በሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት 'አዲስ ምዕራፍ ከፍቷል' የተባለው የፕሪቶሪያው ስምምነት

የፌደራል መንግሥት እና የህወሓት መሪዎች መካከል ሲካሄድ የነበረው ድርድር በስምምነት ተጠናቋል። ሁለቱ አካላት የደረሱበት ስምምነት ግጭት የሚያስቆም፣ ትጥቅ የሚያስፈታ፣ የሰብዓዊ እርዳታ እንዲደርስ እና በትግራይ ክልል ሕገ-መንግሥቱ ተፈጻሚ እንሆን የሚያስችል ነው።

የቀጥታ ሽፋን

  1. “ወሳኝ ቀዳሚ እርምጃ” የተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ

    የተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ
    የምስሉ መግለጫ, የተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ

    በኢትዮጵያ መንግሥት እና በህወሓት መካከል የተደረሰው የሰላም ስምምነት ደም አፋሳሹን ጦርነት ለማብቃት “ወሳኝ ቀዳሚ እርምጃ” ነው ሲሉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አወደሱ።

    አንቶኒዮ ጉቴሬዝ በቃል አቀባያቸው በኩል ባወጡት መግለጫ በአፍሪካ ኅብረት በኩል የተደረሰው ስምምነት የበርካቶችን ሕይወትና ኑሮን ያወደመውን ጦርነት ለማስቆም ተስፋ ሰጪ ጅምር ነው ብለዋል።

    የመንግሥታቱ ድርጅት ዋና ፀሐፊ “ኢትዮጵያውያን እና ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የኢትዮጵያ መንግሥት እና ህወሓት የወሰዱትን ቆራጥ እርምጃ” እንዲደግፉ ጥሪ አቅርበዋል።

    አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ሁለቱም ወገኖች ተኩስ አቁመው አገሪቱን ወደ ሰላምና መረጋጋት ለመመለስ “በቀሩ ጉዳዮች ላይ ዘላቂ ፖለቲካዊ ስምምነት ላይ ለመድረስ በእርቅ መንፈስ ድርድራቸውን እንዲቀጥሉ” ድጋፍ እንደሚያደርጉ ገልጸዋል።

    ድርድሩን በማስተባበርና በመምራት የተሳተፉትን ሁሉንም ወገኖች ያመሰገኑት ጉቴሬዝ፣ ሁሉም ወገኖች ተኩስ አቁሙ የፈጠረውን እድል በመጠቀም “የሰብአዊ እርዳታ አቅርቦት እንዲቀላጠፍ እና በጽኑ የሚፈለጉት መሠረታዊ አገልግሎቶች ሥራ እንዲጀመሩ” ጠይቀዋል።

    “የተባበሩት መንግሥታት በአፍሪካ ኅብረት የሚመራውን ቀጣይ ሂደት ለመደገፍና እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው በማቅረብ በኩል ሥራውን ይቀጥላል” ብሏል የወጣው መግለጫ።

  2. ጠቅላይ ሚኒስትሩ በድርድሩ መንግሥታቸው ያቀረበው ሐሳብ ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት አግኝቷል አሉ

  3. ኬንያ በቀጣይ የሰላም ሂደቱን ለመደገፍ ያላትን ቁርጠኝነት ገለጸች

    የኬንያው ፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ
    የምስሉ መግለጫ, የኬንያው ፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ

    የኬንያው ፕሬዝዳንት ዊሊያም ሳሞይ ሩቶ፣ ኬንያ በቀጣይ የኢትዮጵያን የሰላም ሂደት ለመደገፍ ቁርጠኛ ናት አሉ።

    ፕሬዝዳንቱ ትናንት ጥቅምት 23/2015 ዓ.ም ባወጡት መግለጫቸው፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብም ለአደራዳሪ ቡድኑና ለሚመለከታቸው አካላት የሚያደርጉትን ድጋፍ እንዲያጠናክሩ ጥሪ አቅርበዋል።

    ሩቶ ይህን ያሉት የኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት እና የህወሓት አመራሮች ለቀናት በደቡብ አፍሪካ፣ ፕሪቶሪያ ሲካሄድ በቆየው ድርድር ከስምምነት መድረሳቸውን ተከትሎ ነው።

    ፕሬዝዳንት ሩቶ በመግለጫቸው፣ ሁለቱ ወገኖች በአፍሪካ ኅብረት በተመራው የሰላም ንግግር ሂደት ውስጥ ያሳዩት ቁርጠኝነት በቀጠናችን ሰላም እና ደኅንነት ለማስፈን ካለን የጋራ ፍላጎት ጋር ይጣጣማልም ብለዋል።

    ስምምነቱ በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋትን ለመፍጠር ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል ያሉት ፕሬዝዳንቱ፣ ኢትዮጵያውያን ይህ ስምምነት የሰጣቸውን ዕድል ተጠቅመው ለአገራቸው አዲስ የሰላምና የብልጽግና ምዕራፍ እንዲፈጥሩ አሳስበዋል።

    ፕሬዝዳንት ሩቶ ለመላው ኢትዮጵያውያን የአንድነት፣ የመተሳሰብ እና የእርቅ ዘመን እንዲሆንም ተመኝተዋል።

  4. ስለሰላም ስምምነቱ የአውሮፓ ኅብረት መልዕክት

    ጆሴፍ ቦሬል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ጉዳይ እና የደኅንነት ፖሊሲ ከፍተኛ ተወካይ የሆኑት ጆሴፍ ቦሬል በኢትዮጵያ የእርስ በርስ ጦርነት ለሁለት ዓመታት ሲዋጉ የቆዩት ወገኖች ግጭት ለማቆም በመስማማታቸው የእንኳን ደስ ያላችሁ መልዕክት አስተላለፉ።

    የሁለት ዓመቱን ጦርነት ለማስቆም የሰላም ስምምነቱ ላይ እንዲደረስ የአፍሪካ ኅብረት እና ታዛቢዎች እንዲሁም አስተናጋጇ አገር ደቡብ አፍሪካ የሚደነቅ ተግባር አከናውነዋል ያሉት ጆሴፍ ቦሬል፤ ወደፊት በሚደረገው የሰላም ጥረት የአውሮፓ ኅብረቱ ድጋፉን እንደሚያደርግ ገልጸዋል።

    ስምምነቱ በአስቸኳይ ተግባራዊ ማድረግ ያስፈልጋል ያሉት ቦሬል፤ የሰብዓዊ እርዳታ ትግራይ ማድረስ እና መሠረታዊ አገልግሎቶች ማስጀመር ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ መሆን አለበት ብለዋል።

    ቦሬል የድንበር ጉዳይን በተመለከተ ፖለቲካዊ ውይይቶች ያስፈልጋሉ ሲሉም አክለዋል።

  5. ፖለቲከኞች ስለ ስምምነቱ ምን አሉ?

    ጃዋር መሐመድ
    የምስሉ መግለጫ, ጃዋር መሐመድ

    ፖለቲከኞቹ ጃዋር መሐመድ እና አብረሃ ደስታ በፌደራል መንግሥቱ እና በህወሓት መካከል የተደረሰው ስምምነት አዎንታዊ መሆኑን በመግለጽ ሳይዘገይ ተግባራዊ እንዲሆን ጠየቁ።

    ታዋቂው ፖለቲከኛ ጃዋር መሐመድ ከደቡብ አፍሪካ የተሰማው ዜና አዎንታዊ ነው ያለ ሲሆን፣ መንግሥት እና ህወሓት እንዲሁም አደራዳሪዎች እና ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት በፍጥነት ስምምነቱን ተፈጸሚ ያድርጉ ብሏል።

    “ስምምነቱ ተፈርሟል፤ ሰላም ወዳዶች ደስ ብሎናል። ተግባራዊነቱን ሳይዘገይ እንጠብቃለን” ያለው ደግሞ የአረና ፓርቲ ከፍተኛ አመራር አብረሃ ደስታ ነው።

    ጃዋር ይህ የሰላም እርምጃ በተለይ ጦርነት እየተካሄደባት ነው ባላት የኦሮሚያ ክልልም ልዩነቶች በንግግር እንዲፈቱ እና በመላው አገሪቱ ሰላም እንዲሰፍን ጥረት እንዲደረግ ጥሪ አቅርቧል።

  6. “ስምምነቱ የትግራይን ሕዝብ መሠረታዊ ችግር የሚፈታ ነው” ሚኒስትር ለገሰ ቱሉ

    የመንግሥት ኮሚዩኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ለገሰ ቱሉ

    የፎቶው ባለመብት, GOVERNMENT COMMUNICATION SERVICE

    የምስሉ መግለጫ, የመንግሥት ኮሚዩኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ለገሰ ቱሉ

    ለቀናት ሲካሄድ ቆይቶ ትናንት የተጠናቀቀው የሰላም ስምምነት ዘላቂ ሰላምን የሚያመጣ እና የትግራይን ሕዝብ መሠረታዊ ችግር የሚፈታ መሆኑን የመንግሥት ኮሚዩኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ለገሰ ቱሉ ገለጹ።

    በሰላም ንግግሩ የፌደራል መንግሥቱ እና የህወሓት አመራሮች ግጭት ማቆምንና የህወሓት ኃይሎችን ትጥቅ ማስፈታትን ጨምሮ በ12 ነጥቦች ላይ ከስምምነት ላይ ደርሰዋል።

    ሚኒስትሩ በማኅበራዊ የትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፣ የሰላም ስምምነቱ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱንና ብሔራዊ ጥቅማችንን ባስከበረ መልኩ ተጠናቋል” ብለዋል።

    ስምምነቱ ላይ መድረስ የተቻለውም የጸጥታ ኃይሎችና የደኅንነት ኃይሎች በከፈሉት መስዋዕትነትና ባስመዘገቡት ድል፣ ሕዝቡ በአንድ ላይ በመቆሙ እና መንግሥት ሰላምን ለማምጣት ባለው ቁርጠኝነት መሆኑንም ሚኒስትሩ ገልጸዋል።

    “ድሉ የመላ ኢትዮጵያውያን ድል ነው። አሸናፊዋም ኢትዮጵያ ናት!” ብለዋል ሚኒስትር ለገሰ ቱሉ።

  7. ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የሰላም ስምምነቱን ተግባራዊ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆናቸውን ገለጹ

    ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የሰላም ስምምነቱን ተግባራዊ ለማድረግ እና ለሰላም ቁርጠኛ መሆናቸውን ገለጹ።

    ጠቅላይ ሚኒስተር ዐቢይ አሕመድ ይህን ያሉት በፌደራል መንግሥቱና በህወሓት አመራሮች መካከል በደቡብ አፍሪካ ለአስር ቀናት ሲካሄድ የነበረው የሰላም ንግግር በስምምነት ከተጠናቀቀ በኋላ ባወጡት መግለጫ ነው።

    በሰላም ንግግሩ ሁለቱ አካላት ግጭት ማቆምን እና የህወሓት ኃይሎችን ትጥቅ ማስፈታትን ጨምሮ በ12 ነጥቦች ላይ ከስምምነት ላይ ደርሰዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ትናንት ጥቅምት 23/2015 ዓ.ም. ምሽት በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባጋሩት መግለጫቸው የሰላም ስምምነቱ “ከአራት ዓመት ተኩል በፊት የተጀመረውን ለውጥ ወደፊት ለማራመድ አስተዋጽኦው ከፍተኛ ነው” ብለዋል።

    በመሆኑም የኢትዮጵያ ወዳጆች በጦርነቱ የተጎዱ ሰሜን ኢትዮጵያ አካባቢዎችን መልሶ ለመገንባት እና በአጠቃላይ ላለው ልማት ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመግለጫቸው ጠይቀዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሰላም ንግግሩ ዳር እንዲደርስ ጥረት ላደረጉት አካላትም ምስጋና አቅርበዋል። ለአፍሪካ ሕብረት የአፍሪካ ቀንድ ከፍተኛ ተወካይ ኦሊሴጉን ኦባሳንጆ ፣ ለቀድሞው የኬንያ ፕሬዝደንት ኡሁሩ ኬንያታ፣ ለቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ምክትል ፕሬዚደንት ፋሙዝሌ ላልምቦ፣ ለደቡብ አፍሪካው ፕሬዚደንት ሲሪል ራማፎሳ ምስጋናቸውን ገልጸዋል።

    ከዚህም በተጨማሪ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙሳ ፋኪ መሐመትን ስምምነቱ “ለአፍሪካዊ ችግሮች አፍሪካዊ መፍትሔዎች” በሚለው የአፍሪካ ኅብረት መርኅ እንዲመራ በማድረጋቸው አመስግነዋቸዋል።

    የሰላም ስምምነቱ መቋጫ እንዲያገኝ የነቃ ተሳትፎ ላደረጉ የኢትዮጵያ ወዳጆች፣ ለኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እና ለሕዝባቸው አድናቆታቸውንና ምስጋና ችረዋል።

  8. አሜሪካ ስለሰላም ስምምነቱ ምን አለች?

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ኃላፊ አንቶኒ ብሊንከን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ኃላፊ አንቶኒ ብሊንከን

    በሰሜን ኢትዮጵያ የሚካሄደውን ጦርነት ለማስቆም በአፍሪካ ኅብረት አማካይነት ለተደረሰው ስምምነት አሜሪካ ያላትን ድጋፍ ገለጸች።

    የኢትዮጵያ መንግሥት እና ህወሓት ሁለት ዓመት የሞላውን ጦርነት ለማስቆም መስማማታቸውና የተጀመረውን የሰላም ሂደት ለማጠናከር ንግግራቸውን ለመቀጠል እንዲሁም ያልተገደበ የሰብአዊ እርዳታ እንዲቀርብ፣ ለሰላማዊ ሰዎች ጥበቃ ለማድረግ በመወሰናቸው የአሜሪካ መንግሥት አድናቆቱን ገልጿል።

    በተጨማሪም አሜሪካ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበርንና የኅብረቱ ልዩ ተወካይን እንዲሁም አደራዳሪዎቹ በሰሜን ኢትዮጵያ ሰላም እንዲመጣ ላደረጉት ጥረት እና ደቡብ አፍሪካ ንግግሩን በማስተናገድ ላበረከተችው አስተዋጽኦ አድናቆቷን ገልጻለች።

    የአሜሪካ መንግሥት ባወጣው መግለጫ ላይ ከአፍሪካ ኅብረት፣ ከተባበሩት መንግሥታት፣ ከኢጋድ እና ከሌሎች ጋር በመሆን የተደረሰው ስምምነት ተግባራዊ እንዲሆን በሚደረገው ጥረት ውስጥ ድጋፍ እንምታደርግ ገልጻለች።

    መግለጫው ጨምሮም የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ለአፍሪካ ኅብረት ያቀረቡትን ምስጋና አድንቆ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰሜን ኢትዮጵያ በጦርነቱ የደረሰውን ውድመት መልሶ ለመገንባትና ለልማት ያላቸውን ፍላጎት አሜሪካ እንደምትደረግፍ ገልጿል።

  9. የፕሪቶሪያው ስምምነት በምስል

    በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶርያ በኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት እና በህወሓት መካከል በተደረሰው ስምምነት ላይ አደራዳሪዎች ከተደራዳሪ ወገኖች ጋር
    የምስሉ መግለጫ, በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶርያ በኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት እና በህወሓት መካከል በተደረሰው ስምምነት ላይ አደራዳሪዎች ከተደራዳሪ ወገኖች ጋር
    በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ትቅምት 23/2015 ዓ.ም. የኢትዮጵያ መንግሥት እና የህወሓት ተወካይ ስምምነት ሲፈራረሙ
    የምስሉ መግለጫ, በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ትቅምት 23/2015 ዓ.ም. የኢትዮጵያ መንግሥት እና የህወሓት ተወካይ ስምምነት ሲፈራረሙ
    የኢትዮጵያ መንግሥት ተወካይ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ ሬድዋን ሁሴን እና የህወሓት ተወካይ አቶ ጌታቸው ረዳ የተፈረሙበትን የስምምነት ሰነድ ሲቀባበሉ።
    የምስሉ መግለጫ, የኢትዮጵያ መንግሥት ተወካይ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ ሬድዋን ሁሴን እና የህወሓት ተወካይ አቶ ጌታቸው ረዳ የተፈረሙበትን የስምምነት ሰነድ ሲቀባበሉ።
    የህወሓት ተደራዳሪ ቡድን መሪ የሆኑት አቶ ጌታቸው ረዳ
    የምስሉ መግለጫ, የህወሓት ተደራዳሪ ቡድን መሪ የሆኑት አቶ ጌታቸው ረዳ
    የኢትዮጵያ መንግሥት ተወካዮች ቡድን መሪ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን
    የምስሉ መግለጫ, የኢትዮጵያ መንግሥት ተወካዮች ቡድን መሪ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን
    በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ በኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት እና በህወሓት መካከል በተደረገው ድርድር ላይ የተሳተፉ የህወሓት ተወካዮች
    የምስሉ መግለጫ, በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ በኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት እና በህወሓት መካከል በተደረገው ድርድር ላይ የተሳተፉ የህወሓት ተወካዮች
    በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ በኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት እና በህወሓት መካከል በተደረገው ድርድር ላይ የተሳተፉ የኢትዮጵያ ተወካዮች
    የምስሉ መግለጫ, በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ በኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት እና በህወሓት መካከል በተደረገው ድርድር ላይ የተሳተፉ የኢትዮጵያ ተወካዮች
  10. "አዲስ ምዕራፍ" ከፍቷል የተባለው የፕሪቶሪያው ስምምነት

    የመንግሥት እና የህወሓት ተደራዳሪዎች ድርድሩን ሲያስተባብሩ ከነበሩት ጋር
    የምስሉ መግለጫ, የመንግሥት እና የህወሓት ተደራዳሪዎች ድርድሩን ሲያስተባብሩ ከነበሩት ጋር

    የፌደራል መንግሥት እና የህወሓት መሪዎች መካከል ሲካሄድ የነበረው ድርድር በስምምነት ተጠናቋል።

    ሁለቱ አካላት የደረሱበት ስምምነት ግጭትን የሚያስቆም፣ ትጥቅ የሚያስፈታ፣ የሰብዓዊ እርዳታ እንዲደርስ እና በትግራይ ክልል ሕገ-መንግሥቱ ተፈጻሚ እንሆን የሚያስችል ነው።

    ስምምነቱን የኢትዮጵያን መንግሥት ወክለው አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን በህወሓት በኩል ደግሞ የፓርቲው ማዕካላዊ ኮሚቴ አባሉ ጌታቸው ረዳ ፈርመውታል።