የደቡብ አፍሪካውያን የ30 ዓመታት የነጻነት ጉዞ እና ኤኤንሲ የሚፈተንበት ቀጣዩ አጓጊ ምርጫ

በደቡብ አፍሪካዋ ሶዌታ ለምርጫ የወጡ ሰዎች

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

የምስሉ መግለጫ, ከሦስት አስርት ዓመት በፊት በደቡብ አፍሪካዋ ሶዌታ ለምርጫ የወጡ ሰዎች

ደቡብ አፍሪካ ምርጫ ልታካሂድ ተቃርባለች። ለመሆኑ ያለፉት 30 የዲሞክራሲ ዓመታት እንዴት አለፉ? ከዘረኛው የአፓርታይድ ሥርዓት ካከተመ በኋላ ምን ለውጥ መጣ? የቢቢሲዋ ኖምሳ ማሴኮ ትዝታዋን መለስ ብላ ታስታውሳለች።

እናቴ ለመጀመሪያ ጊዜ በምርጫ የተሳተፈችው እአአ በ1994 ነው። ካርዷን ኮሮጆ ውስጥ ስትከት “ከእስር ቤት የመውጣት ካርድ” እንደሆነ እየተሰማት እንደነበር ገልጻለች።

በወቅቱ 43 ዓመቷ ነበር። እንደ ሌሎች በሚሊዮን የሚቆጠሩ ደቡብ አፍሪካውያን ለመጀመሪያ ጊዜ ነበር በምርጫ የተሳተፈችው።

ከዘረኝነት እና ከጨካኝ የነጭ አናሳ አገዛዝ ሥርዓት ጋር ለአስርት ዓመታት የዘለቀ ተቃውሞ እና የትጥቅ ትግል የወለደው ምርጫ ነበር።

በወቅቱ በጣም ልጅ ስለነበርኩ የምርጫ አስፈፃሚዎች ጣቴን እንደመረጠ ሰው ቀለም እንዳስነካ ፈቅደውልኝ ነበር። እናቴ እና ብዙሃኑ ጥቁሮች ነፃ መውጣታቸውን ተከትሎ የራሳቸውን መንግሥት መምረጥ ምን ማለት እንደሆነ አይታለች።

ከምርጫው በፊት ፖለቲካዊ ብጥብጥ ይኖራል የሚል ከፍተኛ ስጋት ነበር። ከጆሃንስበርግ በስተምሥራቅ በምትገኘው እና የምኖርባት ክዋ-ቲማ አካባቢ አየር በአስለቃሽ ጭስ ተሞልቶ ነበር።

ከ1994 ምርጫ በፊት ግጭት ይኖራል የሚል ስጋት ነበር

የፎቶው ባለመብት, AFP

የምስሉ መግለጫ, ከ1994 (እአአ) ምርጫ በፊት ግጭት ይኖራል የሚል ስጋት ነበር

ወታደራዊ ተሽከርካሪዎች በቤታችን አቅራቢያ በቀንም በምሽትም ሲመላለሱ ዋሉ። ከርቀትም የተኩስ ድምጽ ተደጋግሞ ይሰማ ነበር።

ከምርጫው ቀን በፊት ከጓደኞቼ ጋር እየተጫወትን ሳለ አንድ ነጭ መኪና የፓርቲ ቲሸርቶችን፣ ኳሶችን እና ባንዲራዎችን ጭኖ መጣ።

ይህ ፓርቲ ነው እአአ በ1948 ወደ ሥልጣን የመጣው። አፓርታይድ የሚባለውን ሕጋዊ የዘር ልዩነትን የደነገገው ይህ ፓርቲ ነው።

ብዙዎቻችን ከዚያ በፊት አዲስ ኳስ ይዘን አናውቅም ነበር። ስለዚህ በነፃ ሲሰጠን በጣም ተደስተናል። ደስታችን ግን ብዙም አልቆየም።

“ጓዶች” የሚባሉት የፀረ አፓርታይድ አክቲቪስቶች ሁሉንም ነጠቁን። ቲሸርቶቹን ቀምጠው አቃጠሉት። ኳሶቹን በቢላዋ ቀደዷቸው።

“ከአሁን በኋላ ከጠላት ምንም አትቀበሉ” ተብለን ተገሰጽን። ብናዝንም ግን ምክንያቱ ገብቶናል።

የድምጽ መስጫው ቀን ደረሰ። ጸጥ ረጭ ያለ ቀን ነበር። ቀኑ ፀሐያማ ቢሆንም አየሩ በፍርሃት እና በጭንቀት ተሞልቷል።

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

የምርጫ ጣቢያው ከቤታችን ትይዩ በሚገኘው መምህራን ኮሌጅ ነበር። ሠላምን የሚሰብኩ በርካታ ሰማያዊ እና ነጭ ባንዲራዎች ከፍ ብለው ይውለበለቡ ነበር። በፓርቲያቸው ቀለም ያሸበረቁ ልብሶችን የለበሱ የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች ከቤት ቤት እያንኳኩ ሕዝቡ ወጥቶ እንዲመርጥ ይቀሰቅሱ ነበር።

እንደ እባብ የተጥመለመለው ወረፋ ለብዙ ኪሎ ሜትሮች ተዘርግቶ ነበር። ወጣቶች እና አዛውንቶች ተሰልፈው እጆቻቸውን ወደ ላይ ከፍ በማድረግ “ሲኩሉሌኪሌ” ይሉ ነበር። በዙሉ ቋንቋ “ነጻነታችንን ተቀዳጀን” እንደማለት ነው።

የተለየ ስሜት እየተሰማኝ ነበር። ፈረስ ላይ የተቀመጡ ነጭ ፖሊሶች ሲያልፉ ማየት እና መደበቅ እንደማያስፈልገኝ በመረዳቴ ሁሉ ነገር ቀለለኝ።

ጀርመን ሺፐርድ የሚባለውን የውሻ ዝርያ አሁንም እፈራለሁ። የአፓርታይድ ፖሊሶች ከአነፍናፊነት እና ከጥበቃ በተጨማሪ ህጻናት ሆነን ያለምንም ምክንያት ውሾቹን ይለቁብን ስለነበር ነው።

በሶዌቶ ከተማ ኦርላንዶ ዌስት ሰፈር ስላለው የነጻነት ትግል ብዙ አዎንታዊ ትዝታዎች አሉኝ።

በ1994 የአፍሪካ ብሔራዊ ኮንግረስ (ኤኤንሲ) አሸንፎ ፕሬዝዳንት የሆኑት ኔልሰን ማንዴላ እና ሊቀ ጳጳስ ዴዝሞንድ ቱቱ በአንድ ወቅት በኖሩበት የቪላካዚ ጎዳና ላይ ሳክሁምዚ ማቁቤላ ታዋቂ ሬስቶራንት አላቸው።

“ቱሪዝም ለቪላካዚ ጎዳናን ብዙ ጥቅም ሰጥቷል። ደቡብ አፍሪካ ምን እንደ ሆነች ለማየት የመጡ ቱሪስቶች ላይ ታች እያሉ ሲጎበኙ በመመልከቴ ምግብ መሸጥ ለመጀመር ወሰንኩ” ብለዋል።

ማቁቤላ ላለፉት ሦስት አስርት ዓመታት ያደረጉትን ጥረት ከአገሪቱ መሪዎች ጋር ያመሳስሉታል።

“ያለፉት 30 ዓመታት ለመንግሥታችን የሙከራ ጊዜያቶች ናቸው። እነሱ እየተማሩ በመሆናቸውን ነጥብ ልንሰጣቸው እንችላለን።”

“500 የሥራ ዕድል በመፍጠሬ እና ጥረቴ ለውጥ እንዳመጣ በማወቄ እፎይ ብዬ እተኛለሁ።”

ላለፉት ዓመታት ብዙም ለውጥ ያላው ክሊፕታወን
የምስሉ መግለጫ, ላለፉት ዓመታት ብዙም ለውጥ ያላው ክሊፕታውን

የመጀመሪያዎቹ የዲሞክራሲ ዓመታት ተስፋ ሰጪ ነበሩ። የማንዴላ የመጀመሪያ የሥልጣን ዘመን ላይ ተሳታፊ የነበሩት ታቦ ምቤኪ ቀጣዩን ምርጫ አሸንፈዋል። ሲቪል ማኅበረሰቡም፣ ሐሳብን መግለጽ እና ነፃው ፕሬስ አደገ።

ለኢኤንሲ የጫጉላ ሽርሽሩ ማብቃቱን ብዙዎች በእርግጠኝነት እየተናገሩ ነው። በሙስና እና በውስጣዊ ሽኩቻ እየተራኮተ ይገኛል። አገሪቱ ከፍተኛ ሥራ አጥነት እና ወንጀል ከፊቷ ተደቅኗል። በርካቶች አሁንም እንደ ውሃ እና መብራት ባሉ መሠረታዊ አገልግሎቶች እጦት እየተሰቃዩ ነው።

ማቁቤላ ያገኙት ዲሞክራሲያዊ ትርፍ በቪላካዚ ሴንት አካባቢ ካለው አካባቢ ብዙም ሊስፋፋ አልቻለም።

10 ደቂቃ በመኪና ሲጓዙ ክሊፕታውን ውስጥ እምብዛም የማይጸዱ ወይም ባዶ የሆኑ ተንቀሳቃሽ መጸዳጃ ቤቶች ጎዳናው ላይ ተሰልፈዋል።

በመኖሪያ አካባቢዎቹ ሺቢንስ በመባል የሚታወቁ በርካታ መጠጥ ቤቶች እንጂ ብዙ ትምህርት ቤቶች የሉም። ወጣት እናቶች ከዚህ ለማለፍ እየታገሉ ነው።

“የሰላሳ ዓመት ዲሞክራሲ ለእኔ ምንም ማለት አይደለም። የሚከበርበት ምንም ነገርም የለም” ስትል ቤቷ በራፍ ላይ ሆና የተናገረችው ታስኒማ ሲልቬስተር ናት።

“ኤኤንሲ ሠራሁ የሚለውን ነገር ስላላየሁ በዚህ ዓመት ድምጽ ስለመስጠት አላሰብኩም” ስትል የ38 ዓመቷ የሦስት ልጆች እናት ተናግራለች።

“ሥራ፣ ንጹህ ውሃ እና ሽንት ቤት የለኝም። ተናዳጅ እና ተስፋ የለሽ ሆኛለሁ።”

የሲልቬስተር ታሪክ የዛሬዋ ደቡብ አፍሪካ እውነታ ሆኖ ይንጸባረቃል። በሌላቸው እና ባላቸው መካከል ያለው ልዩነት ሰፊ ሆኗል።

የአውሮፓውያኑ 1955 የነጻነት ቻርተር የተፈረመው በክሊፕታውን ነው። ቻርተሩ ታጋዮች ለደቡብ አፍሪካ ነጻነት ያላቸው ራዕይ ያስቀመጡበት ነው።

የክሊፕታውን ነዋሪዎች ከነጻነት ትግሉ ጋር ያላቸው ግንኙነት ችላ እንደተባለ ይሰማቸዋል።

“ለረጅም ጊዜ ችላ ተብለን ነበር። ከ10ሩ የነፃነት ቻርተር አንቀጾች አንዳቸውም በዚህ ሰፈር ውስጥ አለመተግበራቸው በጣም ያሳዝናል” ሲል የአካባቢው አስጎብኚ ንቶኮዞ ዱቤ ይገልጻል።

የነጻነት ቻርተር

የፎቶው ባለመብት, BBC/Thuthuka Zondi

የምስሉ መግለጫ, የደቡብ አፍሪካ የነጻነት ቻርተር

ለፖለቲካ ተንታኟ ቴሳ ዱምስ 30ኛው ነጻነት በዓል ላይ ከግምት ውስጥ የሚገቡ ከባድ ጥያቄዎች አሉ ትላለች።

“ሰዎች የአገራችንን ግንባታ በመሠረታዊነት የቀየርን አይመስላቸውም” ስትል ተናግራለች።

“አሁንም ካለፈው ጋር በጣም ተመሳሳይ የሆኑ አንዳንድ በጉልህ የሚታዩ ነገሮች አሉ . . . ከፍተኛ ደረጃ ያለው ኢ-እኩልነት ቀጥሏል። በዲሞክራሲያዊው ዘመን ደግሞ ይባስ ብሎ ጨምሯል።”

ቀውሱን የሚያሳይ አንድ ምሳሌ መጥቅስ ይቻላል። በመቶዎች የሚቆጠሩ ሐኪሞች ሥራ ባለማግኘታቸው ምክንያት በአገሪቱ በሚገኙ ዋና ዋና ከተሞች ተቃውሞ እያሰሙ ነው።

ዶክተር ሙምታዝ ኢምራን-ቶማስ ሻይ እየቀዳች
የምስሉ መግለጫ, ዶክተር ሙምታዝ ኢምራን-ቶማስ

“በጣም ተስፋ አስቆራጭ ነው። ደቡብ አፍሪካውያን የጤና እንክብካቤ ቢፈልጉም እየተፍረከረከ ያለ ሥርዓት ነው ያለን። ለዚያም ነው 800 ሐኪሞች በቤት ውስጥ የተቀመጡት” ስትል የተናገረችው በህክምና ዘርፍ ሥራ ማግኘት ባለመቻሏ ሌላ ጊዜያዊ ሥራ የጀመረችው ዶክተር ሙምታዝ ኢምራን-ቶማስ ናት።

በተለይም ወጣቶች ለውጥን እየጠየቁ ነው። ኤኤንሲ ዲሞክራሲን ያሰፍናል የሚለውን እምነታቸውንም እየቀየሩ ነው።

ማንንም አንመርጥም የሚሉ በጣም ተስፋ የቆረጡም አሉ።

እንደ እናቴ ያሉ እና በአፓርታይድ ወቅት ኖረው የምርጫ ጥቅም የገባቸው አብዛኞቹ ዜጎች ግን አሁንም በምርጫ ያምናሉ።

ሰባተኛው አጠቃላይ ምርጫ ሲከናወን የስድስት ዓመት ልጄን ይዛ መጀመሪያ ድምጿን በሰጠችበት ክዋ-ቴማ ምርጫ ጣቢያ ተሰልፋ ድምጿን ትሰጣለች።

አርማ