በኢትዮጵያ በየዕለቱ በኮሮናቫይረስ የሚያዙና የሚያገግሙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው

በኢትዮጵያ በየቀኑ በሚደረገው የኮሮናቫይረስ ምርመራ በሽታው የሚገኝባቸው ሰዎችና ከህመሙ የሚያገግሙ ሰዎች ቁጥር እጨመረ ነው። በዚህም መሰረት የጤና ሚኒስቴርና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ዕሁድ ዕለት ባወጡት ሪፖርት ላይ እንዳመለከቱት እስካሁን 289,550 ሰዎች ላይ ምርመራ ተደርጎ ቫይረሱ 7766 ሲገኝ 4550 ሰዎች ደግሞ አገግመዋል። የባለሙያዎችን ምክር ተግባራዊ በማድረግ እራስን ከቫይረሱ መከላከል እንደሚቻል ይመክራሉ።

የቀጥታ ሽፋን

  1. በኢትዮጵያ በየዕለቱ በኮሮናቫይረስ የሚያዙና የሚያገግሙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው

    ቢቢሲ አማርኛ

    በኢትዮጵያ ተጨማሪ 206 ሰዎች ላይ የኮሮናቫይረስ ሲገኝ 250 ሰዎች ከበሽታው ማገገማቸው ሲነገር የአንድ ሰው ህይወት ደግሞ አልፏል።

    የጤና ጥበቃ ሚኒስቴርና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ዛሬ ባወጡት ዕለታዊ የወረርሽኙ ሁኔታ መግለጫ ላይ እንዳመለከቱት ባለፉት 24 ሰዓታት በአገሪቱ በ3 ሺህ 922 ሰዎች ላይ ምርመራ ተደርጎ 206ቱ ላይ የኮሮናቫይረስ ተገኝቷል።

    በተጨማሪም ቀደም ሲል በወረርሽኙ መያዛቸው ተረጋግጦ የህክምና ክትትል ሲደረግላቸው ከነበሩ ሰዎች መካከል ደግሞ ተጨማሪ 250 ሰዎች ከበሽታው በማገገማቸው በአገሪቱ ከወረርሽኙ ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 4550 ሆኗል።

    ከወረርሽኙ ጋር በተያያዘም የአንድ ሰው ህይወት ማለፉን ዕለታዊው መግለጫ ያመለከተ ሲሆን ውጤቱ የተገኘው በአስከሬን ላይ በተደረገ ምርመራ ላይ ሲሆን በዚህም እስካሁን ድረስ ከኮሮናቫይረስ ጋር በተያያዘ ህይወታቸው ያለፈ ሰዎች ቁጥር 128 ደርሷል።

    በኢትዮጵያ እስካሁን 289 ሺህ 550 ሰዎች ላይ ምርመራ የተደረገ ሲሆን ከእነዚህ መካከልም በአጠቃላይ 7 ሺህ 766 ቫይረሱ ያለባቸውን ሰዎች ተገኝተዋል።

  2. የቦሊውዷ ተዋናይት አይሸዋሪያና ልጇ በኮሮናቫይረስ ተያዙ

    ቤተሰቡ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, አይሸዋሪያ፣ ልጇና ባለቤቷ በቫይረሱ ተይዘዋል

    ሕንዳዊቷ ተዋናይት አይሸዋሪያ ራይ ባቸቻን እና ልጇ በኮሮናቫይረስ መያዛቸው ተገለጸ።

    የአይሸዋሪያ የባለቤቷ አባት ታዋቂው ተዋናይ አሚትባህ ባቸቻን እንዲሁም ባለቤቷ አቢሸክ ቫይረሱ እንደተገኘባቸው የገለጹት ከቀናት በፊት ነበር።

    ሁለቱም ሙምባይ በሚገኝ ሆስፒታል ውስጥ ያሉ ሲሆን፤ በጥሩ ሁኔታ ላይ ናቸው ተብሏል።

    አይሸዋሪያና የስምንት ዓመት ልጇ አራድያ ሆስፒታል ስለመግባታቸው ግን የተባለ ነገር የለም።

    በሌላ በኩል የአሚትባህ ባለቤት ጃያ ባቸቻን ከቫይረሱ ነፃ መሆናቸውን የሕንድ መገናኛ ብዙሀን ዘግበዋል።

    የሙምባይ ማዘጋጃ ቤት በቤተሰቡ መኖሪያ አቅራቢያ “በበሽታው የተበከለ አካባቢ” የሚል ማስታወቂያ ሰቅሏል።

  3. የኮሮናቫይረስ ቅንጣቶች አየር ላይ ከአንድ ሰዓት በላይ እንደሚቆዩ ተገለጸ

    ፕሮፌሰር ዌንዲ ባርክሌ
    የምስሉ መግለጫ, ፕሮፌሰር ዌንዲ ባርክሌ

    በዩናይትድ ኪንግደም በሚገኘው ኢምፔሪያል ኮሌጅ ለንደን ውስጥ በቫይረስ የሚተላለፉ በሽታዎችን የሚያጠኑት ፕሮፌሰር ዌንዲ ባርክሌ፤ የኮሮናቫይረስ ቅንጣቶች ተላላፊ እንደሆኑ በአየር ላይ ከአንድ ሰዓት በላይ ሊቆዩ እንደሚችሉ ተናገሩ።

    ባለፈው ሳምንት የዓለም ጤና ድርጅት፤ ቫይረሱ አየር ወለድ መሆኑን የሚጠቁሙ ማስረጃዎች እንዳሉ ይፋ ማድረጉ ይታወሳል።

    ፕሮፌሰሯ ለቢቢሲ እንዳስረዱት፤ በሽታው አየር ወለድ ሊሆን እንደሚችል ድርጅቱ እውቅና ሲሰጥ የመጀመሪያ ጊዜው ነው።

    “ሌሎችም መተላለፊያ መንገዶች አሉት። ነገር ግን አየር ላይ በሚንሳፈፉ ቅንጣቶች ሊተላለፍ እንደሚችም ተገልጿል” ብለዋል።

    እንደ ተመራማሪዋ ገለጻ፤ ቫይረሱ አየር ላይ ሊቆይ ይችላል። ከተነፈሰው ሰው አልፎ የተወሰነ ርቀት ሊጓዝም ይችላል። በተጨማሪም ወደሌላ ሰው ተላላፊ ሆኖ ከአንድ ሰዓት በላይ ሊቆይ ይችላል።

    በአንድ ክፍል ውስጥ አየር የሚያቀዘቅዝ (ኤር ኮንዲሽነር) ከመጠቀም ይልቅ አየሩን አስወጥቶ ለመቀየር መሞከር የተሻለ እንደሆነም ገልጸዋል።

  4. በቶክዮ በቫይረሱ ከተያዙት 80 በመቶው ከ30 ዓመት በታች ናቸው

    ቶክዮ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የምስሉ መግለጫ, በቶክዮ ትላንት 206 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋገጧል

    በጃፓን መዲና ቶክዮ ትላንት 206 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋገጠ። ለአራት ተከታታይ ቀናት ከ200 በላይ ሰዎች በኮሮናቫይረስ ተይዘዋል።

    የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከተነሳ በኋላ በወረርሽኙ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየናረ ይገኛል። ቶክዮም በሽታውን ለመቆጣጠር እየተጣጣረች ነው።

    በከተማዋ ቫይረሱ ከተገኘባቸው 80 በመቶ የሚሆኑት ከ30 ዓመት በታች መሆናቸውን ኪዮዶ ዘግቧል። ከነዚህ 48ቱ በአንድ ምሽት ክበብ የተገኙ ናቸው ተብሏል።

    ትላንት በመላው ጃፓን በበሽታው የተያዙ ሰዎች ቁጥር 383 ሲሆን፤ 206ቱ የቶክዮ ነዋሪ ናቸው።

    በኪንዋ 61 የአሜሪካ የባህር ኃይል አባላት ቫይረሱ ተገኝቶባቸዋል። ሁለት ወታደራዊ መቀመጫዎች እንቅስቃሴ እንዲያቆሙም ተደርጓል።

  5. በዩናይትድ ኪንግደም ክትባት በቀጣዩ ዓመት ሊደርስ ይችላል ተባለ

    ክትባት

    የፎቶው ባለመብት, IMPERIAL COLLEGE

    ‘ኢምፔሪካል ኮሌጅ ለንደን’ የተባለው የክትባት ምርምር ቡድንን የሚመሩት ፕሮፌሰር ሮቢን ሻቶክ፤ በቀጣዩ ዓመት አጋማሽ በመላው ዩናይትድ ኪንግደም ክትባት ሊዳረስ ይችላል አሉ።

    ክትባቱ ሊደርስ የሚችለው ነገሮች በታቀደው መንገድ ከሄዱ ነው ብለዋል።

    ከስካይ ኒውስ ጋር በነበራቸው ቆይታ 15 ፍቃደኛ ሰዎች ክትባቱ እንደተሰጣቸው ገልጸዋል። በቀጣይ ሳምንታት ከ200 እስከ 300 የሚደርሱ ሰዎች እንደሚከተቡም ተናግረዋል።

    “ሁሉም ነገር በጥሩ ሁኔታ ከሄደ ክትባቱ ይሠራ እንደሆነ የምናውቀው በሚቀጥለው ዓመት መባቻ ነው። ክትባቱን በመላው አገሪቱ ለማዳረስ መሰረተ ልማት መዘርጋት አለብን” ሲሉ ለጋዜጠኛዋ ሶፊ ሪጅ ነግረዋል።

    ክትባቱን ለመግዛት በቂ ድጋፍ ከተደረገ በቀጣዩ ዓመት እንደሚከፋፈልም ተስፋ ያደርጋሉ።

  6. የዩኬው ሌበር ፓርቲ አስገዳጁን ጭምብል የማድረግ ሕግ እደግፋለሁ አለ

    ቦሪስ ጆንሰን

    የፎቶው ባለመብት, Downing Street

    የምስሉ መግለጫ, ቦሪስ ጆንሰን ጭምብል አድርገው ሲሸምቱ

    የዩናይትድ ኪንግደሙ ሌበር ፓርቲ፤ ሰዎች በመገበያያ መደብር ውስጥ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል እንዲያደርጉ የሚያስገድደውን ሕግ እንደሚደግፍ አስታወቀ።

    ጠቅላይ ሚንስትር ቦሪስ ጆንሰን፤ ባለፈው አርብ ጭምብልን በተመለከተ ጥብቅ አመራር ያስፈልጋል ብለው ነበር።

    በሆስፒታልና በሕዝብ ማመላለሻዎች ውስጥ ጭምብል ማድረግ ግዴታ ነው።

    የሌበር ፓርቲዋ ሉሲ ፖዌል፤ መንግሥት አልፎ አልፎ ለመገናኛ ብዙኃን ግልጽ ያልሆነ መግለጫ ከመስጠት ይልቅ፤ አቋሙን በይፋ ማሳወቅ አለበት ብለዋል።

    መገበያያ መደብሮች ውስጥ ሁሉም ሰው ጭምብል ካደረገ፤ ሁሉም ምቾት ተሰምቶት መሸመት ይችላል ሲሉም ተናግረዋል።

  7. በሺዎች የሚቆጠሩ እስራኤላውያን የተቃውሞ ሰልፍ አካሄዱ

    የተቃውሞ ሰልፍ

    የፎቶው ባለመብት, GETTY IMAGES

    የምስሉ መግለጫ, ወጣቶቹ መንግሥት ተገቢውን ምላሽ አለመስጠቱ አስቆጥቷቸዋል

    በእስራኤል፣ ቴል አቪቭ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የተቃውሞ ሰልፍ አካሄዱ። ሰልፈኞቹ መንግሥት ኮቪድ-19 ያሳደረውን የምጣኔ ሀብት ጫና ለመቋቋም አልቻለም ሲሉ ኮንነዋል።

    በራቢን አደባባይ በርካታ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል ያደረጉ ወጣቶች ተገኝተው ተቃውሟቸውን አሰምተዋል። ከመንግሥት የሚጠበቀው የማካካሻ ክፍያ እንደዘገየ ወጣቶቹ ተናግረዋል።

    ሰልፉ የተዘጋጀው አነስተኛ ንግድ ላይ በተሰማሩ፣ የራሳቸውን ሥራ በሚሠሩና በሥነ ጥበብ ባለሙያዎች ነው።

    ኮሮናቫይረስ መተዳደሪያቸውን ያሳጣቸው እነዚህ ሰዎች፤ መንግሥት ተገቢውን ምላሽ አለመስጠቱ አስቆጥቷቸዋል።

  8. ታዋቂው የቦሊውድ ተዋናይ አሚታብ ባቻን በኮሮናቫይረስ መያዙን ገለፀ

    ተዋናዩ አሚታብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በሕንድ የፊልም ኢንዱስትሪ ዘርፍ ውስጥ ከፍተኛ ዝናን የተጎናፀፈው ተዋናዩ አሚታብ ባቻን በኮሮናቫይረስ መያዙን በሚሊዮን ለሚቆጠሩ ተከታዮቹ በትዊተር ገፁ አስፍሯል።

    "በኮሮናቫይረስ ተይዣለሁ። ሌላ ሆስፒታልም ገብቻለሁ። ሆስፒታሉ ባለስልጣናቱን አሳውቀዋል። ቤተሰቦቼና ሰራተኞቼም ምርመራ አከናውነዋል። ውጤታቸውንም እየጠበቁ ነው" በማለት ተዋናዩ በትዊተር ገፁ አስታውቋል።

    የተዋናዩ ልጅ አቢሂሸክም በቫይረሱ መያዙንም እንዲሁ በትዊተር ገፁ አስፍሯል።

    የ77 አመቱ አሚታብ ለአምስት አስርት ዓመታት ያህል በሕንድ የፊልም ዘርፍ መግነን የቻለ ሲሆን ከ200 በላይ ፊልሞችም ላይ ተውኗል።

    እሱም ሆነ የ44 ዓመት ልጁ ሙምባይ በሚገኘው ናንቫቲ ሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸው ሲሆን፤ መካከለኛ ምልክት እያሳዩ ነው ተብሏል።

    አሚታብ በባለፉት አስር ቀናት ከሱ ጋር ግንኙነት የነበራቸው ሰዎች በሙሉ ምርመራ እንዲያደርጉ መልእክቱንም አስተላልፏል።

  9. ፕሬዚዳንት ትራምፕ በአደባባይ ጭምብል አድርገው ታዩ

    ፐሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, REUTERS

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለመጀመሪያ ጊዜ በአደባባይ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል አድርገው ታዩ።

    ፕሬዚዳንቱ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ መዛመት ከጀመረ ወዲህ ጭምብል እንደማያደርጉ ሲናገሩ እንደነበር ይታወሳል።

    ትራምፕ ‘ዋልተር ሪድ’ የተባለ ወታደራዊ ሆስፒታል በጎበኙበት ወቅት ነበር ጭምብል ያደረጉት። ከቆሰሉ ወታደሮችና የጤና ባለሙያዎች ጋር ተገናኝተዋል።

    “ጭምብል በማድረግ አላምንም አላልኩም። ሆኖም ጊዜና ቦታ አለው” ብለዋል ፕሬዚዳንቱ።

    ከዚህ ቀደም የዴሞክራት እጩው ጆ ባይደን ጭምብል በማድረጋቸው ሲሳለቁባቸው ነበር።

    ሆስፒታሉን በጎበኙበት ወቅት ግን “ሆስፒታል ውስጥ ስትሆኑ፣ በተለይም ቀዶ ህክምና ከተደረገላቸው ወታደሮች ጋር ስታወሩ ጭምብል ማድረግ አስፈላጊ ነው” ብለዋል።

    ባለፈው ሳምንት ከፎክስ ቢዝነስ ኔትወርክ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ጭምብል ማድረግን እንደሚደግፉ ተናግረዋል።

  10. አሳሳቢው ምልክት የማያሳዩ ግን በሽታውን የሚያዛምቱ ሰዎች ነገር

  11. እንደምን አደራችሁ? የቀጥታ ዘገባችን ተጀምሯል

    የቢቢሲ አማርኛ ወዳጆች እንደምን አደራችሁ? የሀምሌ 5 ቀን 2012 ዓ. ም. የቢቢሲ አማርኛ የቀጥታ ዘገባ ገጽ ተጀምሯል። ከአገር ውስጥና ከውጪም የተለያዩ ዘገባዎችን እናቀርብላችኋለን።

    ራሳችሁን ከኮሮናቫይረስ ለመከላከል ተገቢውን ጥንቃቄ ማድረግ አትዘንጉ። ከቻላችሁ ቤት ሁኑ፣ ከቤት ከወጣችሁም አካላዊ ርቀታችሁን ጠብቁ።

    ሰው በተሰበሰበበት አካባቢ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭንብል ማድረግ እንዲሁም እጃችሁን አዘውትራችሁ መታጠብም አትዘንጉ።

    መልካም ቀን!

    ጭምብል
  12. በኢትዮጵያ 158 የኮሮናቫይረስ ሲገኝባቸው 154 አገገሙ 3 ሰዎች ደግሞ ሞቱ

    ቢቢሲ አማርኛ

    በኢትዮጵያ ተጨማሪ 158 ሰዎች ላይ የኮሮናቫይረስ ሲገኝ 154 ከበሽታው ማገገማቸው ተነግሯል። በተጨማሪም የሦስት ሰዎች ህይወት ከበሽታው ጋር በተያያዘ አልፏል።

    የጤና ጥበቃ ሚኒስቴርና የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ዛሬ ባወጡት ዕለታዊ የወረርሽኙ ሁኔታ መግለጫ ላይ እንዳመለከቱት ባለፉት 24 ሰዓታት በአገሪቱ በ4 ሺህ 559 ሰዎች ላይ ምርመራ ተደርጎ 158ቱ ላይ የኮሮናቫይረስ ተገኝቷል።

    ከዚህ ባሻገር ቀደም ሲል በወረርሽኙ መያዛቸው ተረጋግጦ የህክምና ክትትል ሲደረግላቸው ከነበሩ ሰዎች መካከል ደግሞ ተጨማሪ 154 ሰዎች ከበሽታው በማገገማቸው በአገሪቱ ከወረርሽኙ ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 4306 ሆኗል።

    ከወረርሽኙ ጋር በተያያዘም የሦስት ሰዎች ህይወት ማለፉን ዕለታዊው መግለጫ ያመለከተ ሲሆን ከሟቾቹ መካከል ሁለቱ በህክምና ማዕከል ውስጥ የነበሩ ሲሆኑ አንደኛው ግን በአስከሬን ላይ በተደረገ ምርመራ የተገኘ መሆኑ ተገልጿል።

    በዚህም እስካሁን ድረስ ከኮሮናቫይረስ ጋር በተያያዘ ህይወታቸው ማለፉ የተመዘገበ ሰዎች ቁጥር 127 ደርሷል።

    በኢትዮጵያ እስካሁን 285 ሺህ 628 ሰዎች ላይ ምርመራ የተደረገ ሲሆን ከእነዚህ መካከልም በአጠቃላይ 7 ሺህ 560 ቫይረሱ ያለባቸውን ሰዎች ተገኝተዋል።

  13. 'የኮሮናቫይረስ መድኃኒት ለሁሉም መዳረስ አለበት' - ቢል ጌትስ

    ቢል ጌትስ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አሜሪካዊው ቢሊዬነር ቢል ጌትስ፤ የኮሮናቫይረስ መድኃኒትና ክትባት በጨረታ የሚሰጥ ከሆነ በሽታው ሊጠፋ እንደማይችል አስጠንቅቀዋል።

    ጌትስ፤ የኮሮናቫይረስ መድኃኒቶች ለሁሉም እኩል መዳረስ አለባቸው ብለው ያምናሉ።

    መድኃኒቶች እንዲሁም ክትባቶች ከፍተኛ ዋጋ ላቀረበ ተጫራች የሚሰጡ ከሆነ "ፍትሃዊ ያልሆነ የተራዘመ ወረርሽኝ ይጠብቀናል" ሲሉ ነው ያስጠነቀቁት።

    የአሜሪካና የአውሮፓ አገራት መንግሥታት በተለያዩ የክትባት ምርምሮች ላይ በርካታ ሚሊዮን ዶላሮች እያፈሰሱ ነው። ይህ ደግሞ ሃብታም አገራት ቀድመው መድኃኒቱን ለራሳቸው ያደርጉታል የሚል ስጋት አጭሯል።

    የአውሮፓ ሕብረትና የዓለም ጤና ድርጅት ጤናማ ያልሆኑ አላስፈላጊ ፉክክሮች መወገድ አለባቸው ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    አንዳንድ የአሜሪካ ባለሥልጣናት መድኃኒቱን ለአሜሪካ ዜጎች ከሁሉ ቀድሞ ለማቅረብ ጥረት እያደረጉ እንደሆነ መነገሩ ይታወሳል።

  14. "ቫይረሱ ለወራት አብሮን ይቆያል" አውስትራሊያዊው አስተዳዳሪ

    ቪክቶሪያ፤ አውስትራሊያ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ እያንሰራራባት በመሆኑ ጥብቅ እርምጃ እየወሰደች ያለችው የአውስትራሊያዋ ግዛት ቪክቶሪያ አስተዳዳሪ ቫይረሱ ከዚህም በኋላ “ለበርካታ ወራት አብሮን ይቆያል” ሲሉ ተናገሩ።

    ዳንኤል አንድሪውስ ይህንን ማስጠንቀቂያ የተናገሩት በግዛቲቱ በአንድ ቀን እስካሁን ከተመዘገበው ከፍተኛ የተባለው የህሙማን ቁጥር በመመዝገቡ ነው።

    በቪክቶሪያ ግዛት ከፍተኛ የተባለው ቫይረሱ የተገኘባቸው 216 ሰዎች ሲሆኑ የአንድ ሰው ህይወት ደግሞ በበሽታው ሰበብ አልፏል።

    አምስት ሚሊዮን ነዋሪዎች ያሉባት ሜልበርንና በዙሪያዋ ያሉ አንዳንድ አካባቢዎች ላይ በድጋሚ የተጣለው የእንቅስቃሴ ገደብ አንድ ሳምንት ሆኖታል።

    አስተዳዳሪው በቴሌቪዥን ቀርበው ለሕዝቡ ባስተላለፉት መልዕክት "ማንም ሰው ከቤት እንዳይወጣ በመደረጉ ደስተኛ አይደለም። ተስፋ የሚያስቆርጥና ፈታኝ ሁኔታ ነው፤ ነገር ግን የተወሰደው እርምጃ ውጤታማ እንዲሆን ሁላችንም የበኩላችንን መወጣት አለብን” ብለዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ በአጎራባቿ ኒው ሳውዝ ዌልስ ግዛት ውስጥ ሰባት ህሙማኖች የተገኙ ሲሆን አንደኛው ግለሰብ ሲድኒ ውስጥ ሁለት በበሽታው የተያዙ ሰዎች የተገኙበት መጠጥ ቤት ውስጥ ገብቶ እንደነበር ተገልጿል።

    ባለፈው ሳምንት ቪክቶሪያ ውስጥ ባለው የወረርሽኝ ክስተት ሳቢያ ኒው ሳውዝ ዌልስ ከአንድ መቶ ዓመት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ከቪክቶሪያ ጋር ያላትን ድንበር ዘግታለች።

  15. በሕንድ በወረርሽኙ የሚያዙ በመጨመራቸው ግዛቶች እርምጃ እየወሰዱ ነው

    ሕንድ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    በዓለም ከፍተኛው ቁጥር ያላቸው በኮሮናቫይረስ የተያዙ ሰዎች ካሉባቸው አገራት መካከል በሦስተኛ ደረጃ ላይ በምትገኘው ሕንድ ውስጥ የህሙማኑ ቁጥር ከ820 ሺህ በላይ ሆነ።

    ትናንት አርብ በአንድ ቀን ውስጥ ከፍተኛው የሆነ ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች የተመዘገቡ ሲሆን በዚህም ከ27 ሺህ 114 በላይ አዲስ ህሙማን ተገኝተዋል ተብሏል።

    በተጨማሪም ወረርሽኙ በሕንድ ውስጥ መኖሩ በይፋ ከተነገረ ወዲህ እስካሁን ድረስ በአጠቃላይ 22 ሺህ 123 ሰዎች በበሽታው ሰበብ ለሞት ተዳርገዋል።

    ቢሆንም ግን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር እንዳለው ከቫይረሱ የሚያገግሙ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ሲሆን አሁን በበሽታው ከተያዙት 62 በመቶው ማገገማቸውን አመልክቷል።

    በአገሪቱ ውስጥ ያሉ አስራ ሁለት የሚጠጉ ግዛቶች የበሽታውን መስፋፋት ለመግታት በሚል ከፊል የእንቅስቃሴ ገደብ ጥለዋል።

    በተያኣዘ በዋና ከተማዋ ዴለልሂ ውስጥ የሚገኙ ሁሉም ዩኒቨርስቲዎች ፈተናዎችን የሰረዙ ሲሆን ተማሪዎችም ቀደም ሲል ባመቷቸው ውጤቶች አማካይነት እንደሚመዘኑም ተገልጿል።

  16. ኢራን ለሁለተኛ ጊዜ የእንቅስቃሴ ገደብ መጣል እንደማትችል አስታወቀች

    ሐሰን ሩሃኒ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የኢራኑ ፕሬዝደንት ሐሰን ሩሃኒ በአገራቸው መልሶ እየጨመረ ያለውን የኮሮናቫይረስ ህሙማን ቁጥርን በማስመልከት፤ የበሽታውን መስፋፋት ለመቆጣጠር ሲባል አገሪቱ የምጣኔ ሐብት እንቅስቃሴዎችን ለመዝጋት እንደማትችል አስጠነቀቁ።

    ፕሬዝደንቱ ይህንን የተናገሩት ዛሬ [ቅዳሜ] በቴሌቪዥን በተላለፈ ስብሰባ ላይ ነው። ሩሃኒ፤ በአገሪቱ ውስጥ “ምጣኔ ሐብታዊ፣ ማኅበራዊና ባሕላዊ እንቅስቃሴዎች ተገቢውን የጤና መመሪያዎች ተግባራዊ በማድረግ” እንዲቀጥሉ መክረዋል።

    በኢራን ተጥሎ የነበረው የእንቅስቃሴ ገደብ የተነሳው በሚያዚያ ወር ላይ ነበር። ገደቡ የተነሳው በአገሪቱ ምጣኔ ሐብት ላይ ከባድ ጫናን ስለተፈጠረ ነው ሲሉ የአገሪቱ ጤና ሚኒስትር ተናግረዋል።

    በወረርሽኙ ምክንያት ሐሙስ ዕለት 221 ሰዎች መሞታቸው የተመዘገበ ሲሆን ይህም በአንድ ቀን ያጋጠመ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሞት ነው።

    የኮሮናቫይረስ ክፉኛ ካጠቃቸው የዓለም አገራት መካከል አንዷ የሆነችው ኢራን ወረርሽኙ ከተከሰተ በኋላ እስካሁን ድረስ ከ12,400 ዜጎቿን በቫይረሱ ሰብብ አጥታለች።

  17. በኮሮናቫይረስ ምክንያት የቀረው የሞት ቅጣት

    በኮሮናቫይረስ ምክንያት የቀረው የሞት ቅጣት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በአሜሪካዋ የኢንዲያና ግዛት ውስጥ ያለ ፍርድ ቤት አንድ ወንጀለኛ ላይ ተደርዶ የነበረን የሞት ቅጣት በኮሮናቫይረስ ምክንያት እንዲሰረዝ ወስኗል።

    የፍርደኛው ቤተሰቦች በኮሮናቫይረስ ምክንያት ከግዛት ወደ ግዛት መንቀሳቀስ ባለመቻላቸው የሞት ቅጣቱን መከታተል አንችልም በማለታቸው ነው ፍርድ ቤቱ ብይኑ እንዲቀር የወሰነው።

    ዳንዜል ሊ የተሰኘው ግለሰብ በሚቀጥለው ሰኞ ነበር የሞት ፍርድ ይፈጸምበታል ተብሎ የሚጠበቀው። በግዛቲቱ ይህ የሞት ፍርድ ሲበየን ከ17 ዓመታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ነበር።

    ወንጀለኛው የሞት ፍርድ የተፈረደበት አርካንሳስ ግዛት ውስጥ አንድ የጦር መሣሪያ ሻጭን እንዲሁም ባለቤቱንና የስምንት ዓመት ሴት ልጁን ገድሏል ተብሎ ነው።

    የሟች ቤተሰብ የሆኑ ሴት ቤተሰባቸውን የገደለው ግለሰብ የሞት ቅጣት ሲቀበል ማየት ባለመቻላቸው ፍርዱ ይቅር ቢባልም የግለሰቧ ጠበቃዎች ዶናልድ ትራምፕ ብይኑን እንዲያፀድቁ ጠይቀዋል።

    የአሜሪካ ፍትህ ሚኒስቴርም የዳኛው ውሳኔ ትክክል አይደለም ሲል ተቃውሞውን አሰምቷል።

  18. ፈረንሳይ ጥላው የነበረው የጤና አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አበቃ

    ምርመራ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    ፈረንሳይ በግዛቶቿ ውስጥ ለወራት ጥላው የነበረው “የጤና አሰቸኳይ ጊዜ” ሕግ አርብ እኩለ ሌሊት ላይ አበቃ።

    የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ አሳሳቢ መሆኑ ከተገለጸ በኋላ ግንቦት ላይ ያበቃል ተብሎ መጋቢት ወር ላይ ሕጉ የተላለፈው ቢሆንም እስከ ትላንት ድረስ እንዲራዘም ተደርጎ ቆይቷል።

    ደንቡ ቢያበቃም ይህ ነው የሚባል ተግባራዊ ለውጥ እንደማይኖር ተነግሯል። የፈረንሳይ መንግሥት አዲስ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እስካልደነገገ ድረስ ቀደም ሲል የተጣለውን ደንብ ከዛሬ ቅዳሜ በኋላ ማራዘም አይችልም ነበር።

    መንግሥት ቀደም ሲል ተጥሎ የነበረው የአስቸኳይ ጊዜ ሕግ እንዲኣበቃ ያደረገው የወረርሽኙ የመስፋፋት መጠን ላይ ይቀንሳል የሚል ተስፋ ስላለው ነው።

    ነገር ግን ባለሙያዎች በሽታው ሊያገረሽ ይችላል የሚል ስጋት ያላቸው ሲሆን በአንዳንድ ቦታዎች ላይም በርከት ያሉ ቫይረሱ ያለባቸው ሰዎች ስለተገኙ በሚቀጥለው ሳምንት የጅምላ ምርመራ ይደረጋል ተብሏል።

    የፈረንሳይ መንግሥት ዋና የጤና አማካሪ “ወጣቶች አካላዊ ርቀትን የመጠበቅን ነገር ሙሉ ለሙሉ እርግፍ አድርገው ትተውታል” ሲሉ አማረዋል።

    በሽታው ለሁለተኛ ዙር ቢያገረሽ ካለው ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጫና የተነሳ ፈረንሳይ በመላው አገሪቱ የእንቅስቃሴ ገደብ ለመጣል የሚያችል የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከዚህ በኋላ ታወጣለች ተብሎ አይታሰብም።

    ከዚህ ይልቅ የፈረንሳይ መንግሥት በተለይ በቫይረሱ በድጋሚ በሚጠቁ ውስን አካባቢዎች ላይ የእንቅስቃሴ ገደብ ለመጣል የሚያስችል ስልጣን የሚሰጠውንና ባለፈው ሳምንት የጸደቀው ሕግ መጠቀም ይችላል ተብሏል።

  19. ቤልጂየም ጭምብል ማድረግን ግዴታ አደረገች

    ጭምብል

    የፎቶው ባለመብት, Empics

    መደብሮችና ሲኒማ ቤቶችን በመሳሰሉ ሕዝብ በሚሰበሰብባቸው ቦታዎች ላይ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል መጠቀም ግዴታ መሆኑን ቤልጂየም አሳወቀች።

    ይህንን ግዴታ ተግባራዊ ሳያደርጉ የተገኙ ሰዎችም 250 ዩሮ (281 ዶላር) እንደሚቀጡ ታውቋል።

    አዲሱ መመሪያ ይፋ የተደረገው ዛሬ ሲሆን ሕዝብ ይሰበሰብባቸዋል ተብለው ከተለዩት ቦታዎች ውስጥም ሙዚየሞች፣ ቤተ መጽሐፍት፣ ፍርድ ቤቶች የቁማር ቦታዎች ን ይጨምራል።

    የገበያ አዳራሾች በመግቢያ በሮች ላይ ደንበኞቻቸው ጭምብል እንዲያደርጉ የሚያስታውሱ ሠራተኞችን እንዲያቆሙ የተደረጉ ሲሆን በተጨማሪ ያለክፍያ ጭምብሎችን መስጠትም ይጠበቅባቸዋል።

    ይህንን መመሪያ ተግባራዊ ሳያደርጉ የተገኙ ተቋማት የ750 ዩሮ የገንዘብ ቅጣት ይጠብቃቸዋል።

    በተጨመሪም በተደጋጋሚ ይህንን የጤና ግዴታ ጥሰው ከተገኙ ደግሞ ቅጣቱ በከፍተኛ መጠን ጨምሮ 4ሺህ ዩሮ ሊደርስ የሚችል ሲሆን በአንዳንድ ሁኔታዎችም ከስምንት ቀናት አስከ ሦስት ወራት የሚደርስ የእስር ቅጣት ሊያስከትል ይችላል ተብሏል።

    ቤልጂየም ከዚህ ቀደም በተለይ በሕዝብ መጓጓዣ አገልግሎቶች ላይ ወይም ጸጉር አስተካካዮችን ጨምሮ ከተገልግዮች ጋር የቅርብ ንክኪ ባላቸው ሙያዎች ላይ የተሰማሩ ሰዎች ጭምብል እንዲያደርጉ መመሪያ አውጥታ ቆይታለች።

  20. ፍሎሪዳ የኮሮናቫይረስ ቢያገርሽባትም የሕዝብ መዝናኛዎችን መክፈት ጀምራለች

    ዋልት ዲዝኒ የመዝናኛ ሥፍራ

    የፎቶው ባለመብት, Getty

    በአሜሪካዋ ፍሎሪዳ ግዛት ውስጥ የሚገኘው ዋልት ዲዝኒ የተሰኘው የመዝናኛ አምባ ለሕዝብ ክፍት እንደሚሆን ተነግሯል።

    ምንም እንኳ በግዛቲቱ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ እንደ አዲስ ቢያገረሽም ሥፍራው ከወራት በኋላ ዛሬ እንደሚከፈት ይጠበቃል።

    ፓርኩ በደረጃ እንደሚከፈት የታወቀ ሲሆን የሚያስተናግደው የሰው መጠንም ከዚህ በፊት ከነበረው ዝቅ ያለ እንደሚሆን ይጠበቃል።

    ጎብኚዎችና የአምባው ሠራተኞች የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል ማጥለቅ ግድ ይላቸዋል። አልፎም ደንበኞች የሰውነት ሙቀት መጠናቸው ወደ ፓርኩ ከመግባታቸው በፊት ይለካል።

    ፍሎሪዳ ዕለተ አርብ ብቻ ከ11 ሺህ በላይ ነዋሪዎች በቫይሱ እንደተያዙባት ይፋ አድርጋለች። 93 ሰዎች ደግሞ በቫይረሱ ምክንያት ሞተዋል።

    ይህን ተከትሎ በግዛቲቱ የሚገኙ አንዳንድ ከተሞች የእንቅስቃሴ ገደብ እንደ አዲስ መጣል ጀምረዋል።