በአብዛኛው የሰሜን ምሥራቅ ኬንያ አካባቢዎች የምርጫ ጣቢያዎች ተከፍተው በሰላም ምርጫ እየተካሄደ ቢሆንም፣ በአንዳንድ ቦታዎች በአል ሻባብ ታጣቂዎች ወከባ እንዲሁም መራጮች ማስፈራሪያ እየደረሳቸው መሆኑን ዘገባዎች አመልክተዋል።
ክልሉ ለሶማሊያ ድንበር ያለው ቅርበት ለአል ሻባብ ጥቃት የተጋለጠ የሚያደርገው ሲሆን፣ አል ሻባብ በክልሉ በአውሮፓውያኑ 2015 የጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ላይ የፈጸመው ጥቃት የሚታወስ ነው።
ሰኞ ምሽት በማንዴራ ግዛት በድንበር አካባቢ በሚገኙ መንደሮች እና ሰፈሮች ላይ ተጠርጣሪ ታጣቂዎች ጥቃት መፈጸማቸው ተሰምቷል።
አጠቃላይ የስልክም ሆነ የኢንተርኔት አገልግሎቶች በአካባቢው የተቋረጡ ሲሆን፣ ከማንዴራ ከተማ በስተምሥራቅ 70 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የምትገኘው አረብ ከተማ ኢላማ እንደተደረገችም ይታመናል።
በድንበሩ አካባቢ ያሉና ግንኙነት ያልተቋረጠባቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ከመገናኛ ብዙኃን ጋር ለመነጋገር ፍቃደኛ አይደሉም።
ለዚህም ዋነኛው ምክንያት በተለይም በምርጫ ወቅት የአል ሻባብ ስጋቶች ከበድ ተደርገው እንዳይነሱ የሚፈልጉ የመንግሥት የፀጥታ አባላትን እንዲሁም ከአል ሻባብ ሊደርስባቸው የሚችለውን የበቀል ጥቃት በመፍራት ነው።
በምሥራቅ ዋጂር ድንበር አካባቢ ነዋሪዎች ወደየምርጫ ጣቢያዎቻቸው እንዳይሄዱ መከልከላቸውንም ዘገባዎች ጠቁመዋል።
በቀርሳ መንደር ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ ነዋሪዎች ታጣቂዎች ተሳፋሪ መራጮች ከሚጓዙበት መኪና ላይ እንዲወርዱ ትዕዛዝ እንደሰጡ እና በኋላ እንዳቃጠሉት ገልጸዋል።
ታጣቂዎቹ የአካባቢው ነዋሪዎች በምርጫው እንዳይሳተፉ ማስጠንቀቂያ ሲሰጡ መቆየታቸውም ይናገራሉ። አስተያየት እንዲሰጡን የዋጂር ግዛት ፖሊስ ኃላፊ ሂላሪ ቶሮይች ቢጠየቁም ምላሽ ማግኘት አልተቻለም።
የምርጫ አስፈፃሚዎች የድምጽ መስጫ ቁሳቁሶችን ወደ ምርጫ ጣቢያዎች ከመላክ እንዲዘገዩ ያስገደዱ ክስተቶች እንደተፈጠሩ ተነግሯል።
- በምሥራቅ ዋጂር ኮንቶን መንደር ከአል ሻባብ ተዋጊዎች ነው ተብሎ የሚታመን ጥይት ከጫካ እየተተኮሰ ነበር።
- ከዋጂር ከተማ በስተምዕራብ በምትገኘው ኤልዳስ የምርጫ ክልል፣ የፓርላማ ተወዳዳሪ ደጋፊዎች የምርጫ አስፈፃሚዎች እንዳይገቡ እየከለከሉ እንደሆነና ብጥብጥ እንዳለ ተነግሯል።
- በኤልዳስ የምርጫ ክልል 72 የምርጫ ጣቢያዎች ድምጽ መስጠት አልተጀመረም። በኤልዳስ ከተማ ሰኞ ማምሻውንም የተኩስ ድምጽ ይሰማ የነበረ ሲሆን፣ ነገርግን ቢቢሲ ምን እንደተፈጠረ ማረጋገጥ አልቻለም።