎች የሚቆጠሩ ፍልስጤማውያን ወደ ደቡብ ፈልሰዋል።

    ተፈናቃዮች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ተፈናቃዮች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters